Saturday, 15 February 2014 13:24

የኮሪያውያን ቤተሰቦች ዕጣ ፈንታ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ኮሪያ እስከ ሁለተኛው የአለም ጦርነት ማብቂያ ድረስ የጃፓን ቅኝ ግዛት ነበረች፡፡ የሁለተኛው የአለም ጦርነት በጃፓን ሽንፈት ተጠናቀቀ፡፡ ሽንፈቷን ተከትሎ የጃፓን አገዛዝ በኮሪያ ላይ አበቃ፡፡ አሜሪካን ቻይና እና ታላቋ ብሪታኒያ የካይሮ ስምምነት በመባል የሚታወቀውን ሰነድ አፀደቁ፡፡ የኮሪያ ሰሜኑ ክፍል በሶቪየት ህብረት፤ ደቡብ ክፍል ደግሞ በአሜሪካን የሞግዚት አስተዳደር ስር እንዲቆይ የሚያደርገው ስምምነት ተግባራዊ ሆነ፡፡ ይህ ክፍፍል ዘላቂ ይሆናል ተብሎ የታሰበ ባይሆንም፣ የሁለተኛውን የአለም ጦርነት ማብቃት ተከትሎ አሸናፊዎቹ ሀይሎች የቀዝቃዛው ጦርነት ሰለባ የማድረግ ብቃት ስለነበራቸው የተከናወነ ነበር፡፡ የቀዝ
ቃዛው ጦርነት ሁለት ተቃራኒ ጎራዎች ቀደም ብለው የኮሪያን ሰሜንና ደቡብ በመከፋፋላቸው፣ ኮሪያውያን የቀዝቃዛው ጦርነት ማሟሟቂያ ሆኑ። በ1950 ሰሜን ኮሪያ በቻይናው ማኦ ዜዱንግ እና በስታሊን አለሁ ባይነት ደቡብ ኮሪያን ወረረች። ከሶስት አመት በኋላ በተደረሰ ስምምነት ጦርነቱ አብቅቶ፣ ሰሜን እና ደቡብ  ኮሪያ የሚለው  ክፍፍል ቋሚ ሆኖ ፀና፡፡ የስምምነቱ አካል በሆነው እና የኮሪያን ጉዳይ ለማየት በሚል የተጠራው የጄኔቫ ኮንፈረንስም ምንም እንኳን ከብዙ አገሮች የአንድነት አንጀንዳ ብልጫ እንዲያገኝ ቢሞከርም የኮሪያውያኑን አንድ ማድረግ ሳይችል ተበተነ፡፡
እጣፈንታቸው በሌሎች እንዲወሰን ግድ የሆነባቸው ኮሪያዎች፤ ደቡብ እና ሰሜን ተብለው ሲለያዩ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ዝምድና ከድንበር ጋር አብሮ እንዲቆራረጥ ሆነ፡፡ ሰሜን ኮሪያ እና ደቡብ ኮሪያ የሚገኙ የአንድ ቤተሰብ አባላትን የነጠለው ውሳኔ፣ ከሀያ ሁለት አመታት በኋላ ይፋ በተደረገ ሚስጥር መፍትሄ ያገኘ መሰለ፡፡ የሁለቱ አገሮች መሪዎች በድብቅ አንዱ የአንዱን ዋና ከተማ እንደጎበኙ እና ዋና የጉብኝቱ አላማም የሁለቱ ኮሪያዎች ሰላማዊ ውህደትን በመሻት የተከናወነ መሆኑን የሁለቱ ሀገር መሪዎች ገለፁ፡፡ የሰሜንና የደቡብ ኮሪያ የጋራ ስምምነት የተባለ ሰነድ መፈራረማቸውን አወጁ። ይሁን እንጂ፤ ይህን ያስፈፅማሉ በሚል ከሁለቱ አገሮች በተውጣጡ ልዑካን የተቋቋመው ኮሚቴ ያለምንም ውጤት ከአንድ አመት በኋላ ታገደ፡፡ በ1990 የሁለቱ ኮሪያዎች ጠቅላይ ሚኒስትሮች  ሲኦል ላይ ተገናኝተው የኮሪያውያንን አንድነት በተመለከተ ውሳኔዎችን ቢያስተላልፉም፣ ከኒኩሊየር ማበልፀጊያ ፖለቲካ ጉዳይ ጋር የተያያዘ ውዝግብ በመፍጠሩ ውጤት አልባ ሆነ፡፡ ከአመት በኋላ፤ እንደገና የሰሜን እና የደቡብ ኮሪያ የጋራ ስምምነትን የሚገልፅ ሰነድ አወጡ፡፡  የሰነዱ ዋነኛ አላማም፤ የሁለቱን ኮሪያዎች ሰላማዊ ውህደት የሚመለከት እንደሆነ አወጁ፡፡
የዚህ ውህደት እርምጃ በ2000 ተጀምሮ በ2007 በሰሜን ኮሪያ መንግስት ውሳኔ እንዲቆም የተደረገው ከሀምሳ አመታት በላይ የተለያዩ ቤተሰቦችን የማገናኘቱ ስራ ሰሞኑን እንደገና አገርሽቶ የመገናኛ ብዙሀን ትኩረት ሆኗል፡፡ ቤተሰቦችን ማገናኘቱ በሚቀጥለው ወር እንደሚጀመር ከስምምነት ላይ ተደርሶ የነበረ ቢሆንም ደቡብ ኮሪያ ከአሜሪካን ጋር በምታደርገው የፖለቲካ ወንድማማችነት ምክንያት ውሳኔዬን ልሰርዝ እችላለሁ ስትል ሰሜን ኮሪያ አስጠንቅቃለች፡፡
በተለያዩ የፖለቲካ ወገንተኞች ፍላጎት እና ውሳኔ፤ እንዲሁም ፅንፈኛ አቋም በያዙ መሪዎቻቸው እሰጥአገባ ሳቢያ የተነጣጠለ የቤተሰብ አባላትን የማገናኘቱ ፕሮግራም ለኮርያዊያኖች ከጥልቅ ስሜታቸው ጋር የተያያዘ ጉዳይ ነው፡፡ ቀን በሄደ እና እድሜ በገፋ ቁጥር በሞት መለየት ሊመጣ እንደሚችል ሲያስቡት ጉጉታቸው የበለጠ ይበረታል፡፡
የደቡብ ኮሪያ የቀይመስቀል ማህበር ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በ1988 ከቤተሰባቸው ጋር ለመቀላቀል ማመልከቻ ካስገቡ 127፣400 በሰሜን ኮሪያ የሚኖሩ ዜጐች ውስጥ አርባ ሺህ ያህሉ ቤተሰቦቻቸውን መቀላቀል ሳይችሉ ህይወታቸው ማለፉን ለማወቅ ተችሏል፡፡ እስከ አሁን 16ሺ 200 ኮሪያውያን በአካል፣ 3ሺ 740 የሚሆኑት ደግሞ በቪዲዮ ከቤተሰባቸው ጋር እንዲገናኙ ለማድረግ ተችሏል፡፡ ቤተሰቦችን የማገናኘቱ ፕሮግራም ከመጀመሩ በፊት ባሉት ቀደምት አመታት፣ ኮሪያውያኑ በያሉበት ከቤተሰቦቻቸው ጋር የፖስታ የስልክም ሆነ የኢሜይል መልእክት መለዋወጥ የማይችሉ ሲሆን ያለ መንግስት ፈቃድም ድንበር ማቋረጥ ተከልክለው ቆይተዋል፡፡
የ“ሁለቱ ኮሪያዎች ውህደት” የሚለው መፈክር ለዘለቄታው ተግባራዊ አይሆንም የሚሉ ወገኖች አሉ። ለዚህ ሀሳባቸው በመከራከሪያነት የሚያቀርቧቸውን ማሳመኛዎች አንድ ሁለት ብለው ይዘረዝራሉ፡፡ አንደኛ፤ ሁለቱ ኮሪያዎች በመለያየት ባሳለፏቸው አመታት ውስጥ ብዙ የተለያዩ ማንነቶችን አብቅለዋልና ይህ ልዩነት መቼም ወደ መታረቅ ሊመጣ አይችልም፤ ይላሉ፡፡
ሁለተኛ፤ ተለያይተውም በቆዩበት ብዙ አስርት አመታት የነበራቸው ግንኙነት እጅግ የሻከረ መሆኑ ለውህደት ባይሆንም … ቢያንስ በሁለቱ መሀል ያለውን ውጥረት ለማርገብ ሊያግዝ ይችል ይሆናል። ሶስተኛው፤ ከቤተሰቦቻቸው ጋር መቀላቀል የሚፈልጉት ኮሪያውያን እድሜ ሰባ እና ከዛ በላይ በመሆኑ፤ ኮሪያን አንድ በነበረች ጊዜ የሚያውቃት ትውልድ እየከሰመ በአዲስ ትውልድ በመተካቱ ምክንያት ነው፤ ብለው ማሳመኛዎቻቸውን ይተነትናሉ፡፡ የውህደት ጥያቄውም ልክ እንደ ትውልዱ እየከሰመ ይሄዳል፤ ውህደቱ ለቀድሞው ትውልድ እንጂ ለአዲሱ ትውልድ ትርጉም የሚሰጥ ሊሆን አይችልም ይላሉ፡፡
በቀዝቃዛው ጦርነት ምክንያት ሁለት አገር የሆኑት ኮሪያውያን፤ ሰሞኑን ደግሞ ደቡብ ኮሪያ ከአሜሪካን ጋር ወግናለች በሚል ምክንያት ከሀምሳ አመታት በላይ ከተለዩዋቸው ቤተሰቦቻቸው ጋር የመገናኘት ህልማቸው ጥያቄ ላይ ወድቋል፡፡

Read 4359 times