Monday, 14 April 2014 09:20

የአይዳና የጁሊ ስራዎች በጀርመን እየታዩ ነው

Written by 
Rate this item
(4 votes)

‘ዘ ናይንቲ ናይን ሲሪየስ’ የተሰኘው የአይዳ ሙሉነህ ስራ

የታዋቂዋ ኢትዮጵያዊት ፎቶግራፈር አይዳ ሙሉነህ እና የኢትዮ-አሜሪካዊቷ ሰዓሊ ጁሊ ምህረቱ የስነ-ጥበብ ስራዎች፣ በፍራንክፈርት የሞደርን አርት ሙዚየም (MMK) ውስጥ  በተከፈተ አለም አቀፍ ኤግዚቢሽን በመታየት ላይ እንደሚገኙ ታዲያስ ከኒውዮርክ ዘገበ፡፡
ታዋቂ አፍሪካውያን ዘመናዊ አርቲስቶች ስራዎቻቸውን ያቀረቡበትና ጣሊያናዊው የ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን  ገጣሚ ዳንቴ በጻፈው ‘ዘ ዲቫይን ኮሜዲ’ የተሰኘ የግጥም ስራ የተሰየመው ‘ሄቨን፣ ሄል፣ ፑርጋቶሪ ሪቪዚትድ ባይ ኮንቴምፖራሪ አፍሪካን አርቲስትስ’ የተባለው አለም አቀፍ የስነ-ጥበብ ኤግዚቢሽን፣ እስከ መጪው ሃምሌ አጋማሽ ድረስ ለተመልካች ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡
በታዋቂው የስነ-ጥበብ አጋፋሪ ሲሞን ጃሚ እና በሞደርን አርት ሙዚየም ትብብር በተዘጋጀው በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ የቀረቡት ስራዎች፣ በቀጣይም በተለያዩ የአለም አገራት በሚገኙ አራት ቦታዎች ለእይታ እንደሚበቁ ተነግሯል፡፡
ከዚህ ቀደሞቹ  ከአፍሪካ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ኤግዚቢሽኖች በተለየ የአፍሪካ ስነ-ጥበብ፣ የድህረ ቅኝ-ግዛት ጉዳዮችን ማንጸባረቅ ብቻ ሳይሆን ውበትን አጉልቶ በማሳየት ጭምር ጥቅም ላይ ሊውሉ ይገባል በሚል እምነት የዘንድሮውን ኤግዚቢሽን እንዳዘጋጀ፣ ሞደርን አርት ሙዚየም አመልክቷል፡፡
‘ዘ ናይንቲ ናይን ሲሪየስ’  የተሰኘውን ጨምሮ የተለያዩ ስራዎቿን በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ ለእይታ ያበቃችው አይዳ ሙሉነህ፣ ከሃዋርድ ዩኒቨርሲቲ በፊልም፣ በሬዲዮና በቴሌቪዥን ሙያ የመጀመሪያ ዲግሪዋን ያገኘች ሲሆን፣ ስራዎቿን በተለያዩ ታላላቅ ኤግዚቢሽኖች ላይ ከማቅረብ ባለፈ፣ በርካታ አለማቀፍ ሽልማቶችን ለማግኘት የቻለች የፎቶግራፍ ባለሙያ ናት፡፡  
በአሁኑ ወቅት፣ ‘ደስታ ፎር አፍሪካ’ (DFA Creative Consulting plc.) የተባለና ትኩረቱን የፈጠራ ሥራዎች ላይ በማድረግ፤ ለአገር ውስጥና ለዓለም አቀፍ ገበያ የሚሆኑ የፈጠራ ሃሳቦችን የማማከር፣ ደረጃቸውን የጠበቁ ፎቶግራፎችን የማንሳትና ባህላዊ ዝግጅቶችን የማቀድ አገልግሎቶችን የሚሰጥ ኩባንያ በማቋቋም፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የተለያዩ ስራዎችን በማከናወን ላይ ትገኛለች፡፡
የታላላቅ ኢትዮጵያውያን ሴቶችን ታሪክ በሚተርከውና በቅርቡ ለህትመት እንደሚበቃ በሚጠበቀው ‘ተምሳሌት’ የተሰኘ መጽሃፍ ውስጥ የተካተቱት በርካታ ፎቶግራፎችም በአይዳ የተነሱ ናቸው፡፡
ነዋሪነቷ በኒውዮርክ የሆነው ኢትዮ-አሜሪካዊቷ ሰዓሊ ጁሊ ምህረቱም፣ በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የስነጥበብ ትምህርቷን የተከታተለች በአለማቀፍ ደረጃ የምትጠቀስ ሰዓሊ ናት፡፡ የተለያዩ አለማቀፍ ሽልማቶችን የተቀበለች ሲሆን  የስዕል ስራዎቿም በከፍተኛ ዋጋ ተሸጠውላታል፡፡ ከእነዚህም መካከል፣ የዛሬ አራት ዓመት በታዋቂው አጫራች ድርጅት ሱዝቤይ አማካይነት፣ 1 ሚሊዮን 22 ሺህ  ዶላር (20 ሚሊዮን ብር ገደማ) የተሸጠላት ርዕስ አልባ ስዕሏ  ይጠቀሳል፡፡

Read 2164 times