የፓርቲው የሦስት አመት ሪፖርት ለጉባኤተኞቹ እንደሚቀርብ የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ግርማ ሰይፉ ጠቅሰው፤ ተሻሽለው የተዘጋጁ የህገ ደንብ እና የፕሮግራም ሰነዶች በጠቅላላ ጉባኤው ውሳኔ ይሰጥባቸዋል ብለዋል፡፡ በእስር ላይ በሚገኙት አቶ አንዱአለም አራጌ ምትክ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ የሆኑት አቶ ግርማ ሰይፉ፤ በፓርላማ ውስጥ ብቸኛው የተቃዋሚ ፓርቲ አባል ናቸው፡፡
በሁለተኛው ጉባኤ ቀን፤ የፓርቲውን ፕሬዚዳንትና የከፍተኛ የስራ አመራሮች እንደሚመረጡ የተናገሩት አቶ ግርማ፤ መመረጥ የሚፈልጉ ሰዎችን በማወዳደር ጉባኤተኞቹ የፓርቲውን አመራር ይመርጣሉ ብለዋል፡፡
በእስር ላይ የሚገኙ የፓርቲው አመራር አባላትን በተመለከተ አቶ ግርማ ተጠይቀው፤ በፍ/ቤት እስካልተወሰነባቸው ድረስ በህግ በተደነገገው መሰረት ንፁህነታቸውን እንደተቀበልን እንቀጥላለን ብለዋል፡፡
ጥፋተኝነቱ በፍ/ቤት ያልተረጋገጠበት ሰው ንፁህነቱ ሊከበርለት እንደሚገባ በመጠቆምም፤ በእስር ላይ ቢሆኑም የፓርቲው አባላት ናቸው ያሉት አቶ ግርማ፤ በፓርቲው ውስጥ የነበራቸውን ስራ ተክተው በሚሰሩ አባላት እንደሚከናወን ገልፀዋል፡፡
በእስር ላይ ያሉት የፓርቲው አባላት ቤተሰቦች እንዳይቸገሩ በማለት ድጋፍ እንደሚያደርጉላቸው አቶ ግርማ ጨምረው ተናግረዋል፡፡
አንድነት ፓርቲን ጨምሮ በመድረክ ውስጥ ጥምረት የፈጠሩ ፓርቲዎች፤ ወደ ግንባር ለመሸጋገር መወሰናቸውን በማስታወስ፤ ስምምነቱ ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቦ ውሳኔ እንደሚያገኝ አቶ ግርማ ገልፀዋል፡፡
አንድነት ፓርቲ ከብርሃን ፓርቲ ጋር ውህደት ለመፍጠር መወሰናቸውም የሚታወቅ ሲሆን፤ እሁድ እለት በሚካሄደው የአመራር ምርጫም የሁለቱ ፓርቲዎች አባላትና መሪዎች ይሳተፋሉ ብለዋል - አቶ ግርማ፡፡
ዶ/ር ነጋሶ፣ ዶ/ር ንጋት እና ኢ/ር ዘለቀ ለፕሬዚዳንትነት ለመመረጥ ይወዳደራሉ፡፡ ከዚህ ቀደም በነበረው የአሰራር ደንብ፤ በጠቅላላ ጉባኤም አማካኝነት የአመራር ምክር ቤት አባላት ለተመረጡ በኋላ የምክር ቤቱ አባላት ደግሞ ፕሬዚዳንት ይመርጡ ነበር፡፡
አሁን ግን ጠቅላላ ጉባኤው በቀጥታ ፕሬዚዳንቱን ይመርጣል ብለዋል - አቶ ግርማ፡፡