Monday, 10 February 2014 07:04

መድረክ በአረና አባላት ላይ የተፈፀመውን ወንጀል አወግዛለሁ አለ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(8 votes)

             የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ሰሞኑን በሰላማዊ መንገድ ሲንቀሳቀሱ በነበሩት የአረና ትግራይ ለዴሞክራሲና ሉአላዊነት ፓርቲ አባላት ላይ የተፈፀመውን ወንጀል አጥብቆ እንደሚያወግዘው አስታወቀ፡፡
መድረክ በትላንትናው ዕለት “በሰላማዊ አግባብ ሲንቀሳቀሱ በነበሩት የአረና ትግራይ ለዴሞክራሲና ለሉአላዊነት አባላት ላይ የተፈፀሙት ወንጀሎች የሀገራችንን ፖለቲካ ከድጡ ወደ ማጡ የሚከቱ ስለሆነ አጥብቀን እናወግዛለን” በሚል ባወጣው መግለጫ፣ ሰሞኑን በትግራይ ክልላዊ መንግስት የተለያዩ ዞኖች የፓርቲውን አላማና ፕሮግራም በማስተዋወቅ ላይ የነበሩትን የአረና አባላት ገዢው ፓርቲ በተደራጁ ወንጀል ፈፃሚ ቡድኖች ድብደባ እንዲፈፀምባቸው በማድረግ ጥር 18 ቀን 2006 ዓ.ም በአዲግራት ከተማ ሊካሄድ የነበረውን ስብሰባ ማደናቀፉ እጅግ እንዳሳዘነው ገልዷል፡፡
ፓርቲው ህጋው እውቅና ያለውና በህጋዊ አግባብ የሚንቀሳቀስ መሆኑን የገለፀው መድረክ፤ በህጋዊ መንገድ ሲንቀሳቀሱ የነበሩትን የፓርቲውን አባላት በተደራጀ ወንጀል ፈፃሚዎች ማስደብደብና ህዝባዊ ስብሰባን ማደናቀፍ የአገራችን ፖለቲካ ወደ ቁልቁለት እየተንደረደረ መሆኑን ማሳያ ነው በማለት አጥብቆ እንደሚያወግዘው ገልጿል፡፡
“እስከ ዛሬ ድረስ በተለያዩ የአገሪቱ ክልሎችና ከተሞች መድረክና አባል ድርጅቶቹ ለማካሄድ ያቀዷቸውን ህዝባዊ ስብሰባዎች በተለያዩ ማስፈራሪያዎችና የቢሮክራሲ ማደናቀፊያ ስልቶች ኢህአዴግ ሲያስተጓጉል ቆይቷል” ያለው መድረክ፤ አፍራሽና ህገ-ወጥ ስልቱን በማባባስ በአዲግራት ከተማ ለህዝባዊ ስብሰባ ቅስቀሳ ለማድረግ በተሰማሩ የአረና/መድረክ አባላት ላይ ድብደባ እንዲፈፀምና የአካል ጉዳት እንዲደርስ ማድረጉ እንዳሳዘነው ገልዷል፡፡ “ጉዳዩን ይበልጥ የከፋ የሚያደርገው በአረና/በመድረክ አባላት ላይ ድብደባው የተፈፀመው ህግ አስከባሪ ፖሊሶችና የአካባቢው አስተዳደሮች ባሉበት መሆኑ ነው” ካለ በኋላ፤ በድብደባው አካል ጉዳት ከመድረሱም በላይ እንደ አቶ አሰግድ ገ/ሥላሴና አቶ አብርሃ ደስታ ያሉ የፓርቲውን ከፍተኛ አመራሮች በማሳሰር የስብሰባ እቅዱ እንዲደናቀፍ ኢ-ህገ-መንግስታዊ የሆነ አፈናውን በግልፅ መቀጠሉ ለኢትዮጵያ ህዝብ በተለይም ለትግራይ ህዝብ በፅናት ታግያለው የሚለውን የህውሀት.ኢህአዴግን ማንነት በግልፅ ያሳያል ብሏል መድረክ፡፡ በቅርቡ በአረና አባላት ላይ የተፈፀመው ወንጀልም የሰላማዊ ትግሉን በር የሚዘጋና ኢትዮጵያን ወደ አስከፊ የጦርነት አዙሪት የሚገፋ በመሆኑ አጥብቆ እንደሚያወግዘው ገልፆ፣ “ህዝቡም ይህን ፀረ-ሰላምና ፀረ-ዲሞክራሲ የኢህአዴግ ድርጊት እንዲያወግዝ ጥሪ አስተላልፋለሁ” ብሏል፡፡

Read 1678 times