Tuesday, 04 March 2014 10:58

የመንግስትን ቤት በማጭበርበር ወደ ራሳቸው አዛውረዋል የተባሉት ተከሰሱ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(5 votes)

ከ15 ዓመት በላይ እስር ሊያስቀጣቸው ይችላል

ከቀበሌው ሊቀመንበር ጋር በመመሳጠር ንብረትነቱ የመንግስት የሆነን ቤት፣ በህገወጥ መንገድ ወደ ራሱ አዛውሮ ሲጠቀም ተደርሶበታል የተባለው ግለሰብና ተባብረዋል በሚል የተጠረጠሩት የቀበሌው ሊቀመንበር ላይ ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከትናንት በስቲያ ክስ መሰረተባቸው፡፡
ሲኖሩበት የነበረውን የመንግስት ቤት ወደ ግል ይዞታቸው ለማዞር የተለያዩ የማታለያ ዘዴዎችን ተጠቅመዋል በተባሉት አቶ በዳሳ ጫልቺሳና ከ1989-99 ድረስ በዘለቀው የቀበሌ ሊቀመንበርነት ስልጣናቸው ተጠቅመው ቤቱ የመንግስት መሆኑን የሚያስረዱ መረጃዎች እንዲጠፉ አስደርገዋል በተባሉት አቶ መንግስቱ ኃ/ጊዮርጊስ ላይ የአታላይነት የሙስና ክስ መመስረቱን የአቃቤ ህግ የክስ ማመልከቻ ይጠቁማል፡፡ በማስረጃነትም 12 የሰው ምስክሮች እና 14 የሰነድ ማስረጃዎች ተቆጥረዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ እንዲቀርቡ ባስተላለፈው ትእዛዝ መሰረት፤ ከፍተኛ ፍ/ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡት አቶ በዳሳ፤ የዋስትና መብቴ ይከበርልኝና ጉዳዩን በውጭ ሆኜ ልከታተል ቢሉም አቃቤ ህግ በክስ ማመልከቻው የጠቀሰው የወንጀለኛ መቅጫ አንቀፅ፣ ከ15 ዓመት በላይ ሊያስቀጣ ስለሚችል ፍ/ቤቱ ጥያቄያቸውን ውድቅ በማድረግ ጉዳያቸውን በማረሚያ ቤት ሆነው እንዲከታተሉ ትእዛዝ አስተላልፏል፡፡
በእለቱ ያልቀረቡትን ሁለተኛ ተከሳሽ ኮሚሽኑ እንዲያቀርብ ያዘዘው ፍ/ቤቱ፤ መዝገቡን ለመጋቢት 4 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጥሯል፡፡

Read 2485 times