Monday, 31 March 2014 10:51

አነስተኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች በግል ጤና ተቋማት የሚታከሙበት አሰራር ሊጀመር ነው

Written by  መታሰቢያ ካሳዬ
Rate this item
(2 votes)

          በቀጣዩ ዓመት ከአገሪቱ የመድኀኒት ፍጆታ ግማሽ  ያህሉን በአገር ውስጥ ለማምረት ታቅዷል
አነስተኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች በግል የጤና ተቋማት ውስጥ ተጠቃሚ የሚሆኑበትን አሰራር ተግባራዊ ለማድረግ ጥረት መጀመሩ ተገለፀ፡፡ ድሃውን ተጠቃሚ የሚያደርግ የግል የጤና ተቋም ቀጣይነቱ አጠያያቂ ነው ተብሏል፡፡
“The private Health Sector in Ethiopia at a Crossroads” በሚል ሰሞኑን ለሁለት ቀናት በተዘጋጀው ጉባኤ ላይ እንደተገለፀው፤ የግሉ የጤና ሴክተር ከመንግስት የጤና ዘርፍ ጋር በትብብር በመስራት አነስተኛ ገቢ ያላቸውን ዜጎች ተጠቃሚ ለማድረግ ጥረት ያደርጋል፡፡ አብዛኛ ህብረተሰብ በግል የጤና ተቋማት ውስጥ አገልግሎት ለማግኘት አቅም የሌለው በመሆኑ፣ የግሉን የጤና ዘርፍ በተለያዩ መንገዶች በማገዝ አገልግሎቱን ለድሃው ህብረተሰብ ለመስጠት የሚቻልበትን መንገድ መፈለግ አማራጭ የሌለው ጉዳይ ነው ተብሏል፡፡
በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የሚኒስትሩ ቢሮ ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አዲስ ታምሪ ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት፤የመንግስትና የግሉ የጤና ተቋማት በትብብር በመሥራት በአገሪቱ የጤናው ዘርፍ የሚታየውን እጥረት ለመቅረፍ ጥረት ያደርጋሉ። የግሉ የጤና ዘርፍ ከመንግስት በሚደረግለት ድጋፍና ትብብር አገልግሎቱን በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረበ፣ድሃውን ህብረተሰብ ተጠቃሚ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ መንግስት በቅርቡ ተግባራዊ ማድረግ የሚጀምረው የግሉንም ሆነ የመንግስትን የጤና ተቋማት ደረጃ የሚያወጣው መመሪያ ተግባራዊ መሆን ይህንን አሰራር ለመቆጣጠርም እንደሚረዳ ዶ/ር አዲስ ተናግረዋል፡፡ አገሪቱ በጤናው ዘርፍ እየተገበረች ላለው ሥራ የግሉ የጤና ዘርፍ የሚያበረክተው አስተዋፅኦ በቀላሉ የሚገመት እደለም ያሉት ዶክተሩ፤ ይህንን አስተዋፅኦ የበለጠ ለማሳደግ እንዲችል ድጋፍ ሊደረግለት ይገባል ብለዋል፡፡ የግሉና የመንግስቱ የጤና ተቋማት በትብብር ድሃውን በተመጣጣኝ ዋጋ ለማገልገል የሚችሉበትን መንገድ ማመቻቸት ጊዜ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ አይደለም ሲሉ ዶክተሩ ተናግረዋል፡፡
በቀጣዩ አመት አገሪቱ ከሚያስፈልጋት የመድኀኒት ፍጆታ ግማሽ ያህሉ በአገር ውስጥ በሚገኙ የመድኀኒት ማምረቻ ፋብሪካዎች የሚመረቱ እንደሆኑ ዕቅድ መያዙንም ዶክተሩ በዚሁ ጊዜ ተናግረዋል፡፡

Read 1782 times