Monday, 10 February 2014 07:12

“ልማድ ሲሰለጥን ተፈጥሮ ይሆናል” ሼክስፒር

Written by 
Rate this item
(6 votes)

ጥንት ዱሮ አያ ቋቴ የሚባሉ ብልህ ሰው ነበሩ ይባላል፡፡ የአያ ቋቴ መታወቂያ ሰው እህል ለመዝራት ገና መሬቱን ሳያለሰልስ እሳቸው እርሻ መጀመራቸው ነው፡፡
“አያ ቋቴ?” ይላቸዋል አንዱ፡፡
“አቤት” ይላሉ
“ምነው እንዲህ ተጣደፉ? በጊዜ እርሻ ጀመሩ?”
“በጊዜ ቋቴን (የዱቄት እቃዬን) ልሞላ ነዋ” ይላሉ፡፡
“መሬቱ የት ይሄድቦታል? ቀስ ብለው አያርሱትም ታዲያ?”
“አርሼውስ የት ይሄድብኛል? ብዘራበትስ መች እምቢ ይላል?”
አያ ቋቴ በጊዜ በማለዳ እየተጣደፉ ሄደው አዝመራቸውን ሲሰበስቡ፤ ገና ያልዘሩ ሰዎች፤
    “አያ ቋቴ?”
    “አቤት”
“አሁን አዝመራው የት ይሄድብዎታል? እንዲህ ሰማይ ዐይኑን ሳይገልጥ እየሮጡ የሚሄዱት?”
“ፈጥኖ የደረሰ እህል አንድም ለወፍ አንድም ለወናፍ ነው፡፡ በጊዜ እጅ የገባ ነገር ጥሩ ነው፡፡ ቋቴ በጊዜ ሞልቶ ቢገኝ ምን ይጎዳኛል?” ይላሉ፡፡  
ቆይተው እየተጣደፉ ሊያስፈጩ እህል በአህያ ጭነው ሲሄዱ ሰዎች ያገኙዋቸዋል፡፡
    “አያ ቋቴ?”
    “አቤት”
    “ወዴት ነው እንዲህ እየተጣደፉ የሚሄዱት?”
    “ወደ ወፍጮ ቤት”
    “እንዲህ በጠዋት፣ እንዲህ እየሮጡ?”
    “አዎን እንዲህ በጠዋት፣ እንዲህ እየሮጥሁ”
    “ምነው ጦር መጣ እንዴ? ፀሐይ ሞቅ ሲል ቀስ ብለው አይሄዱም?”
    “ለቋቴ፡፡ ቋቴ በጊዜ እንዲሞላ ነዋ!”
አያ ቋቴ እህላቸውን አስፈጭተው ማጠራቀሚያ ቋታቸው ውስጥ ከትተው እያስጋገሩ ሲበሉ፣ ሰዉ ገና እርሻ ላይ ወዲያ ወዲህ ይላል፤ በማህል አንዱ ይመጣና
    “አያ ቋቴ?”
    “አቤት”
    “የምንበላው አጣን እባክዎ ዱ    ቄት ያበድሩን”
ሌላው አዛውንት ይመጡና፤
    “የእገሌ ቤተሰብ በረሀብ ሊያልቅ ነው እባክዎ ትንሽ ዱቄት ካለዎት?”
ቀጥሎ የእድሩ ዳኛ ይመጡና፤
“አያ ቋቴ”
    “አቤት”
“እባክዎ የእገሌ ልጅ ሞቶ ለቀስተኛውን እምናበላው አጣን፤ እንደሚያውቁት እህል አልደረሰልንም?”
አያ ቋቴም አይ ያገሬ ሰዎች፤ “ለልመና ሲሆን ሰው ሳይቀድማችሁ ትነሳላችሁ፡፡ እኔ ለቋቴ ማለዳ ስነሳ ታሾፋላችሁ! መቼ ነው ጊዜ ቋት መሆኑ የሚገባችሁ?” አሉ ይባላል፡፡
    *     *     *
ከአያ ቋቴ የምንማረው ለዓላማችን ስንል በጠዋት መነሳትን ነው፡፡ አስቀድሞ መዘጋጀትን ነው፡፡ በጊዜ መሰነቅን ነው፡፡ በጊዜ መክተትን ነው፡፡ ጊዜ የትግል ቋት ነው፡፡ “ጊዜ የስልጣን እጅ ነው” ይላሉ አበው፡፡ ሰው ሳይቀድመን ለልመና ከመነሳት ይሰውረን፡፡
ገጣሚው ራልፍ ኤመርሰን “አልኮል፣ ሐሺሽ፣ ፕሩሲክ አሲድ፣ ካናየን ደካማ ሱሶች ናቸው፡፡ ዋና መርዘኛ ዕፅ ጊዜ ነው” ይለናል፡፡
“የሰዓቱ እጀታ ከምናስበው በላይ እየተንቀረፈፈ ነው፡፡ ረፍዶብናል!” የሚሉት መዝሙር አላቸው ቦሄማውያን፡፡ መርፈዱን መገንዘቢያችን ደቂቃ ወይም ሰከንድ ላይ ነን፡፡ በወሬ የምንፈታው ጦር የለም። በወሬ የምንፈታው ዳገት የለም፡፡ ሁሉ ነገር ሥራ ይፈልጋል፡፡ ነገን ዛሬ እንሻማው፡፡ “ዛሬ ላይ ሆነን ከነገ መስረቅ ነው (Plagiarizing the future)” እንደተባለው ነው፡፡
ዛሬ፤ የለመድነውን ይዘን ከመቀጠል ሌላ የአስተሳሰብ ለውጥ ሽታው ጠፍቷል፡፡ ዕውቅናና ገንዘብ የማሰባሰቢያውን ማሺን እጁ ያስገባ ሰው የሚነግስበት ዘመን ሆኗል! ይሄንን ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ብለን እየተጓዝን ነው፡፡ ሆኖም ፓርቲ እየዘቀጠ ሲሄድ ባለፀጋ መሆን (Fattening) ይበረክታል፡፡ ዝነኛ መሆን ግብ ይሆናል፡፡ ቲፎዞ በመሰብሰብ የሚመራ መሪ ባዶ ገረወይና ነው፤ እንደሚባለው ዓይነት ነገር ይዘወተራል፡፡ ይለመዳል፡፡ ዲሞክራሲ ይህ ከሆነ ዲሞክራሲ ራሱ ገና ዲሞክራሲያዊ መሆን ያስፈልገዋል። (Let’s Democratize Democracy-Fareed Zekaria)
ለማስመሰል በማይሆን ተስፋ መፅናናት ብዙዎቻችንን ላልተጨበጠ መንገድ ይዳርገናል፡፡ አስተሳሰባችን አሜሪካዊው ድራማቲስት ብሩክ አትኪንሰን “አንድ ቀን በፀሐይ ዙሪያ” በሚለው ፅሑፍ ተስፈኝነትን ሲገልፅ፤ ካለው ጋር የሚሄድ ነው፡፡ “አንዳች ተዓምራዊ-ሚሥጥራዊ መንገድ ፍቅር ሁሉንም ድል ይመታል፣ መልካሙ ነገር መጥፎውን በሁለንተናዊው ዓለም ሚዛን መሰረት ይረታል፤ እናም በ11ኛው ሰዓት ክፉ ነገር በእኛ ላይ ከመምጣቱ በፊት አንዳች ገናናና ታላቅ ኃይል ያቆመዋል፤ ይከለክልልናል!” ከዚህ ቢሰውረንና ለመስራት ብንነሳ፣ ለመደራጀት ብንዘጋጅ፣ ውጣ ውረዳችንን ከወዲሁ በተጨባጭ ልንበግረው ብንጣጣር ይሻላል፡፡ ልባችን ዘውድ ለመጫን ያስብ እንጂ እጃችን አፈር አልጨበጠም፡፡
የተለመደ መፈክር፣ የተለመደ የአፍ ወረርሺኝ፣ የተለመደ ከላይ ወደታች ትዕዛዝ፣ የተለመደ ዝቅጠት፣ የተለመደ በሙስና ወደ ሀብት ጉዞ፤ ተፈጥሮ የሰጠን ይመስል ተቀብለነው የምንኖር ልማድ ሆኗል። መብራት ሲጠፋ ለመድነው፡፡ ውሃ ሲጠፋ ለመድን፡፡ ስልክ መስመር ሲጠፋ ለመድን፡፡ ኑሮ ሲከፋ ለመድን፡፡ ይሄንኑ ማማረርንም ለመድን… በመልመድ ተሞላን፡፡
ዛሬ በአገራችን ኢ-ሜይል ሳይሆን “ስኔይል” ተሽሏል እየተባለ ነው፡፡ ከኢሜይል ይልቅ የቀንድ-አውጣ ጉዞ ይሻላል እንደ ማለት ነው፡፡ በአጠቃላይ አነጋገር እየተንቀረፈፍን ነው፡፡ የቴሌ ሥርዓት ዋናው አንቀርፋፊያችን ነው እተባለ ነው፡፡ በእንሰቅርት ላይ ጆሮ ደግፋችን መዓት ነው!
Death and taxes and childbirth! There’s never any convenient time for any of them!
የ “ነገም ሌላ ቀን ነው” ደራሲ ማርጋሬት ሚሼል “ሞት፣ ቀረጥ እና ልጅ-መውለድ ምኔም ምቹ ጊዜ ኖሮት አያውቅም” ትላለች፡፡ ምጡ ከደረሰ ማሰቃየቱ አይቀርም ነው፡፡ ሦስቱ አንድ ላይ ሲመጣማ የመርገምት ሁሉ መርገምት ነው፡፡
በ11ኛው ሰዓት ይላሉ ፈረንጆች፡፡ አዬ፤ አማርኛ ቢያውቁ “ሰርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ” ይሉ ነበረ። ይሄንን ክፉኛ ለምደናል፡፡ ዕዳ የምንከፍለው በ11ኛው ሰዓት ነው፡፡ ስልክ የምንከፍለው በ11ኛው ሰዓት ነው። (ስልክ ባይኖርም)!! መብራት የምንከፍለው በ11ኛው ሰዓት (ውሃው ባይኖርም)!! ለፈተና የምናጠናው በ11ኛው ሰዓት (ትምህርት ቢደክምም ባይደክምም)!! ወደ ሐኪም የምንሄደው በ11ኛው ሰዓት!! (ቢጭበረበርም ባይጭበረበርም)!! ይሄን ልማድ ካልተውን መቼም ህይወትን አንረታም፤ ባላንጣችንንም ተፎካካሪያችንንም አናሸንፍም!!
ሼክስፒር በፀጋዬ ገ/መድህን ብዕር፤
“ዛሬ ለወግ ያደረግሺው፣ ወይ ለነገ ይለምድብሻል
ልማድ ፊት እንዳሳዩት ነው፣ ወይ ይጠፋል ወይ ያጠፋል
ከርሞም የሰለጠነ እንደሁ፣ ተፈጥሮ ይሆናል ይባላል”፡፡ የሚለን ለዚህ ነው፡፡”    

Read 6500 times