Tuesday, 04 March 2014 11:52

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ቅጥር ፈታኝ ሆኗል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ቅጥር ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን  ፈታኝ  እንደሆነበት የተለያዩ ሁኔታዎች ያመለክታሉ፡፡ ፌደሬሽኑ ለሁለት ዓመት በዋና አሰልጣኝነት የመሩትን ሰውነት ቢሻው፤ ምክትላቸውንና የግብ ጠባቂዎችን አሰልጣኝ ካሰናበተ በኋላ ብሄራዊ ቡድኑ ያለ አሰልጣኝ አንድ ወር ሆኖታል፡፡ ለዋና አሰልጣኙ ቅጥር የሚያስፈልጉ ዝርዝር መስፈርቶቹን የቴክኒክና ልማት ኮሚቴ ለፌደሬሽኑ ካሳወቀ በኋላ ክፍት የስራ ቦታ ማስታወቂያው ሰሞኑን ወጥቷል፡፡
ማስታወቂያ
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት አመልካቾችን አወዳድሮ ለመቅጠር ያስቀመጣቸው መስፈርቶች ሃላፊነቱ በከፍተኛ ጫና ውስጥ መውደቁን ያመለክታሉ፡፡ የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ መስፈርቱን የሚያሟሉ አመልካቾች ማስረጃቸውን ፅህፈት ቤት በግንባር ተገኝተው በማቅረብ መመዝገብ እንደሚችሉ ቢያስታውቅም መቼ የቅጥር ሂደቱ እንደሚፈፀም የሰጠው ፍንጭ የለም፡፡ ፌደሬሽኑ ለቅጥሩ ባወጣው ማስታወቂያ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት  ብቁ የሚሆን ተወዳዳሪ ከታወቀ የትምህርት ተቋም ዲኘሎማ ያገኘና ተመጣጣኝ ወይም ከዛ በላይ የትምህርት ደረጃ ያለው፣ በእግር ኳስ አሰልጣኝነት ከፍተኛ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው የምስክር ወረቀት ማቅረብ የሚችል፣ በእግር ኳስ የማሰልጠን የCAF “B” ወይም ከዛ በላይ ፈቃድ ላይሰንስ (License) ያለው፣ በብሔራዊ ቡድኖች ወይም በከፍተኛ ሊግ ውድድሮች ደረጃ ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገበ፣ ዕድሜው ከ35 በላይ መሆን እንዳለበት አመልክቷል፡፡ የእንግሊዝኛ ቋንቋ መናገር ማንበብና መፃፍ የሚችል፣ በኮምፒዩተር ችሎታ እውቀት ያለው፣ ብሔራዊ ቡድኑን የማስተባበርና የመምራት ችሎታ ያለው፣ከፍተኛ ጫና ባለበት ተቋቁሞ መስራት የሚችልና ፈጣን ውሳኔ የመወሰን ችሎታ ደግሞ ለዋና አሰልጣኝነት የሚወዳደረው አመልካች የሚያስፈልገው ችሎታ እንደሆነም ዘርዝሯል፡፡ ፌደሬሽኑ ለክፍት የስራ ቦታው በጠየቀው የሥራ ልምድ ከ1ዐ ዓመት በላይ በብሔራዊ ቡድኖች ወይም ከፍተኛ ሊጐች ደረጃ በዋና አሰልጣኝነት የሰራ ያሠለጠነ በዓለም አቀፍ ደረጃ የማሰልጠን ልምድ ያለውን እንደሚያበረታታ ገልፆ፤ የቅጥር ሁኔታው     በኮንትራት ሆኖ በሚያስመዘግበው ውጤት እንደ አስፈላጊነቱ ሊራዘም እንደሚችል አስታውቋል፡፡ የሚቀጠረውን አሰልጣኝ ተግባርና ኃላፊነትን በመዘርዘር ካስቀመጣቸው መስፈርቶች መካከል   የአጭር፣ የመካከለኛና የረጅም ጊዜ የስልጠና ዕቅድ መሠረት ያደረገ ዝግጅትና ተግባር የሚያከናውን፤ ብሔራዊ ቡድኑን በማንኛውም ደረጃ ለሚደረጉ ውድድሮች በብቃት የሚያዘጋጅ፤ ብሔራዊ ቡድኑ ለሚያደርጋቸው ጨዋታዎች፣ ውድድሮች በተመለከተ ከጨዋታ በፊት እቅድና ከጨዋታ በኋላ የአፈፃፀም ሪፖርት በወቅቱ በኃላፊነት የሚያቀርብ ፣ የሩብ፣ የግማሽና የዓመት የዝግጅት አፈጻጸም ዕቅድ የሚያቀርብ፤ ከብሔራዊ ቴክኒክና ልማት ኮሚቴ እና ከዲፖርትመንት ጋር ብሔራዊ ቡድኑ ውጤታማ በሚሆንባቸው ሁኔታዎች ላይ ተባብሮ የሚሰራ፤ የእግር ኳስ አሰልጣኞች ስልጠና እንዲሰጥ በሚጠየቅበት ጊዜ የሚሰጥ፤ ከኘሪሚየር ሊግ እና ከብሔራዊ ሊግ ክለብ አሰልጣኞች ጋር ተቀራርቦ የሚሰራ፤ የሚያሰለጥናቸውን የእያንዳንዱን ብሔራዊ ቡድን ተጫዋቾች የቀድሞ የእግር ኳስ ኘሮፋይል የሚያሰባስብና የሚያደራጅ ፤በአገሪቱ እግር ኳስ ላይ የእግር ኳስ ኘሮፊሽናሊዝም እንዲበረታታ እንዲስፋፋ የሚያደርግና የኢትዮጵያ ወጣት U-17፤ U-20 እና የኦሎምፒክ ቡድንን የሚያግዝ መሆን እንዳለበት አስቀምጧል፡፡
ፈታኞቹ ሁኔታዎች
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ  ቅጥርን በቶሎ እና በስኬታማ ሂደት ለማከናወን የእግር ኳስ ፌደሬሽኑን ፈተና ያከበዱት በርካታ ሁኔታዎች ናቸው፡፡  የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ዋና ብሄራዊ ቡድኑ ያለ ዋና አሰልጣኝ  ወር እንዲያልፍ ከማድረጉ በተያያዘ በፊፋ የወዳጅነት ጨዋታ ፕሮግራም ተገቢውን ዝግጅት እንዳየደርግ ምክንያት ሆኗል፡፡ በሌላ በኩል ፌደሬሽኑ እያዘጋጀ ያለው ስትራቴጂክ እቅድ ገና በይፋ ካለመፅደቁ ጋር በተያያዘ  የአዲስ አሰልጣኝ ቅጥሩን ለማከናወን ግራ መጋባቱም አልቀረም፡፡ አንዳንድ የመረጃ ምንጮች የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ክፍቱን የስራ ቦታ በጊዜያዊ ሹመት ሰጥቶ ደረጃውን የጠበቀ ምርጥ አሰልጣኝ ለመቅጠር በቂ ጊዜ መድቦ ለመስራት ፍላጎት እንዳለውም እያመለከቱ ናቸው፡፡
ለብሄራዊ ቡድኑ ዋና አሰልጣኝነት የሚበቃ ኢትዮጵያዊ አሰልጣኝ ለማግኘት በአገር ውስጥ እየሰሩ ካሉ ባለሙያዎች የጎላ ወቅታዊ ብቃት እና ተገቢ ልምድ ያለው አሰልጣኝ ለማግኘት ያለው እድል መጥበቡም ሌላው ፈተና ነው፡፡ በተያያዘም ለብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት ኢትዮጵያዊ ወይንስ  የውጭ ዜጋ የቱ ይሻላል በሚለው አጀንዳ በስፖርት ቤተሰቡ መካከል የተቀሰቀሰው ውዝግብ የቅጥሩን ሂደት አጓጊ እና አስጨናቂ አድርጎታል፡፡ ፌደሬሽኑ በጊዜያዊነት ለዋና አሰልጣኙ ቅጥር ብቻ ትኩረት መስጠቱም ብሄራዊ ቡድኑ ዓለም አቀፍ ተፎካካሪነት እንዲኖረው ለማስቻል ሙሉ አቅም ያለው ስታፍ ማስፈለጉን አለማስተዋሉም ያሳስባል፡፡ እንደ ጋና አይነት ብሄራዊ ቡድኖች ከዋና አሰልጣኙ ጋር የሚሰሩ ከ13 በላይ የተለያዩ ባለሙያዎች ቀጥረዋል፡፡ በጋና ብሄራዊ ቡድን ከዋና አሰልጣኙ ሌላ አንድ ምክትል አሰልጣኝ፤ ሁለት የግብ ጠባቂ አሰልጣኞች፤ የቴክኒክና የተጨዋቾች ምርጫ የሚመለከታቸው ሃላፊዎች፤ የስነልቦና የምግብ እና የፊዚዮ ቴራፒ አገልገሎት የሚሰጡ ባለሙያዎች፤ የብሄራዊ ቡድኑ ቃል አቀባይ፤ የትጥቅ ሃላፊ፤ ልብስ ሰፊ፤ ከበሮ መቺ ተጠቃሽ የሃላፊነት ስፍራዎች ናቸው፡፡ ይሁንና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌሬሽን ከዋና አሰልጣኙ ቅጥር ባሻገር ለሌሎች የአሰልጣኝ ድጋፍ ሰጪ ባለሙያዎች ቅጥር ስላለው ፍላጎት የሚታወቅ ነገር የለም፡፡ ወይም የታሰበበት አይመስልም፡፡
ሌላው ፈተና የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ በሚያከናውነው ቅጥር የውጭ ዜጋ  ከመረጠ በወቅታዊው የገበያ ሁኔታ  የሚያስፈልገው የደሞዝ ክፍያ ከፍተኛነት ሲሆን ይህንንም ለማሳካት የፋይናንስ ምንጩ ከየት እንደሚገኝ በግልፅ አለመታወቁ ናቸው፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽን ለዋና አሰልጣኙ ቅጥር የሚከፍለውን ደሞዝ በስምምነት ለማድረግ ይፈልጋል፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ በአሰልጣኝነት ከፍተኛው ተካፋይ የነበሩት ሰውነት ቢሻው ይከፈላቸው የነበረው ወርሃዊ ደሞዝ 50 ሺብር በዶላር ሲመነዘር ከ3ሺ ያንሳል ፡፡ ሰውነት ቢሻው ኢትዮጵያዊ በመሆናቸው ክፍያው ተመጣጣኝ ሊሆን በቅቷል፡፡ ይሁንና አንዳንድ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በአሁኑ ጊዜ በአፍሪካ ደረጃ የሚሰሩ ዋና አሰልጣኞች ለየአገሮቹ ዜጋ በወር እስከ 11ሺ ዩሮ የውጭ አገር ዜጋ ከሆኑ ደግሞ እስከ 110ሺ ዩሮ መተመኑ የገበያውን ውድነት ያሳያል፡፡ የግብፅ ብሄራዊቡድን አሰልጣኝ የነበሩት አሜሪካዊ ቦብ ብራድሌይ በወር 35ሺ ዶላር፤ የምዕራብ አፍሪካ ቡድኖችን ያሰለጠኑት ፈረንሳዊ ሄነሪ ሚሸል 50ሺ ዶላር፤  ስዊድናዊ ሰኤሪክሰን አይቬሪኮስትን ሲያሰለጥኑ እስከ 175ሺ ዶላር፤ የካሜሮን አሰልጣኝ የነበሩት ፖል ሌግዌን 80ሺ ዶላር በላይ የሚከፈላቸው ነበሩ፡፡ በቅርብ ጊዜ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆነው የሰሩት ጋርዚያቶ እስከ10ሺ ዶላር ከዚያም በኋላ የሰሩት ኢፌም ኦኑራ 13ሺ ዶላር ይከፈላቸው እንደነበር ይታወሳል፡፡ ቶም ሴንት ፌይት ደሞዝ ባይከፈላቸውም ሺ ዶላር ተከፍሏቸው ለመስራት ፍላጎት የነበራቸው ሲሆን በናይጄርያ የቴክኒክ አማካሪነት 20ሺ ዶላር በወር ያገኙ ነበር፡፡ሚቾ በሩዋንዳ  ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት ሲሰሩ 16ሺ በኡጋንዳ ደግሞ 25ሺ ዶላር እየታሰበላቸው ነው፡፡ከላይ ከተዘረዘሩት የውጭ ዜጋ አሰልጣኞች መካከል እና አስቀድመው በኢትዮጵያ የሰሩ ባለሙያዎችን ወቅታዊ ዋጋ በመመዘን  ፌደሬሽኑ ለዋና አሰልጣኙ ቅጥር ወርሃዊ ክፍያ እስከ 30ሺ ዶላር ሊያስፈልገው እንደሚችል ይገመታል፡፡
ኢትዮጵያዊ ወይንስ  የውጭ ዜጋ?
ለዋና ብሄራዊ ቡድኑ አሰልጣኝነት ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚገኙ አሰልጣኞች በይፋ ፍላጎቱን የገለፀ እና ያመለከተ ባለሙያ ስለመኖሩ የታወቀ ነገር የለም፡፡ ይሁንና ባለፉት ሁለት ሳምንታት ከተለያዩ የአውሮፓ አህገራት እና በአፍሪካ ውስጥ ታላላቅ ቡድኖችን ያሰለጠኑ 10 ትልልቅ አሰልጣኞች ብሄራዊ ቡድኑን ለመያዝ ያላቸውን ፍላጎት ለፌደሬሽኑ እንዳስታወቁ ከሁለት ሳምንት የእግር ኳስ ፌደሬሽኑን ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻህን በማነጋገር በሱፕርስፖርት በተሰራ ዘገባ ተገልጿል፡፡ ይሁንና የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ በሚያከናውነው ቅጥር የውጭ ዜጋ  ከመረጠ በወቅታዊው የገበያ ሁኔታ  የሚያስፈልገው የደሞዝ ክፍያ ከፍተኛነትና ለማሳካት የፋይናንስ ምንጩ ከየት እንደሚገኝ ግልፅ አልሆነም፡፡  ከአገር ውስጥ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን በዋና አሰልጣኝነት ለመረከብ በይፋ ፍላጎታቸውን የገለፁ ባይኖሩም ቀድሞ ዋናውን ብሄራዊ ቡድን ያሰለጠኑት እና የሴቶች ብሄራዊ ቡድንን ያሰለጠኑት ኢንስትራክተር አብርሃም ተክለሃይማኖት ለሃላፊነቱ የታጩበትን ሁኔታ ሳይቀበሉት መቅረታቸው ተነግሯል፡፡ ከዚያ ባሻገር ከኢትዮጵያ ቡና ጋር የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው እና አሁን በሱዳኑ ክለብ አልሃሊ ሼንዲ  የሚሰራው ውበቱ አባተ ፤ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ክለብ አሰልጣኝ የሆነው ፀጋዬ ኪዳነ ማርያም፤ የመከላከያ ክለብ አሰልጣኝ የሆነው ገብረመድህን ሃይሌ እንዲሁም የቀድሞው የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ አስራት ሃይሌ ለሃላፊነቱ ብቁ ስለመሆናቸው ተባራሪ ወሬዎች  ያመለክታሉ፡፡  ከውጭ ዜጎች መካከል ደግሞ ቤልጅማዊው የቀድሞው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ የነበሩት ቶም ሴንትፌይት ወደ ሃላፊነቱ ለመመለስ ያላቸውን ፍላጎት ለሱፕር ስፖርት ሲገልፁ፤ በአሁኑ ጊዜ የኡጋንዳ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ የሆኑት ሰርቢያዊው ሰርዴጆቪች ሚሉቲን ደግሞ ለአሰልጣኙ ቅጥር የሚጠቅሙ ምክሮችን በመለገስ፤ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ማሰልጠን ታላቅ ክብር መሆኑን  ከ2 ሳምንት በፊት ከስፖርት አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለምምልስ መግለፃቸው አይዘነጋም፡፡  በኡጋንዳ ብሄራዊ በድን ዋና አሰልጣኝነት ኮንትራት ያላቸው ሰርዴጆቪች ሚሉቲን ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የቅጥር  ማመልከቻ ማስገባታቸው አይጠበቅም፡፡ በአንፃሩ ቤልጅማዊው ቶም ሴይንትፌይት የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ የቅጥር ማስታወቂያውን ካወጣ በኋላ ለፌደሬሽኑ  ማመልከቻ ሊያስገቡ እንደሚችሉ ይገመታል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን በዋና አሰልጣኝነት ለመምራት ፍላጎታቸውን በተለያየ መንገድ አሳውቀዋል ከተባሉ 10 የውጭ አገር ባለሙያዎች መካከል በይፋ  ለሃላፊነቱ ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የስራ ማመልከቻ ማስገባታቸው እንደማይቀር የተወራላቸው በስፔን ላ ሊጋ በሚወዳደሩ ክለቦች በተጨዋችነት  እና  በአሰልጣኝነትየ25 አመት ከፍተኛ የስራ ልምድ  ያካበቱት የ57 ዓመቱ አንቶኒዮ ሎፔዝ  ናቸው፡፡ እንደሆኑ ሱፕር ስፖርት የገለፀው ከሁለት ሳምንት በፊት ነበር፡፡  ስፔናዊው አንቶኒዮ ሎፔዝ በስፔን ላ ሊጋ ውስጥ አትሌቲኮ ማድሪድ፣ሲቪላ ጨምሮ በተለያዮ ክለቦች በተጨዋችነት ያሳለፉ እና ሴልታ ቪጎን እና ቫሌንሲያን በማሰልጠን ከፍተኛ ልምድ ያካበቱ ፤በደቡብ አፍሪካ ሁለት ክለቦችን ያሰለጠኑና በፊት የቦሊቪያን ብሔራዊ ቡድን ሁለት ጊዜ የኮፓ አሜሪካ ውድድር ተሳታፊ እንዲሆን ያስቻሉ ናቸው፡፡

Read 2359 times