Tuesday, 04 March 2014 11:47

ኢንዱራሊ የመኪናና የሞተር ብስክሌት ውድድር ነገ ይካሄዳል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

የኢትዮጵያ ሞተር ስፖርት አሶሴሽን ያዘጋጀው የኢንዱራሊ የመኪናና የሞተር ብስክሌት ውድድር ነገ በቃሊቲና አቃቂ አካባቢ ገላን ገበሬ ማህበር ክልል ውስጥ እንደሚካሄድ ታወቀ ፡፡ የሞተር ስፖርት አሶሴሽኑ የበላይ ጠባቂ የሆኑት የተከበሩ አቶ አባዱላ ገመዳ ውድድሮቹን በስፍራው ተገኝተው እንዲያስጀምሩ ጥሪ ተደርጎላቸዋል፡፡ ኢንዱራሊ   በ2006 ዓ.ም ለማካሄድ በዕቅድ ከያዛቸው ውድድሮች መካከል አንዱ መሆኑን የገለፁት የአሶሴሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ኤርምያስ አየለ  በቀጣይ ወራት ሁለት የከተማ እና አንድ የከተማ ውጭ ውድድሮችን እንደሚዘጋጁም ተናግረዋል፡፡
በኢንዱራሊ የመኪናና የሞተር ብስክሌት ውድድር ላይ 15 መኪናዎችና 27 ሞተርብስክሌቶች እንደሚካፈሉ የሚጠበቅ ሲሆን ከተወዳዳሪዎቹ መካከል 4 ኢትዮጵያዊያን፤ 9 የጣልያናውን፤ 1 ጅቢቲያዊና 1 ህንዳዊ ይገኙበታል፡፡
የመኪናው ውድድር በአራት ምድብ ተከፍሎ እንደሚካሄድ ያመለከተው የሞተር ስፖርት አሶሴሽኑ መግለጫ ባለ 2000 ሲሲ ቱርቦ መኪናዎች በአንደኛው ምድብ፤ ከ1601 እስከ 2000 ሲሲ በሁለተኛው ምድብ፤ ከ1301 እስከ 1600 ሲሲ በሶስተኛው ምድብ፤ በአራተኛው ምድብ ደግሞ እስከ 1300 ሲሲ ጉልበት ያላቸው መኪናዎች ይወዳደሩበታል፡፡ የውድድር መኪናዎቹ የተለያየ ጉልበት ያላቸው ብቻ ሳይሆኑ ዓይነታቸውም እንደሚለያይ የገለፀው አሶሴሽኑ ፎርድ፤ ፔጆት፤ ላንቻ ዴልታ፤ ሚትሱቢሺ፣ ቶዮታ፣ ኦፔል፣ ሱዙኪና ሊፋን መኪናዎች መሆናቸውን አስታውቋል፡፡  
በተጨማሪ በሚካሄደው  የሞተር ብስክሌት እሽቅድምድም ላይ 4 ኢትዮጵያዊያን፤ 7 ፈረንሳዊያን፤ 5 ጣሊያናዊያን፤ 6 ጅቡቲያዊያን፤ 2 አሜሪካዊያን፤ 1 እንግሊዛዊ እና 1 ጀርመናዊ እንደሚሳተፉ ሲታወቅ መወዳደርያዎቹ ሞተር ብስክሌቶች ከ125 እስከ 600 ሲሲ ጉልበት ያላቸው ናቸው፡፡
የኢንዱራሊ የመኪናና የሞተር ብስክሌት ውድድሩን ከጀላዳ ራይደርስ ጋር በመተባበር እንዳዘጋጀው የገለፀው የኢትዮጵያ ሞተር ስፖርት አሶሴሽን  ቢጂአይ አምበር ቢራ፤ ኮባ ኢምፓክት፣ አልታ አውቶ ካር ኬር ጋራጅ፤ ዩኒቨርሳል ፕላስቲክ ፋብሪካ፣ ናሽናል ሞተርስ፣ አምቦውሃ ፋብሪካና አምቼ ኢቪኮ በስፖንሰርነት እንደደገፉት አመልክቷል፡፡

Read 1218 times