Monday, 31 March 2014 11:01

“የአገር ፍቅር ከየትኛውም ሽልማትና ሞገስ በላይ ነው”

Written by 
Rate this item
(18 votes)

የአሜሪካ መንግሥት “የአፍሪካ ስኬታማ ወጣት መሪ” በሚል የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት መርጦ ለመሸለም ጥሪ ማድረጉን የፓርቲው ልሳን ጋዜጣ ባለፈው ሳምንት ዘግቧል፡፡ በሌላ በኩል ከአሜሪካ ኤምባሲ በኩል የተገኙ መረጃዎች የሰማያዊ ፓርቲ መሪ የተመረጡት የአሜሪካ  ስቴት ዲፓርትመንት  በየዓመቱ ለሚያዘጋጀው የሊደርሺፕ ፕሮግራም እንጂ ለሽልማት አይደለም ይላሉ፡፡  የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው የፓርቲውን ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃልን በጉዳዩና ኤርፖርት ላይ በገጠማቸው ችግር ዙርያ አነጋግራቸዋለች፡፡

ወደ አሜሪካ ለመጓዝ ኤርፖርት ከገቡ በኋላ ችግር እንደገጠመዎት ሰምቻለሁ፡፡ ችግሩ ምን ነበር?
በአሜሪካ መንግስት ተጋብዤ ለሶስት ሳምንት የምቆይበት “ወጣት የአፍሪካ መሪዎች” የሚል ፕሮግራም ነበር፡፡ በሉፍታንዛ ነበረ የምሄደው። በኤርፖርት ውስጥ አስፈላጊውን ሂደት ሁሉ አልፌ የኢሚግሬሽንና ደህንነት ሰዎች ፎቶ ወስደው ፓስፖርቴን ተቀበሉኝና አንደኛው አለቆቹ ጋር ይዞኝ ሄደ፡፡ ለሶስት ሰዓት ያህል አንድ ክፍል ውስጥ አቆዩኝ፡፡ መጨረሻ ላይ ከፓስፖርቴ ውስጥ አንድ ገፅ ነቅለው አውጥተው … “አንድ ገፅ ወጥታለች” ብሎ ቀዶ አመጣልኝ … እቃዬ አውሮፕላኑ ውስጥ ገብቶ ነበር፤ እሱንም አወረዱት፡፡ ባለፈው ሰኞ ነበር አሜሪካ መገኘት የነበረብኝ፤ ለጊዜው ተስተጓጉሏል።
የአሜሪካ መንግስት “የአፍሪካ ስኬታማ ወጣት መሪ” በሚል እንደሸለማችሁ ባለፈው ሳምንት በፓርቲያችሁ ልሳን ላይ ተዘግቧል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ዕድሜው አጭር ከመሆኑ አንፃር ሽልማቱ ይገባናል ትላላችሁ?
ኢትዮጵያ ከዓለም የመጨረሻ ድሃ አገር ናት፡፡ አገሪቱን ከድህነት ለማውጣት የልጆቻችንን ዕድሜ የሚጠይቅ ተከታታይ ሥራ እና ትግል የሚያስፈልገው ነው፡፡ ሥራችንን የምትለኪው ግን በአንፃራዊነት ነው፡፡ ለምሳሌ ሰልፍ የሚባል ነገር ለስምንት አመት ኢትዮጵያ ውስጥ የማይታሰብ ነበር፡፡ አሁን ግን ሁሉም ፓርቲዎች ሰልፍና የአደባባይ የፖለቲካ ስራን እንደ ባህል እየያዙትና፤ እየተነቃቁም ናቸው። የሌሎች ፓርቲ አመራሮች “ህዝቡ ፈርቷል፤ ሰልፍ አይወጣም፣ አይተባበረንም” በሚል ዝም ብለው የመግለጫ ስራ ነበር የሚሰሩት፡፡ አሁን  ነገሮች ተለውጠዋል፡፡ አዲሱ ትውልድ በፊት ተከታይ እንጂ የራሱ ሀሳብ ኖሮት የሚሳተፍ አልነበረም። በሰማያዊ ፓርቲ ውስጥ ግን ሌት ተቀን የሚተጉ ሰዎችን ታያለሽ… እስከመታሰርም ደርሰዋል፡፡ ይህም የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ የሚታየው የተፈጠረው የፖለቲካ መነቃቃትና ግንዛቤ ነው እንጂ የሀገራችንን ችግር ሰማያዊ ፓርቲ ፈትቶ ይጨርሰዋል ወይ ብትይ …. ትውልዱም የሚጨርሰው አይመስለኝም። ብዙ ተከታታይ ስራዎች ይጠይቃል፡፡ ከነበርንበት ጨለማ አንፃር ነው መታየት ያለበት፡፡ ቅንጅት በመፍረሱ ህዝቡ  ተስፋ ቆርጧል፡፡ ኢህአዴግ ጠቅላይ  በመሆኑና አፋኝ አዋጅ በመያዙ ዘላለማዊ ይመስል ነበር፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ያንን አስቸጋሪ ሁኔታ ወደ ይቻላል በማምጣትና መነቃቃት በመፍጠር የፖለቲካ ድባቡን ቀይሮታል፡፡ ይሄ ደግሞ ረጅም ጊዜንና ትልቅ ስራን የሚጠይቅ ነበር፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ግን በአጭር ጊዜ ይሄንን ማድረግ ችሏል፡፡ ከዚህ መንፈስ ነው የሚታየው እንጂ እኛ ብዙ ሰራን ብለን አንኩራራም፡፡ ገና ብዙ ስራ ነው የሚቀረን፤ ወደፊትም ብዙ እንሰራለን፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ አሁን በዘረዘሩልኝ ምክንያቶች በአሜሪካ መንግስት “የአፍሪካ ስኬታማ ወጣት መሪ” በሚል ሸልሞታል፤ ሽልማቱም ይገባናል እያሉኝ ነው?
አዎ .. በደንብ ተሸልመናል፡፡ ሽልማቱም ይገባናል፡፡ ሽልማቱ ይገባናል ስንል ግን አሜሪካኖች አይደሉም የሚሸልሙንና የሚያወድሱን፡፡ ግን በራሳቸው መመዘኛ እኛን መምረጣቸው መልካም ነገር ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ የሚያድግ ፓርቲ ነው፡፡ በኢትዮጵያ 70 ከመቶ የሚሆነው ህዝብ ወጣት ነው፡፡ ወጣቱን ሊወክል የሚችል ፓርቲ ነው፡፡ አዲስ አስተሳሰብን እንደፈጠረ ሃይል፣ ሽልማትን አስበን አይደለም የምንሰራው፡፡ ከዚህ በላይ ለሃገራችን ብዙ መስራት ይጠበቅብናል፡፡
በየጊዜው የተለያዩ ፖለቲከኞች ለህዝብ የገቡትን ቃል ሳይፈጽሙ ሸርተት ይላሉ፡፡ ህዝቡን ከዚህ ዓይነቱ ጥርጣሬ እንዴት ማውጣት ይቻላል ይላሉ?
ህልም ተፈርቶ ሳይተኛ አይታደርም፡፡ ከዚህ በፊት ኢትዮጵያ ውስጥ በተደጋጋሚ ውጤት ያልመጣው የግለሰብ ፖለቲካ በመሆኑና ፖለቲካው በሰዎቹ ስብዕና ላይ በመመስረቱ ነበር፡፡ ይሄም ትግሉን ጎድቷል፡፡ ለዚህ መፍትሔው ትግሉን ህዝባዊ ማድረግና በአንድ ሰው ላይ አለመንጠልጠል ነው፡፡ ህዝቡ ፖለቲካውን የራሴ ነው ብሎ መያዝ አለበት፡፡ ግለሰቦች ሲሄዱ ሌሎች ይተካሉ፡፡
ኢትዮጵያ የወላድ መካን አይደለችም፤ ብዙ ልጆች አሏት፡፡ ፖለቲካውን የጋራ ካደረግነው የህዝቡ ስጋት ይቀንሳል፡፡ ፖለቲካ የዜግነት ጉዳይ ነው፤ ሁሉም መሳተፍ አለበት፡፡ ያ በሆነ ጊዜ ራሳቸውን ብቻ ለአገር ጠቃሚ አድርገው የሚያስቡ ሰዎች መመፃደቃቸውን ያቆማሉ፡፡ ያኔ መግነንም አምባገነንነትም ይጠፋል፡፡ ፓርቲውም ህዝባዊነት ይኖረዋል ማለት ነው፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ልጆች የትኛውም ቦታ ላይ ተወዳድረውና ሰርተው መኖር የሚችሉ ናቸው፡፡ በዚህ በአሰልቺና በተጠላ ፖለቲካ ውስጥ የገቡት የአገር ፍቅር ስላላቸው ነው፡፡ የአገር ፍቅር ደግሞ ከየትኛውም ሽልማትና ሞገስ በላይ ነው፡፡   
ከወር በፊት ለፓርቲ ሥራ ወደ አሜሪካና አውሮፓ ተጉዘው ነበር፡፡ የተለያዩ ስብሰባዎችንም ከዳያስፖራው ጋር አድርጋችኋል፡፡ በዚህ ጉዞ ዋና ዓላማችሁ ምን ነበር?
ሁለት ወር ነው የቆየሁት፤ አውሮፓ አስራ አምስት ቀን፣ አሜሪካ 45 ቀን ያህል፡፡ አትላንታ፣ ሳንሆዜ፣ ቦስተን፣ ላስቬጋስ፣ ሎስአንጀለስ፣ ሲያትል… ነበርኩ። የመጀመሪያ ስብሰባዬ ዲሲ ነበር፡፡ የስብሰባው ዓላማ ሰማያዊ ፓርቲ የተመሰረተባቸውን መሰረታዊ አላማዎችና ምሰሶዎችን ማስተዋወቅ ነበር፡፡ እዚህም አብዛኛውን ቅዳሜና እሁድ ምሁራንን ቢሮዋችን ውስጥ እየጋበዝን በፀረ ሽብር ህጉ፣ በመሬት ፖሊሲ፣ በአጠቃላይ በኢኮኖሚ በታሪካችን ዙሪያ በመወያየት ሰማያዊ ፓርቲ ያለውን አቋም ለህዝብ በተደጋጋሚ ይገልጽ፣ ያስተምር ነበር፡፡ የአሜሪካና አውሮፓ ጉዞ ዓላማ፣ በውጭ ያለው ኢትዮጵያዊ ለሰማያዊ ፓርቲ ሀሳቦችና ፕሮግራሞች ድጋፍ እንዲሰጥና የትግል ስልቶቻችንንም ጭምር ለማስተዋወቅ ነበር፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ የቅስቀሳ ሀይል እንጂ ድርጅታዊ መዋቅር የለውም፤ የንቅናቄ ፓርቲ ነው፤ የበሰለ ፖለቲካ አያራምድም የሚል ትችት ይሰነዘርባችኋል? እርስዎ ምን ይላሉ?
የሞተን ፖለቲካ ልታነሺ የምትችይው፤ ህዝብ ሲከተልሽና መነቃቃትን መፍጠር የምትችይው የአገሪቱን ችግር በሚገባ መረዳት ሲቻል፣ ለዚያ ችግር መፍትሄ ሊሆን የሚችል ቀጥተኛ ፖሊሲ ሲኖር፣ ፖሊሲውን ለማስፈፀም ደግሞ ብቃት ያለው አመራር ሲኖር ነው ህዝቡ የሚነቃነቀው፡፡ በስልጣን ላይ የተቀመጡ ሰዎች ፖሊሲ አላቸው፤ ሰማያዊ ፓርቲዎች ግን ፖሊሲ የላቸውም ቢባል ለአመለካከት የማይመች ነው የሚሆነው፡፡ በመሰረቱ አንድ ሰው ሊነቃነቅ የሚችለው  የሚያምንበት ነገር ሲኖር ነው። መነቃነቅ ከተፈጠረ እምነት አለ፡፡
ተቃዋሚ ፓርቲዎች በህብረት ለመስራት የትብብርና የውህደት እንቅስቃሴ ላይ ቢሆኑም ሰማያዊ ፓርቲ ለውህደት ዳተኝነት ይታይበታል የሚል ትችት ይሰነዘርበታል…
በኢትዮጵያ የ40 ዓመት የፖለቲካ ፓርቲዎች ታሪክ “ዛሬ ተዋህደው፤ ነገ ፈረሱ” ሲባል ነው የምናውቀው፡፡ ይሄ እንዲቀጥል አንፈልግም፡፡ ስለዚህም የውህደትንና የጥምረትን ነገር በጥንቃቄ መመርመር እንፈልጋለን፡፡ በሆይሆይታ የሚፈጠሩ ጥምረቶችና ውህደቶች ውጤቱ ሲያመጡ አልታየም። ለምሳሌ አንድነት ወደ መድረክ የገባው በጣም ፈጥኖ ስለነበር ራሱን ጎድቷል፡፡ እናም አንድነት ከመድረክ ታገደ ተባለ፡፡ ሰላሳ ሶስት ፓርቲዎች ተቋቁመው ምንም ነገር ሳይፈይዱ ነው የከሰሙት። በቅርቡ ደግሞ “አንድነትና መኢአድ ለውህደት እየተነጋገሩ ነው” ሲባል ነበር፡፡ አሁን ደግሞ ተቋረጠ ተብሏል፡፡ እኛ ጥናት ሳይደረግ በፍጥነት ሮጠን ወደ ውህደት አንገባም፡፡ ወደ ፖለቲካው ያልገባ አዲሱ ትውልድ አለ፤ ፓርቲዎች አካባቢ ጊዜ ከምናጠፋ እዛ ላይ አተኩረን ህዝብ ውስጥ ብንሰራ ጉልበትም፣ ሀይልም፣ ዕውቀትም ገንዘብም አለ የሚል አቋም ይዘን ነው የምንንቀሳቀሰው፡፡ በመርህ ደረጃ ግን ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ለመስራት ሰማያዊ ፓርቲ ዝግጁ ነው፡፡
የምርጫ ስነ ምግባር ኮዱን አንፈርምም ብላችኋል፡፡ ለምንድነው ለመፈረም ያልፈለጋችሁት?
አንድ ህግ በሀገር ደረጃ ህግ ሆኖ ከወጣ በኋላ መፈረም አለመፈረም አስገዳጅ አይደለም፤ ትክክለኛም አሰራር አይደለም፡፡ ለምሳሌ የማናምንባቸው አዋጆች ሁሉ ወጥተዋል፡፡ የፀረ-ሽብር አዋጅ፣ የመሬት ሊዝ አዋጅ፣ የሲቪክ ማህበራት ማደራጃ፣ የሚዲያና የመረጃ ነፃነት አዋጅ ወጥተዋል፡፡ እነዚህን አዋጆች ሰማያዊ ፓርቲ አፋኝ አዋጆች ናቸው ብሎ ያምናል፡፡ ህግ ሆነው ከወጡ በኋላ ግን ህገመንግስታዊ በሆነ መንገድ እስከ ምንቀይራቸው ድረስ ለአዋጆቹ መገዛት ግዴታችን ነው፡፡ የስነ ምግባር ደንብና አዋጅ በፓርላማ ህግ ሆኖ ፀድቋል፤ ለእሱ ብቻ መፈረም አያስፈልግም። አዋጅ በወጣ ቁጥር እኮ አንፈርምም፡፡ አጀንዳ ሆኖም መቅረብ የለበትም፡፡ ኢህአዴግ ለድርድር እንቅፋት ለመፍጠር ሲፈልግ ያመጣው ነው፡፡

Read 6852 times