Saturday, 15 February 2014 12:52

ሙስና፤ “ሙሶ-ሎጂ” እና “ሙሶ-ሜትሪ”

Written by  ቤተማርያም ተሾመ betemariam2000@yahoo.co
Rate this item
(2 votes)

        የማህበረሰባችንን ወቅታዊ የሞራል ደረጃ ለመለካት አንድ ሀሳባዊ ቀመር እንቀምር፡፡ ይህንንም ቀመር “ሙሶ-ሎጂ” እንበለው፡፡ ይህንን ቀመር በማህበረሰብ ላይ ተፈጻሚ በማድረግ የሚገኘውን አህዛዊ ውጤት ደግሞ “ሙሶ-ሜትሪ” እንበለው፡፡
(ይህ ማለት ፡-አንድ በሙሶ-ሎጂ ቀመር የተጠና ማህበረሰብ የተገኘው አህዛዊ ውጤት  10 ሙሶ-ሜትሪ ፣0ሙሶ-ሜትሪ ወይም ኔጋቲቭ 5 ሙሶ-ሜትሪ ሲሆን እንደማለት ነው)፡፡
ሙሶ-ሎጂ የማህበረሰብን የሞራል ደረጃ ለመለካት እራሱን ሙስናን እንደ ግብአት ይጠቀማል፡፡ ከማህበረሰብ የሞራል ደረጃ ጥናቱ ጎን ለጎንም ሙስኖችንና  ሙሰኞችንም ለማህበረሰብ ከሚያበረክቱት አዎንታዊም ይሁን አሉታዊ ፋይዳቸው አንጻር በልዩ ልዩ ደረጃዎች ይከፋፍላል፣ ይተነትናል፡፡ በሙሶ- ሎጂ ትንታኔ መሰረትም ሙስና እንደ ሙሰኞች ከልማታዊ እስከ ጥፋታዊ ያሉትን ደረጃዎች ይይዛሉ፡፡ ልማታዊም ሆኑ ጥፋታዊ ሙሰኞች ከቅጣት እንደማይድኑ ልብ ይባልልኝ፡፡
የዚህ አጭር ፅሁፍ አላማ የማህበረሰባችንን የሞራል ደረጃ በሃሳባዊው የሙሶ-ሎጂ ቀመር በመፈተሽ ያለንበትን የሞራል ከፍታ አልያም ዝቅታ ለማየት ሲሆን እግረ መንገዳችንንም የሙስና አይነቶችን እና ባህርያትን ከልማት አልያም ከጥፋት ፋይዳቸው አንጻር በሙሶ-ሎጂ ጥበብ በመታገዝ እንመረምራለን፣ እንተነትናለን፡፡
የሙስና ባህሪያት እና ደረጃቸው
ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው በሙሶ-ሎጂ ጥበብ መሰረት ሙስና ሁሉ ሃጢያት፣ ሙሰኛ ሁሉ ውጉዝ አይደለም፡፡ ሙስና እና ሙሰኞችም ከልማታዊ እስከ ጥፋታዊ ባሉት እርከኖች ውስጥ ይመደባሉ፡፡ ይህንን ስንል በልማዳዊው የሞራል እና ግብረገብ ህግ መሰረት፣ ማንኛውም አይነት ሙስና ውጉዝ እና ፀረ- ልማት እንደሆነ ልብ ልንል ይገባል፡፡
“ልማታዊ ሙስና”
በሙሶ-ሎጂ ጥበብ መሰረት፣በተለያዩ እርከኖች ላይ ከሚገኙ ሙስናዎች መካከል ይህ የሙስና ደረጃ ለማህበረሰብ ከሚያበረክተው በጎ ውጤት አንጻር ሲመዘን አዎንታዊ (ፖዘቲቭ) ሙሶ-ሜትሪ ውጤትን ያሳያል፡፡
ይህንን ስንል በዚህ እርከን ላይ ያለ አንድ የሙስና ክስተት እና ተሳታፊ ሞሳሽ  ጥቅል ባህሪ በሙሶ-ሎጂ ቀመር ሲሰላ፣ የእለት ተእለት መስተጋብርን ከማሳለጥ፣ ፍትሃዊ የገንዘብ ሽግግርን (ኢ-መደበኛ ቢሆንም ) ከማፋጠን በዘለለ በሞሳሹ እና በተሞሳሹ ማህበረሰብ ላይ የሚፈጥረው ምንም አይነት አሉታዊ ተጽእኖ የለም፡፡ እንዲያውም መደበኛ በሆነው የሞራል ህግ ጭምር ሲመዘን ከመወገዝ ይልቅ ከእለት ተእለት እንቅስቃሴዎች እንደ አንዱ ሊፈረጅ ይችላል፡፡ ሞሳሹም ሆነ ሙስናው ውጉዝ እና እርኩሳን መሆናቸው ተዘንግቶ ለሂደቱ ይሁንታ እና ልዩ ልዩ ገንቢ ስሞች ተችረውት በብዛት ሲዘወተርና  አገልግሎትን ሲያሳልጥ ይስተዋላል፡፡
በዚህ ማእቀፍ ውስጥ የተካተቱ ሙስናዎች በሂደታቸው ማለትም ከጅማሬያቸው እስከ ፍጻሜያቸው ምንም አይነት ተጎጂ (ከሳሪ) የማህበረሰብ ክፍል የለም፡፡ ይልቁንም የየእለት መስተጋብርን በማሳለጥ በመደበኛው ህግ የተፈጠሩ ክፍተቶችን በመሙላት፣ ለልማታዊ ጉዞአችን ጠቃሚ እሴትን ይጨምራሉ፡፡ በዚህ የሙስና እርከን  ውስጥ የሚመደቡ ሙስናዎች እጅግ ብዙ ቢሆኑም የመንግስት አገልግሎት ሰጪ ተቋማትና  በየእርከኑ የተቀመጡ ፈጻሚዎች (የስራ ሂደቶች)፣ እየዳበረ በሄደው የግንባታ ዘርፍ ላይ ያሉ ልዩ ልዩ ባለሙያዎችና መሰል ተቋማት አይነተኛ ምሳሌዎች ናቸው፡፡
ምሳሌ እንጥቀስ፡- ሙስና እንደምን ልማታዊ ሆነ?
ወደ አንድ አንድ መንግስታዊ የአገልግሎት ሰጪ ተቋም ጉዳይ ኖሮን ሄድን እንበል፡፡ በ BPR አልያም በካዘይን ከተገነባው ተቋምና ከባለስልጣናቱ የምናገኘው መስተንግዶና  ትብብር ግን በኢቴቪ እንደምናየው አሊያም በአዲስ ዘመን እንደምናነበው ምቹ እና አልጋ በአልጋ ላይሆን ይችላል(አንዳንዴ ሊሆንም ይችላል)ጉዳያችንን ከውነን ወደ ስራችን በፍጥነት ለመመለስ ግን በሌላ የተሻለና  በሂደት በዳበረ ስውር ህግ ውስጥ ማለፍ ግድ ነው፡፡ በተለያየ እርከን ላይ ላሉ ሹሞች  ኪሳችንና  ዝምድናችን አንደፈቀደ የወጉን ልንል ግድ ይለናል፡፡
ለዚህ ሂደት ያወጣነውን መሞሰሻ ከአገኘነው ፈጣን ውጤት አንፃር ስንመዝነው፣ አትራፊ ከመሆናችን በተጨማሪ በስውር ከተዋቀረው የሙስና ማህበረሰብ አባላት ክብርን፣ባወጣነው መሞሰሻ ለጎንዮሽ  ተጠቃሚዎች መዋጮን እንቸራለን፤አገልግሎት እናሳልጣለን፤የገንዘብ ዝውውሩን ተደራሾች አድማስ በማስፋት የተከሰተውን የኑሮ ውድነት በመዋጋቱ እርብርብ ላይ የበኩላችንን በመወጣት በልማታዊው ሙስና ውስጥ ግንባር ቀደም ተዋናይ እንሆናለን ይለናል - ሙሶ-ሎጂ፤ ልማታዊ ሙስናን እና አዎንታዊ መስተጋብሩን በምሳሌ ሲያስረዳን፡፡
ማሳሰቢያ፡- “ልማታዊ ሙስናም” ቢሆን ከተጠያቂነት ነፃ አያወጣም፡፡
ጥፋታዊ  ሙስና
ይህ የሙስና ደረጃ ከልማታዊው ሙስና በተቃራኒው እረድፍ ላይ ሲገኝ በሙሶ-ሎጂም ይሁን በልማዳዊው የሞራል ህግ ሲመዘን ፍፁም አጥፊ፣ የማህበረሰብ ነቀርሳ እና ሲከፋም በዘመንኛ ስሙ “አሸባሪ ሙስና” ሊባል እና ሊፈረጅ ይችላል። በዚህ የሙስና እርከን እና ባህሪ ላይ የትኛውም የፖለቲካ፣ የእምነት አልያም የባህል አባል ምንም አይነት ልዩነት ሳይኖረው በእኩል ድምጽ ያወገዘው ፀረ-ልማት፣ኪራይ ሰብሳቢ፣ሃራም እና ውጉዝ ሲሆን ሙስናው እና ሞሳሹም የታዩበት የማህበረሰብ ክፍል ከሚደርስበት የልማት ሳንካ ይበልጥ እንደማህበረሰብ የመቆሙ ጉዳይ አደጋ ውስጥ ይወድቃል፡፡ በእኛው ሃሳባዊ ቀመር ሙሶ-ሎጂም ከዜሮ በታች ኔጌቲቭ ሙሶ- ሜትር ውጤት ያስመዘግባል፡፡
በሙሶ-ሎጂ ቀመር ትንተና መሰረት፣የአንድ ጥፋታዊ ሙስናና  በስሩ የሚዋቀረው ስውር የሙስና ሰንሰለት (ማህበረሰብ )የሚፈጠሩት በሁለት ዓይነት ሂደቶች ነው፡፡ እነርሱም፡-
ከየትኛውም እርከን ላይ ተነስተው የልማታዊ ሙስና ኡደታቸውን ጨርሰው ፍጹም አፍራሽ (ኢ-ልማታዊ) ወደሆነ የሙስና ደረጃ ከሚለወጡ አዳጊ የሙስና አይነቶች  እና፤
ከጅማሬያቸው እና ባህሪያቸው ፍጹም አጥፊ እና የነቀርሳ ባህሪን ከተላበሱ ሙስኖች  ነው፡፡
በጊዜ ሂደት ወደጥፋታዊ ሙስናነት የሚለወጡ ኡደታዊ ሙስኖች
 የእነዚህ የሙስና አይነቶች መነሻ በየትኛውም ሙስና እርከን ላይ ካሉ እና በእድገት ሂደታቸው ጫፍ ላይ ሲደርሱ ከጉዳት አልባነት አልያም ከልማታዊ ሙስናነት ጀምረው የልማት ሳንካ ከመሆን ባሻገር  ለማህበረሰብ ውድቀት ጉድጓድ ቆፋሪዎችና የሞራል ዝቅጠት አመላካቾች የሚሆኑ የሙስና አይነቶች ናቸው፡፡ እነዚህ የሙስና አይነቶች  በለውጥ ሂደታቸው ወቅት ለመሞሰሻ የተተመነው ገንዘብ አልያም ሌላ ተመጣጣኝ ክፍያ በፈጣን ሁኔታ ጭማሪን በማሳየትና በሙስናው አፈፃጸም ሰንሰለት ውስጥ ተሳታፊ አባላቱን በከፍተኛ ፍጥነት በማሳደግ እንዲሁም ተቋሙን በመውረር የተሞሳሹን ጥሪት እስከማሟጠጥ ይደርሳል፡፡ በአጭር ግዜ ውስጥም ስውር የሙስናው ህግጋቶች  የመንግስትና  የህግ አካላትን ትኩረት እስኪስቡ ድረስ በጠራራ ጸሃይ የሚፈፀሙና መደበኛውን አሰራር ተክተው የሚከወኑ የካንሰር ባህሪን የሚጋሩ ሙስና አይነቶች ናቸው፡፡
የእነዚህ ሙስኖች ሌላው አይነተኛ መገለጫቸው በሙስና ሰንሰለቱ ጫፍ ላይ ለሚገኙ ጥቂት ባለስልጣናት (ጉምቱ ሙሰኞች) ኪስ ማደለቢያነት በማገልገል የተቋሙን አገልግሎት እና የማህበረሰብ ተደራሽነት በማቀጨጭ እንዲሁም በነፃው የአገልግሎት ገበያ ላይ አርቲፊሻል የአገልግሎት እጥረትን በመፍጠር፣ የብዙሃን መጉላላትንና  ምሬትን በመከሰት፣ በእድገት ጅማሬያቸው ላይ ከነበራቸው ልማታዊ ባህርይ ወደ ጥፋታዊ ሙስናነት በፍጥነት ይመነደጋሉ ፤የሙሶ ሜትሪ ውጤታቸውም በፍጥነት ወደ ኔጌቲቭ  ያሽቆለቁላል፡፡
ሙስና፤ ሞራል እና ሙሶ-ሎጂ
   ከላይ እንደተመለከተው በሙሶ-ሎጂ ቀመር በመታገዝ  የሙስና አይነቶች እና ባህሪያቸው፤ ከልማት ጋር ያላቸውን መስተጋብር በወፍ በረር ለመቃኘት ተሞክሯል፡፡ በመቀጠልም ወደ አብይ ጉዳያችን እና የሙሶ-ሎጂ አንዱ እና ተወዳጅ ዘርፍ እናምራ፡፡ ይህ ዘርፍ የአንድ የተመረጠ ጥፋታዊ ሙስናን እና ፈጻሚ ሙሰኞችን  ባህሪ በማጥናት ሙስናውን እና ሞሳሹን  ስለቀፈቀፈው ማህበረሰብ የሞራል ደረጃ እንዲሁም የማህበረሰቡን መጻኢ እጣ ፈንታ የሚተነትን እና የሚተነብይ  የሙሶ-ሎጂ ንኡስ ዘርፍ ነው፡፡
በዚህ ቀመር መሰረት፣ የአንድ ጥፋታዊ ሙስና እና ተዋናይ ሞሳሽ የሞራል ዝቅጠት እንዲሁም ይህንን ሞሳሽ  ያፈራን ማህበረሰብ የሞራል ደረጃ እና የማህበረሰቡን እጣ ፈንታ ይተነትናል። ይህንንም ለማስላት አንድ የተመረጠ ጥፋታዊ ሙስና የተፈጸመበትን ግዜ (T1) እና የሙስናው አሉታዊ ውጤት የታየበትን ግዜ ደግሞ (T2) ብንላቸው በሁለቱ ሰአቶች መካከል ያለው የግዜ ልዩነት በጠበበ መጠን ማለትም (T1 - T2 ) ወደ ዜሮ በቀረበ መጠን የሙስናው ጥፋታዊነት (ሀ) እየጨመረ የሙሰኛው የሞራል ደረጃ (ለ) እየወረደ ይመጣል- ይለናል ሙሶሎጂ በዚህ ንኡስ ዘርፉ፡፡ ይህንን ጽንሰ ሃሳብ ወደ ሂሳባዊ ቀመር (ፎርሙላ ) በመለወጥ የተመረጡ እና በማህበረሰባችን ውስጥ የተከሰቱ ምሳሌ ሙስኖችን በዚህ ቀመር (ፎርሙላ ) በመፈተሸ አንድ ሙከራ እንስራ ፡፡
በመጀመሪያ ዋናውን ቀመር ከነባራዊ እውነታዎች እና ሂሳባዊ መሰረታውያን በመነሳት እናዋቅር፡፡
(ማሳሰቢያ፤- ለሂሳብ እና ሂሳብ ነክ ትምህርት ባለሙያዎች የዚህ ቀመር አመጣጥ ቀላል እና ግልጽ ሲሆን ለሂሳብ እና ቁጥር አለርጂኮች  ደግሞ ትንታኔውን መገንዘብ ብቻ በቂ ነው)
 ቀመር (ፎርሙላ) 1.–––––––––––
  ቀመር(ፎርሙላ) 2----------------------
በቀመር 1 ላይ እንደምንመለከተው የሙስናው የጥፋት መጠን (ሀ) እና በሙስናው ጥንስስ እና ፍጻሜ መሃል ያለው የግዜ እርዝመት (T1 - T2 )  ተገላቢጦሽ ተዛማጅ (inversely proportional) ሲሆኑ በቀመር ሁለት ላይ ደግሞ የሙሰኛው የሞራል ደረጃ (ለ) እና በሙስናው ጥንስስ እና ፍጻሜ መሃል የለው የግዜ እርዝማኔ (T1 - T2 ) መሳ ለመሳ ተዛማጅ  (directly proportional) ናቸው፡፡
ከላይ የተመለከቱትን ሁለት ቀመሮች በማዋሃድ ሌላ ከ (ሀ) እና ከ (ለ) አንፃር የተዋቀረ ሶስተኛ  
የሚል ቀመር እናገኛለን፡፡ ይህ ቀመር ደግሞ የሞሳሹ የሞራል ደረጃ (ለ) እና የሙስናው የጥፋት መጠን(ሀ) ተገላቢጦሽ ተዛምዶ እንዳላቸው ያሳየናል፡፡ ይህ እውነታ በቀላል አማርኛ ሲገለጽ  አንድ የሞራል ደረጃው እጅግ የወረደ ሙሰኛ  እጅግ ፈጣን እና ከባድ አጥፊ ሙስናን ያደርሳል በማለት እውነታውን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል ቀመር 3

እና ምን ይጠበስ ለሚሉ
ከላይ የተዘረዘሩትን ምሁራዊ ዲስኩሮች እና ሃሳባዊ ሂሳባዊ ቀመሮች  ለዩኒቨሪሲቲዎቻችን የማህበረሰብ ሳይንስ ምሁራን ቀጣይ ጥናት እንደመንደርደሪያ በመተው
(የሃሳቡ እና የቀመሮቹ ቀማሪ የባለቤትነት መብት እንደተጠበቀ ሆኖ)፣
አንዳንድ በእኛ ማህበረሰብ ውስጥ የተፈጸሙ አጥፊ ሙስኖችን በቀመርነው ቀመር በመታገዝ፣ የማህበረሰባችንን የሞራል ዝቅጠት፤ የአንዳንድ ሙስኖችን ከክፋታዊ ሙስናነት የዘለለ የከባድ ውንብድና ጫን ሲልም የዘር ማጥፋት ወንጀልነት ባህሪን ከሙሶ-ሜትሪ ውጤታቸው በግልጽ ለመመልከት ነው፡፡
ምሳሌ 1- በፍትህ ተቋማት የሚፈጸሙ ሙስኖች፤-
የእነዚህ የሙስና አይነቶች ውጤት በሞሳሹ ላይ በፍጥነት በመፈጸም፣ ህግን በማጣመም ተበዳይን ለከፋ እንግልትና ፍትህ እጦት ሲዳርጉ፣ የሚከወኑትም የሞራል ደረጃቸው በወረደና  የፍትህ እጦት በማይገዳቸው ምግባረ ብልሹ ሙሰኞች ነው።

ምሳሌ -2
በህክምና ተቋማት የሚፈጸሙ ሙስኖች፤- የእነዚህ ሙስኖች የሙስና ውጤት በአጭር ግዜ ውስጥ በህክምን ፈላጊው (ተሞሳሹ) ላይ የሚታይ ሲሆን በውጤታቸውም የከፋ የጤና መቃወስንና ፈውስ ማጣትን በተሞሳሹ ላይ ያስከትላሉ፡፡
ፈጻሚዎቹም በሰው ጤናና  ህይወት ላይ ቁማር በመጫወት ቢዝነስ የሚያጧጡፉ የሞራል ደረጃቸው በምሳሌ 1 ከተጠቀሱት ሞሳሾች እጅግ የወረደ እና የሙስናቸው አሉታዊ ውጤትም እጅግ የፈጠነ ብልሹዎች ናቸው፡፡

ምሳሌ 3- ይህ የሙስና አይነት ልዩ እና ምናልባትም በኢትዮጵያውያን ሙሰኞች ብቻ በኢትጵያውያን ላይ የሚፈፀም የማህበረሰባችን የሞራል ዝቅጠት ዓይነተኛ ማሳያ ሲሆን ሙስናው የሚፈጸመው ምግብ እና የምግብ ውጤቶችን ጥራት ሆን ብሎ በማጓደል ፤ ባእድ እና መርዛማ ነገሮችን ቀይጦ በመሸጥ ወገንን እና   የገዛ ቤተሰብን በመመረዝ፣ ገንዘብ ለማካበት በሚደፍሩ ሞራለ-ዝቃጭ ሙሰኞች (አሸባሪዎች) ነው፡፡  ይሄ የሙስና ዓይነት ጸያፍ እና ውጤቱም በፍጥነት የሚታይ ነው።  

ምሳሌ 4- ይህ የሙስና አይነት በሌሎች የማህበረሰብ ክፍሎች እንዲሁም በሰብአዊ ፍጡርና  በሰብአዊ ታሪክ መፈጸሙን እርግጠኛ አይደለንም። የሙስናው  ወንጀል የሚፈጸመው (በእርግጠኛነት መፈጸሙ በማስረጃ ባይደገፍም) የእሳት አደጋ በተነሳበት አካባቢ  ሲሆን ሙሰኞቹም የእሳት አደጋ አጥፊ አባላት ናቸው፡፡
ተሞሳሹ ደግሞ ንብረቱ፣ ልጁ አልያም ሌላ የቅርብ ቤተሰቡ በሚንተገተገው ሰደድ የተከበበበት እና በጣር የተያዘ ግለሰብ ነው፡፡
(ማሳሰቢያ፤-የዚህ የሙስና አይነት ሲፈጸም በአይኔ ያልተመለከትኩ ቢሆንም የሙያውን ስነምግባር የተላበሱና  ህይወታቸውን መስዋእት እስከማድረግ የሚተጉ ምስጉን አባላትን ግን ተመልክቻለሁ)
ከላይ በምሳሌው የተገለጹት  ሙስኖች እና ሞሳሾች ከማህበረሰብ ጠንቅነታቸውና ከፈጻሚያቸው  የሞራል ደረጃ እንዲሁም በሚያስመዘግቡት የሙሶ-ሜትሪ ውጤታቸው አንጻር በቅደም ተከተል ከላይ ወደታች ለማስቀመጥ ከሙስናው ጅማሬ እና በሙስናው ውጤት መሃል ያለውን የግዜ እርዝማኔ
(T1 - T2 ) እንደማወዳደሪያ የተጠቀምን ሲሆን ፤የዚህ የግዜ እርዝማኔ አሽቆልቁሎ በሰደድ እሳት ተከቦ የሽራፊ ሰኮንድ እድሜን በሚጠብቅ ምስኪን ጨቅላ ህጻን እና ሊውጠው በሚወነጨፍ ሰደድ እሳት መሃል በቀረች የእድሜ ቅጽበት መሃል ከሚከወን የሙስና ደረጃ ላይ እንዲሁም ይህንን አጋጣሚ እንደ መልካም የቢዝነስ እድል ለመቁጠር በቂ የሞራል ዝቅጠት ካለው ሙሰኛ ዜጋ ላይ ደርሰናል፡፡
ይህንን ሙስና ለመፈጸም የሚያስችል የሞራል ዝቅጠት ባለቤት የሆነ ሙሰኛና ይህ እንዲሆን ኮትኩቶ ያሳደገ ማህበረሰብ ስንተ ሙሶ-ሜትር ይመዝናል? በዚህ ደረጃ ካለ የሞራል ዝቅጠት ጋርስ እንደ ማህበረሰብ እና ሃገር ምን ያህል እርቀት እንጓዛለን?


Read 3215 times