Monday, 31 March 2014 10:49

“የትግራይ አርሶ አደሮች በካድሬዎች መብታቸው እየተረገጠ ነው”

Written by  አበባየሁ ገበያው
Rate this item
(1 Vote)

በነገው እለት በትግራይ ክልል በእንደርታ ኪዊሃ፣ ህዝባዊ ስብሰባ እንደሚያካሂድ የገለፀው ዓረና ፓርቲ፤የትግራይ አርሶ አደሮች በካድሬዎች መብታቸው እየተረገጠና እየታፈነ ነው አለ፡፡
95 ፐርሰንት ያህሉ አርሶ አደሮች ከብድር ተቋማት ከ5ሺ እስከ 30ሺ ብር ብድር መውሰዳቸውን ከአንድ ጥናት መረዳታቸውን የጠቆሙት የፓርቲው ሥራ አስፈፃሚ አቶ አብርሃ ደስታ፤ ዓረና ለመጪው ምርጫ የፓርቲውን ፕሮግራም ለማስተዋወቅ በተዘዋወረባቸው የገጠር ክፍሎች አርሶ አደሮቹ በወሰዱት ብድር የተነሳ  መብትና ነፃነታቸው እየታፈነ መሆኑንና ክፉኛ እንደተማረሩም ተናግረዋል፡፡
የዓረና ፓርቲ አመራሮች ህዝባዊ ስብሰባ ባደረጉባቸው ሰባት የገጠር ክፍሎች፣ የትግራይ አርሶ አደሮች በማዳበሪያ ዕዳና በብድር በመያዛቸው ህወሐትን የሚቃወሙ ከሆነና በዓረና  ስብሰባ ላይ ከተገኙ፣ ዕዳችሁን ክፈሉ እየተባሉ መውጪያ መግቢያ እንደሚያጡ አቶ አብርሃ ገልፀዋል፡፡ በዚህም የተነሳ ነፃነት ተነፍገው ከህወሐት በቀር ሌላ ፓርቲ እንዳይደግፉ መብታቸውን ተነፍገዋል ብለዋል፡፡
ባለፉት  ወራት ከሳዑዲ ከተመለሱ ኢትዮጵያውያን መካከል አብዛኞቹ በትግራይ ክልል የሚገኙ ወጣቶች እንደነበሩ የጠቆሙት የፓርቲው ሥራ አስፈፃሚ፤ የስደት ተመላሾቹ “ለሥርዓቱ አደገኛ ናቸው” በሚል በመገለላቸው፣ አብዛኞቹ በእግርና በባህር እያቋረጡ ወደየመንና ሳኡዲ ተመልሰው እየተጓዙ ነው ብለዋል፡፡

Read 1747 times