Saturday, 22 March 2014 12:00

ከአሜሪካ የመጡ የሙስሊም ምሁራን የታሰሩ ሙስሊሞችን ከመንግስት ጋር ያደራድራሉ

Written by  አበባየሁ ገበያው
Rate this item
(10 votes)

           በአሜሪካ አገር ‹‹በድር ኢትዮጵያ›› የተሰኘውን የሙስሊም ማህበር የሚመሩ ምሁራንና ታዋቂ ሰዎች፤ የታሰሩ ሙስሊሞችን ከመንግስት ጋር ለማሸማገል በኢትዮጵያ መንግስት ፈቃድ ሰሞኑን አዲስ አበባ መግባታቸው ተነገረ።
በአወሊያ ትምህርት ቤት ሰበብ የተቀሰቀሰው ውዝግብ ቀስ በቀስ እየተካረረ፤ የእስልምና ጉዳዮች ጠቅላላ ጉባኤ ምርጫም የመወዛገቢያ ነጥብ ወደመሆን እንደተሸጋገረ የሚታወስ ሲሆን፤ በ2004 ዓ.ም በርካታ የተቃውሞ ሰልፎች ከተካሄዱ በኋላ ነው፤ በሐምሌ ወር ሃያ ዘጠኝ ሰዎች ታስረው ክስ የተመሰረተባቸው፡፡ ታህሳስ 2006ዓ.ም. አስሩ ታሳሪዎች የሚያስከስስ ጥፋት የለባቸውም ተብለው በፍ/ቤት ቢለቀቁም የአስራ ዘጠኝ ታሳሪዎች ክስ በፍ/ቤት እየታየ መሆኑ ይታወቃል፡፡
የሙስሊሙ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ በሚል ስያሜ ሲንቀሳቀሱ የነበሩት ታሳሪዎች፤ “የአወሊያ ት/ቤት ራሱን ችሎ መንቀሳቀስ አለበት፤ የእስልምና ጉዳዮች ጠቅላላ ጉባኤ ምርጫ በተጽእኖ ስር የተከናወነ ነው” በማለት ተቃውሞ ሲያሰሙ ቆይተዋል፡፡ የአወሊያ ት/ቤትን ተገን በማድረግ አክራሪነትን ለማስፋፋት እንቅስቃሴ ሲደረግ ነበር የሚለው መንግስት በበኩሉ፤ የእስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤት ምርጫ በአግባቡ አልተከናወነም የሚለው ተቃውሞ፤ ግጭት ለመቀስቀስ ታስቦ የተዘጋጀ መሰረተ ቢስ ውንጀላ ነው ይላል፡፡  
በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት እየታየ ባለው የክስ ሂደት አስራ ዘጠኙ ተከሳሾች በአቃቤ ህግ ለቀረበላቸው የክስ ማስረጃ መከላከያ እንዲያቀርቡ የታዘዙ ሲሆን ከሚቀጥለው ማክሰኞ ጀምሮ ለ15 ቀናት በተከታታይ መከላከያ ያሰማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በዚህ መሃል ነው፤ በሽምግልና ታሳሪዎቹን ሊያስፈቱ ይችላሉ የተባሉ ታዋቂ ሙስሊሞች ሰሞኑን ከአሜሪካ የመጡት፡፡
‹‹በድር ኢትዮጵያ›› የተሰኘው ማህበር መሪዎችና አባላት የሆኑት እነዚሁ ሙስሊም ዶክተሮችና ፕሮፌሰሮች አዲስ አበባ የገቡት በመንግስት ፈቃድ እንደሆነ የገለፁልን ምንጮች፤ ታሳሪዎችን ያነጋግራሉ ብለዋል፡፡

Read 3836 times