Saturday, 03 May 2014 12:07

35 የሰማያዊና የ“አንድነት” አባላት ታሰሩ

Written by  አበባየሁ ገበያው
Rate this item
(3 votes)

           የአንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ፤ ነገ በአዲስ አበባ ለሚያደርገው ‹‹የእሪታ ቀን›› የሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ በራሪ ወረቀት ሲበትኑ የነበሩ ከሰባት በላይ አመራሮችና አባላት በፖሊስ ተይዘው መታሰራቸውን ገለፀ፡፡
በሌላ በኩል፤ ሰማያዊ ፓርቲ ባለፈው እሁድ ላካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ ሲያካሂዱ የነበሩ የፓርቲውን ምክትል ሊቀመንበር አቶ ስለሺ ፈይሳ እና ምክትል የምክር ቤት ሰብሳቢው አቶ የሽዋስ አሰፋን ጨምሮ 28 አባላቱ በእስር ላይ እንደሚገኙ ገልጿል፡፡ ከሰላማዊ ሰልፉ በፊት በነበሩት ማክሰኞ፣ ረቡዕ እና ሐሙስ ቀናት በተደረጉ የቅስቀሳ ስራዎች ላይ ሳሉ በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉት የፓርቲው አባላት ፍ/ቤት ቀርበው የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ የተጠየቀባቸው ሲሆን “ክስ ሳይመሰረትብን ዋስትና አንጠይቅም” በማለታቸው በእስር ላይ እንደሚገኙ የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
በነገው እለት አንድነት ለሚያካሂደው ሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ ሲያደርጉ የነበሩ የፓርቲው አመራሮችና አባላት ባለፈው ረቡዕና ሀሙስ የታሰሩ ሲሆን የፓርቲው ልሣን ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ነብዩ ሲራክ፣ የብሄራዊ ምክር ቤት የአዲስ አበባ ዞን ሰብሳቢ አቶ ዘካርያስ የማነ ብርሃን፣  የህዝብ ግንኙነት ቋሚ ኮሚቴ አመራር አቶ ዘላለም ደበበ እና ሌሎች አባላት በእስር ላይ እንደሚገኙ የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ሃብታሙ አያሌው ተናግረዋል፡፡
ፖሊስ የፓርቲውን አመራሮችና አባላት ያሰረው “በቤተመንግሥትና በፖሊስ ጣቢያ አልፋችኋል” በሚል ነው ብለዋል - አቶ ሀብታሙ፡፡ የአዲስ አበባ ፖሊስ በቁጥጥር ስር ባዋላቸው የአንድነት አመራሮችና አባላት ላይ ክስ እንደመሰረተባቸው የጠቆሙት አቶ ሀብታሙ፤ ትናንት በተለያዩ ፍርድ ቤቶች እንደቀረቡ ታውቋል፡

Read 2454 times