Print this page
Monday, 27 January 2014 08:20

ከጎንደር ከተማ ከንቲባ ጋር - በጥምቀት ማግስት

Written by 
Rate this item
(2 votes)

የቻይና አምባሳደር ሞባይላቸውን ስለመሰረቃቸው ምን ይላሉ ?  
በጥምቀት በዓል በስርቆት ላይ ከተሰማሩት መካከል 26ቱ ተይዘዋል
 የጽዳት ችግር እንዳለ አምነዋል፣ “ከተማዋን  ጽዱ ለማድረግ እየሰራን ነው”
በየአዝማሪው ቤት በህፃናት ማስታወቂያ የሚያሰሩ ቢራ ፋብሪካዎችን ወቅሰዋል   

አቶ ጌትነት አማረ ይባላሉ፡፡ የጐንደር ከተማ ከንቲባ ናቸው፡፡ ባለፈው ዓመት በምርጫ ተወዳድረው ከንቲባ ከመሆናቸው በፊት ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ  በምክትል ከንቲባነትና በተቀዳሚ ምክትል ከንቲባነት አገልግለዋል፡፡ በቢዝነስ አድሚንስትሬሽንና በዴቨሎፕመንት ማኔጅመንት ሁለት ዲግሪዎች ያገኙት ከንቲባው በኧርባን ማኔጅመንት ደግሞ የማስተርስ ድግሪያቸውን ተቀብለዋል፡፡ ባለፈው ሳምንት ለጥምቀት በዓል ወደ ጎንደር የሄደችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፣ የከተማዋን ከንቲባ አቶ ጌትነት አማረን በቢሮቸው አግኝታ በተለያዩ የከተማዋ ጉዳዮች ላይ አነጋግራቸዋለች፡፡  

ጐንደር  ባሏት ታሪካዊ  ቅርሶች የተነሳ በአለም አቀፍና በአገር ውስጥ ቱሪስቶች በየጊዜው የምትጎበኝ ከተማ ናት፡፡  ከተማዋና ህዝቧ ከቱሪዝም ምን ያህል ተጠቃሚ ሆነዋል ይላሉ?
እንዳልሽው በየጊዜው በቅርሶቿ ከመጐብኘቷም ባሻገር በወርሀ ጥር፣ ጥምቀት በድምቀት የሚከበርባት ከተማ ናት፡፡ በመሆኑም ህዝቡን የኢኮኖሚ ተጠቃሚ ከማድረግና የከተማዋን ገጽታ ከመገንባት ባለፈ የአገር ውስጥና የውጭው አለም ጐበኚዎችን የቆይታ ጊዜ ለማራዘም በማሰብ፣ ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ የባህል ፌስቲቫል እያዘጋጀን ቆይተናል፡፡ በነዚህ ፌስቲቫሎች አገራችንን በደንብ ማስተዋወቅና የቱሪስቶችን ቁጥርም መጨመር ተችሏል፡፡ የቱሪስቶች የቆይታ ጊዜያቸውም አንፃራዊ በሆነ መልኩ እየጨመረ መጥቷል፡፡ ሰሞኑን አይተሽ ከሆነ----አዳዲስ ሆቴሎች፣ ሎጆች፣ የባህል ምሽት ቤቶች እየተገነቡና እየተከፈቱ ቢሆንም አሁንም በቂ አይደለም፣ አሁን ባለው ሁኔታ አልጋ በቀላሉ ማግኘት አይቻልም፡፡ የቱሪስት ቁጥር መጨመር፣ የቆይታ ጊዜው መራዘምና መሰል ነገሮች ለከተማዋም ሆነ ለነዋሪዎቿ ተጠቃሚነት መጨመር ጉልህ ሚና አላቸው፡፡ ለምሳሌ የታክሲና የባጃጅ ሹፌሮች ሰፊ ስራ ያገኛሉ፣ ባለሆቴሎች በምግብና በመኝታ በኩል ተጠቃሚ ናቸው፤ የባህል ቡና የሚያፈሉት፣ አዝማሪ ቤቶች፣ ሊስትሮ ሳይቀር-- የገቢ መጠኑ ይጨምራል። የስጦታ እቃ ሻጮች፣ ባህላዊ አልባሳትና ቁሳቁስ አምራቾችም እንዲሁ ተጠቃሚ ይሆናሉ፡፡ ባለሀብቱ ሎጅና ትልልቅ ሆቴል ለመገንባት ፍላጐት እያሳየ በመሆኑ ለነዋሪው የስራ እድል በመፍጠርም ሚናው የጐላ ነው፡፡
ሰሞኑን በከተማዋ ሶስት በዓላት (ዝግጅቶች) ነበሩ፡፡ አንዱ አመታዊው “አገር አቀፍ” የባህል ፌስቲቫል ሲሆን ሁለተኛው “ኢትዮጵያን በጐንደር” የተሰኘ አመታዊ ካርኒቫል ነው ሶስተኛው ጥምቀት፡፡ በዓላት እንዲህ ሲደራረቡ ለጐብኚዎች የሚደረገውን መስተንግዶ ጥራት አይቀንሰውም ?
አንደኛው በዓል በቅንጅት የተከበረ ነው፡፡ በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ በብሔራዊ የባህል ማዕከልና በጐንደር ከተማ አስተዳደርና ባህል ቱሪዝም መምሪያ ማለት ነው፡፡ እኛ ይህንን በዓል ስናከብር አንደኛ የባህል ፌስቲቫሉ ሲከበር ነበር። እኛ ከዚያ ቀደም ብለን “ኢትዮጵያን በጐንደርን” ስናከብር ቆይተናል፡፡ ዘንድሮ ለየት የሚያደርገው አንድ አይነት አላማ የያዘ በመሆኑና ከቀድሞው ትንሽ የእንግዳ ቁጥር መጨመሩ ነው፡፡ ሌላው ልዩነት ዘንድሮ ከዘጠኙ ክልል እና ከሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች ሰዎች መጥተው የእንግዳውን ቁጥር በተወሰነ መጠን ጨምረውት ነበር፣ እግዚቢሽንም ነበር፣ ከዚያ በፊትም ባዛር ነበረ፡፡ ባዛሩ “አዘዞ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት” ለመገንባት የተዘጋጀ ነበር፡፡ እንዳልሽው በዓሉ ተደራራቢ ነው፤ አዎ ይሄ እርግጥ ነው፡፡ ነገር ግን የባህል ማዕከሉና የእኛ ከተማ አስተዳደር ያዘጋጀው በዓል በአብዛኛው ተመሳሳይ ነው፡፡ ቀጥሎ ጥምቀቱ ነው፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ፍላጐት ምንድነው--- የቱሪስቱ ቁጥርም ሆነ የከተማ አስተዳደሩ ቁጥር እንደሚጨምር ነው፡፡ በሌላው ዓለም ለምሳሌ ብራዚልን ብትወስጂ--- በሚዲያ እንደምንሰማው በዓመት አንዴ ለሳምንታት የሚያከብሩት ፌስቲቫል በዓመት ውስጥ የማይሰበስቡትን ገቢ ያገኙበታል፡፡ አላማውም ይሄው ነው፡፡
ሌላው አለም ምናልባትም በቂና የተደራጀ  የመስተንግዶ አገልግሎት የተሟላ ስለሚሆን በርካታ እንግዳ ቢጠራም  ተደራራቢ በዓላት ቢያዘጋጅም ችግር ላይገጥመው ይችላል፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አዳጊ አገራት ግን የምንገነባውን ገጽታ እንዳናፈርሰው የሚያሰጋ ይመስለኛል ----
የሆስፒታሊቲውን ሁኔታ በተመለከተ አንዱና ዋነኛው ነገር፣ በባህልና ቱሪዝም በኩል አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን በስልጠና ማገዝ፣ ሁለተኛ ሰርቪሱን መጨመር ከተቻለ ለጐንደር ከዚህም በላይ እንግዳ መጥራት ይቻላል፡፡ ጀማሪ ከመሆናቸው አኳያ በግንዛቤ እጥረትና በልምድ ማነስ የተነሳ መስተንግዷቸው አርኪ ላይሆን ይችላል እንጂ እንግዳው ስለበዛ፣ በዓል ስለተደራረበ ሆስፒታሊቲ መጥፎ ይሆናል የሚል እምነት የለኝም፡፡ ግንዛቤና ልምድ ከሌለ ጥቂት እንግዳ መጥቶ መስተንግዶውና ሁኔታው ላይመቸውና ቆይታውንም ላያራዝም ይችላል፡፡ ስለዚህ ቀስ በቀስ በልምድና በስልጠና በሆስፒታሊቲ ዘርፍ የተሰማሩ ተቋማትን ማስተካከል ይቻላል፡፡ ለምሳሌ በ2003 ዓ.ም በተደረገው አጠቃላይ የመስተንግዶ ግምገማ፣ 2004 ዓ.ም እና 2005 ዓ.ም ላይ የተሻሉ የመስተንግዶ ስራዎች ተሰርተዋል፡፡ ከባለፈው ዓመት የዘንድሮው የተሻለ እንደሆነ አምናለሁ፣ ስለዚህ በዓላት መደራረባቸው ሳይሆን የግንዛቤው ጉዳይ ነው  ሆስፒታሊቲው ላይ ችግር የሚፈጥረው የሚል እምነት አለኝ፡፡ በዓላት ተደራርበውም ግን  ያን ያህል ጐንደር በእንግዳ ተጥለቀለቀች ለማለት ያስቸግረኛል፡፡ ቀደም ብዬ እንደተናገርኩት፣በበዓላቱ መደራረብ ከወትሮው የእንግዳ ቁጥር ትንሽ ጨምሯል፡፡ በሌላው ዓለም እኮ በአንድና በሁለት ቀን የሚገባው ቱሪስት መጠን የሚያስደነግጥ ነው፡፡
እርስዎ የሚያውቁት ቱሪስት የሚጎርፍበት የአለም ከተማ አለ?
እኔ በቅርቡ እስራኤል አገር ሄጄ ነበር፡፡ እየሩሳሌም ኦልድ ሲቲ የሚባል ቦታ አለ፡፡ በአንድ ቀን የሚገባው ቱሪስት አካባቢውን የሚያጨናንቅ ነው፡፡ ታሪካዊ ቦታዎችን ለማየት ወረፋው በጣም በጣም የሚያታክት ነው፡፡  ያንን ያየ ሰው፣ጐንደር እንግዳ ያጨናነቃት፣ አስተናጋጆች መውጫ መግቢያ አጥተው የሚዋከቡባት ናት ሊል አይችልም፡፡ ነገር ግን አገልግሎት ሰጪ ተቋማት በተፈለገው ደረጃ ተገንብተው፣ በጥራት ደረጃቸውም ልቀው ሄደዋል ለማለት አንችልም፡፡ ይሄ ቀስ በቀስ ከልምድም ከኢኮኖሚ አቅምም ጋር ተያይዞ የሚስተካከል ነው፡፡
ህዝቡ ከቱሪዝሙ ተጠቃሚ ሆኗል ብለውኛል፡፡ ቱሪስቱ የሚመጣው ቅርሶች ስላሉ ነው፡፡ ነገር ግን ህዝቡ ለቅርሶቹ ያን ያህል ጥንቃቄና ጥበቃ ያደርጋል የሚል እምነት አላደረብኝም፡፡ አንዳንድ ታሪካዊ ቅርሶች በጥንቃቄ ጉድለት ጉዳት ደርሶባቸው ይስተዋላል፡፡ የአስተዳደሩ  ጽ/ቤት  ህዝቡ በቅርስ አጠባበቅ ላይ ግንዛቤ እንዲኖረው ምን ያህል ጥረት አድርጓል?
ትክክል! አንደኛ በባለቤትነት የጐንደር ከተማ ባህልና ቱሪዝም አለበት፡፡ ከእኛ ጽ/ቤት ጋር በትብብር የሚሰሩም አሉ፡፡ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን ቅርሱ እንዲጠገንም እንሰራለን፡፡ ሁለተኛ ቅርሱን ለመንከባከብ፣ ጥፋት እንዳይደርስበት የምንሰራቸው ስራዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ በፊት የሰርግ ስነስርዓት ሲኖር፣ በፋሲል አብያተ መንግስታት ጭፈራና የሞንታርቦ ጩኸት ይደረግበት ነበር፡፡ ድምፁና ጭፈራው ቅርሱን እንዳይጐዳው ያንን ማስቀረት ችለናል፡፡ እዛው አካባቢ ባዛርም ይካሄድ ነበር፡፡ መስቀል አደባባይ ላይ ሁከቱና  ባዛሩ ቅርሱን እንዳይጐዳው እሱንም አስቀርተናል፡፡ የፓርኪንግ ስራም ነበረው፡፡ አሁን በአካባቢው ምንም ስራ አይሰራም፡፡ በከተማ አስተዳደሩ በኩል የጐደሉ ነገሮችን ማስተካከሉ እንዳለ ሆኖ ቅርሶችን የመንከባከብ ስራ እየሰራን ነው፡፡ ከግንዛቤም አኳያ አጠቃላይ ለህዝቡ ግንዛቤ ፈጥረናል ብለን አናስብም፣ ግን በዘርፉ እየተሰሩ ያሉና የተጀመሩ እንቅስቃሴዎች አሉ፡፡ የአመቱን እቅዳችንን ለፈፃሚ አካላት በምናስተዋውቅበት ጊዜና በተለያዩ ዎርክሾፖች ላይም ቅርሱን መታደግ የከተማ አስተዳደሩና የተወሰኑ አካላት ብቻ ሳይሆን የህዝቡም እንደሆነ ግንዛቤ ለማስጨበጥ የጀመርናቸው እንቅስቃሴዎች አሉ፡፡ በአጠቃላይ ግን የተሟላ ግንዛቤ ህዝቡ ልብ ውስጥ አኑረናል የሚል እምነት የለንም፡፡ በቀጣይ ከፍተኛ ስራን መስራት ይጠይቃል ማለቴ ነው፡፡
የተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት /UNESCO/ አንድ ቅርስ የአለም ቅርስ ነው ብሎ ሲመዘግብ የቅርሱን ዙሪያና አጠቃላይ ድባብ /Buffer Zone/ ብሎ ይከልላል። በፋሲል አብያተ መንግስታት ዙሪያውን ያሉ የድሮ ክብክብ ድንጋይ ቤቶች በባፈር ዞኑ የተከለሉ ይመስለኛል፡፡ እዛ አካባቢ ግን ስጋቶች አሉ?
ምን አይነት ስጋቶች ናቸው?
ሰሞኑን በእንኮዬ በር በኩል እነ እመት አበቅየለሽ መንደር ሄጄ ነበር፡፡ እዛ አካባቢ ያሉ የድንጋይ ክብክብ ጥንታዊ ቤቶች ሲፈርሱ ነበር፡፡ የህንጻ ግንባታ ሊካሄድ ነው የሚል ስጋትም አለ፡፡ ይሄ ከዩኔስኮ ጋር አያጋጫችሁም?
ጥሩ! አንደኛ በጐንደር ከተማ ላይ እየሰራን ያለነው ስራ ምንድነው---ህንጻ በአካባቢው ሲገነባ ከፍታው አልፎ አልፎ ችግር ነበረው፡፡ ይህ የሆነው ከግንዛቤ ማነስ ነው፡፡ የፋሲልን አጠቃላይ እይታ የሚከልሉ ፎቆች ተሰርተው ነበር፡፡ ነገር ግን ባለፉት አመታት የባህል ፌስቲቫሎቹን ስናከብር እግረ መንገዱን ልዩ ልዩ የፓናል ውይይቶች ይካሄድ ነበር፡፡ እዚያ ላይ ትኩረት ሰጥተን ያየነው ነገር ምንድነው--- በግንቡ ዙሪያ እይታውን የሚከልሉ ፎቆች በተሰሩ ቁጥር፣ ግንቡ ቱሪስትን የመሳብ አቅሙ ይቀንሳል፡፡ በተጨማሪም ዩኔስኮ ከዝርዝር ውስጥ ያወጣዋል የሚለውን ጉዳይ ተመልክተናል፡፡ ከዚያም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከመጡ ምሁራን ጋር በመተባበር በተደረገ ውይይት፣ ከግንቡ በተወሰነ ሬዲየስ ላይ የሚገነቡ ፎቆች ከፍታ መጠን እንዲወሰን የሚያደርግ ሥራ ተሰርቷል፡፡ ሌላው ቅድም ያልኳቸው እንኮዬ መስክ አካባቢ ያሉ ቤቶች እንዳይፈርሱ ጥብቅ ክትትል እናደርጋለን። ሌላው ቀርቶ ፊት ለፊት ቅድም ያየሻቸው ቤቶች በመኖራቸው፣ የጐንደር ዋና ዋና መንገድ አይተሽው ከሆነ ድሮ በጣሊያን የተቀየሰ ነው፡፡ በዚያ ምክንያት ትንሽ የትራፊክ መጨናነቅ አለ፡፡ አሁን የእግረኛ መንገድ እየሰራን ነው፡፡ መንገዱን ስንሰራ እነዚህን የድንጋይ ክብክብ ቤቶችን አገኘን፡፡ እነዚህን ቤቶች ማፍረስ በቅርሱ ላይ የሚያደርሰውን ጥፋት ስለምናውቅ እንዳይነካ አድርገናል፡፡ እንኮዬ መስክ ላይ ያሉ ተመሳሳይ ቤቶችንም እንዲሁ የምንነካበት ምክንያት አይኖርም፡፡ ሁለተኛ የኮር ዞንና በፈር ዞን የሚለውን በተመለከተ  ከፌዴራልም ከክልሉም ጋር እየተነጋገርንበት ነው፡፡ ባለሙያዎችም ያጠኑት ነገር አለ፡፡ በፈር ዞኑ እስከየት ድረስ ነው? የሚለውን ጉዳይ ማለት ነው፡፡ የት የት ድረስ መከለል አለበት የሚለውንም ያጠኑት ባለሙያዎች ለከተማው ባህልና ቱሪዝም ገልፀዋል፡፡ በቅርቡም ለከንቲባ ኮሚቴ ቀርቦ መልክ የምናስይዘው ይሆናል፡፡
ቀደም ሲል የመፍረስ ስጋት ብቻ ሳይሆን ይፍረሱ የሚል ትዕዛዝ ተሰጥቶ ላለፉት ስድስት አመታት ክርክር ላይ ያሉ ባለ ይዞታዎችን አግኝተናል፡፡ “እነዚህ ደብር ያላቸውና ከግንቡ ጋር ልዩ ታሪክ ያላቸው በመሆኑ ሊፈርሱ አይገባም፣ ሲፈርሱም ከ300 ሰዎች በላይ ይፈናቀላሉ” ሲሉ ቅሬታ አቅርበዋል፡፡ ይህን ያውቃሉ?
የምትይውን ቦታ በትክክል አላወቅኩትም ነገር ግን ዩኔስኮ እንዲጠበቁ በበፈር ዞን የያዛቸው ቤቶች እንደማይሆኑ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ሌላው ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ እዛ አካባቢ ፎቅ ይገንባ ቢባል እንኳን የከፍታው ሁኔታ የተመጠነና የግንቡን ሁኔታ በማይከልል ሁኔታ ነው፡፡ ይፈርሳል የሚባሉ ቤቶች  ካሉም ዝም ብሎ በግለሰቦች የተያዙ ነገር ግን ከተማዋ ደረጃዋን የጠበቀች እንድትሆን የመልስ ማልማት ስራ የሚካሄድባቸው ይሆናሉ እንጂ እነዚህ ዩኒስኮ ጥብቅ ያደረጋቸው “ጅጌ” የተባሉት ክብ የድንጋይ ቤቶች አይነኩም፡፡ የቀበሌ ቤቶች ይኖራሉ- በግለሰብም የተያዙ ሆነው ጐስቋላ ቤቶች፡፡ እነሱ ለመልሶ ማልማት ሊፈርሱ ይችላሉ፡፡ ይህ ደግሞ አዲስ አበባም ሆነ ሌላ የትኛውም ከተማ ላይ የሚካሄድ ነው፡፡
ሌላው የአካባቢው ነዋሪዎች ያነሱት ቅሬታ “እዛው መንደር ውስጥ እመት አበቅየለሽ ጠጅ ቤት ፊት ለፊት አቢሲኒያ ባንክ ያለበት ህንፃ የተገነባው ሌሎች ጥንታዊ ቤቶች ፈርሰው ነው፡፡ የህንፃው ሶስት አራተኛ ክፍል ግን አልተከራየም፡፡ ሰው ከቦታው የተፈናቀለው በከንቱ ነው” የሚል ነው፡፡ በዚህ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድነው?
ያልሽው ህንፃ ከተገነባ ቆይቷል፡፡ ያን ጊዜ እኔም አልነበርኩም፡፡ ግን ህንፃው ሲገነባ የምትያቸው ጥንታዊና መፍረስ የሌለባቸው ቤቶች እንደፈረሱ የሚያሳይ ሪፖርት የለም፡፡ በየሶስት ወሩ ህዝቡን በሲኒማ አዳራሽ እያገኘን እንወያያለን፡፡ ሆኖም እንዲህ ዓይነት ቤቶች ፈረሱ የሚል ቅሬታ ሳይሆን ቅድም ከቅርስ ጥበቃ ጋር ያነሳሽው አይነት ሃሳብ ያቀርባሉ፡፡ ይህ ማለት እንዴት ቅርሶች ከጉዳት ይጠበቁ፣ ህዝቡ እንዴት የባለቤትነት ስሜት ይሰማው በሚልና በመሰል ጉዳዮች ህዝቡ ሃሳቦችን እያነሳ እንወያያለን፡፡ አሁንም አቢሲኒያ ባንክ ያለበትን ህንፃ በተመለከተ በፋሲል ግንብ ፊት ለፊት እንደመሆኑ ከG+1 በላይ እንዳይገነባ በወቅቱ የነበረው አመራር መከልከል ነበረበት፡፡
ግን እኮ ህንፃው ባለሶስት ፎቅ ነው?
ትክክል ነው፣ ሶስት ፎቅ ነው፡፡ ይህንን እንደ ስህተት ነው የምንወስደው፣ አሁንም የማረጋግጥልሽ ለቅርስ ተብለው የተያዙ ቤቶች አይፈርሱም። ከዚያ ውጭ ያሉ የግል ጐስቋላ የቀበሌ ቤቶች በመልሶ ማልማት ግን ይፈርሳሉ፡፡
ከተማዋ የአለም አቀፍ ቱሪስቶች መዳረሻ ከመሆኗ አንፃር  ጽዳት ይጐድላታል፣ የሚሸቱ ቱቦዎች አሉ፣ ይሄ ደግሞ ቱሪስቶችን ያሸሻል፡፡ ይሄን ለማሻሻል ምን አስባችኋል?
ትክክል ነው፣ የጽዳት ችግር አለ፣ ግን ጽዱ ለማድረግ እየሰራን ነው፡፡
ለምሳሌ ምን አይነት ስራዎች?
ለምሳሌ አንዱ ያደረግነው ነገር ምንድነው--- የደረቅ ቆሻሻ ማኔጅመንቱ በፊት በማዘጋጃ ቤቱ ነበር የሚካሄደው፡፡ ነገር ግን ውጤታማ ባለመሆኑ፣ እንዲህ አይነት ስራዎችን በሌላ አካል (አውት ሶርስ) በማሰራት የስራ እድል መፍጠርና ህዝቡንም ማሳተፍ ይቻላል በሚል ከባለፈው አመት ጀምሮ በምክር ቤታችን አጽድቀን እየተሰራበት ነው፡፡ እዚህ ላይ ያጋጠመን ችግር ማህበራቱ የጠነከሩ አለመሆናቸው  ነው፡፡ አንደኛ ተሽከርካሪ የላቸውም፣ ተከራይተው ነው የሚሰሩት፡፡ ሁለተኛ የልምድም ማነስ ችግሩን ሙሉ በሙሉ ለመቅረፍ እንቅፋት ሆኗል፡፡ አሁን የትኛውን አማራጭ እንጠቀም የሚለውን እያጠናን ነው፡፡
ሁለተኛ ከፍሳሽ ቱቦዎች መሽተት ጋር ያነሳሽው ችግር፣ ብዙዎቹ በተለምዶ ፒያሳ በሚባለው አካባቢ ያሉት ድሮ በጣልያን ጊዜ የተሰሩ ፍሳሽ ማስወገጃዎች በመሆናቸው የመጣ ችግር ነው። ከባለፈው አመት ጀምሮ የእግረኛ መንገድም የፍሳሽ ማስወገጃ ቦይዎችም እየሰራን ነው፡፡ እሱን ስንሰራ ሴፕቲክ ታንካቸው በቀጥታ ከድሬኔጅ ጋር የተገናኘ ሆኖ ነው ያገኘነው፡፡ እነዚህ ችግሮች በአብዛኛው ያለባቸው ቤቶችና አካባቢዎች የኪራይ ቤቶች ይዞታ ናቸው፡፡ አሁን ሳያልቅ ስለመጣችሁ ነው እንጂ እሱን የማስተካከል ስራ ጀምረናል፡፡ ሴፕቲክታንክ እንዲቆፈር፣ ከድሬኔጅ ጋር የተያያዙ ስዌሬጆች እንዲላቀቁ የማድረግ ስራ ተጀምሯል፡፡ አንቺ እንዳልሽው የተወሰኑ ቅሬታዎች ይደርሱናል፣ ነገር ግን ኪራይ ቤቶች በቅርቡ እልባት ይሰጠዋል ብለን እናምናለን፡፡ በአጠቃላይ ያለውን የከተማ ጽዳት ወደተሻለ ደረጃ ለማድረስ፣ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የፍሳሽ ማስወገጃ መኪኖችን ገዝቶ በቅናሽ ዋጋ ለማህበረሰቡ መስጠት ጀምሯል። ያየሽውና የጠየቅሽው ትክክል ነው፡፡ ጐንደር ከተማ በተፈለገው ደረጃ አልፀዳችም፡፡ ግን ይህንን ለማስተካከል እየተሰራ ነው፡፡  
ሌላው እጅግ አሳሳቢው ነገር የቢራ ፋብሪካዎች የፉክክር ትንቅንቅ ነው፡፡ በየምሽት ቤቱ ቢራዎችን እየጠጡ የሚያስተዋውቁት 18 አመት ያልሞላቸው ታዳጊዎች ናቸው፡፡ በሁሉም ቢራ በሚሸጥባቸው  ምሽት ቤቶች ቢራ ስፖንሰር ያደርጉና “ይሄ የእከሌ ቢራ ቤት ነው ይሄኛው ራስ ምታትና ሀንግኦቨር አለው” እያሉ ህፃናቱ ሲናገሩ አንገት ያስደፋል። ይህን ጉዳይ የእርስዎ ጽ/ቤት ያውቀዋል? ይሄ ትውልዱን ወዴት ይወስደዋል?
ይሄ ጉዳይ ከማስታወቂያ አለጣጠፉ ጀምሮ ቅድም ያልሽውን ነገር ያመጣል፡፡ አሳሳቢም ነው። ሰሞኑን ከበዓሉ ጋር ተያይዞ በየኮርነሩ ያለው ማስታወቂያ ይገርማል፡፡ የነፃ ገበያ አስተሳሰብና ግንዛቤ ልክ እንዳልሆነ እየገባን ነው፡፡ በቀደም ዕለትም በጨረፍታም ቢሆን አሁን አንቺ ያልሽኝን ነገር ሰምቼዋለሁ፡፡ አንድ የቢራ ኩባንያም ሆነ ሌላ ባለምርት ምርቱን ማስተዋወቅ ያለበት ተጽእኖ በማሳደር አይደለም፡፡ ለምሳሌ ዳሽን ምርቱን ለማስተዋወቅ የራሱ ጋርደኖች አሉት፡፡ አሁን በየምሽት ቤቱ ህፃናቱን እያሰማሩ እንዲህ አይነት ስራ ስለማሰራታቸው በጨረፍታ ሰምቻለሁ፡፡ ስህተቱ ግን የወጣቶቹ ነው የሚል እምነት የለኝም። ይህ ችግር የቢራ ኩባንያዎቹ ነው፡፡ የቅስቀሳውም ሁኔታ ትክክል አይደለም፡፡
በአንድ የአዝማሪ ምሽት ቤት “ይሄን ቢራ አትጠጡ ራስ ምታት አለው” እያሉ ህፃናት ልጆች ሲናገሩና የሚያስተዋውቁትን ቢራ እየጠጡ ሲጨፍሩ እዚያው ሆኜ በዓይኔ አይቼአለሁ---
ለዚህ ችግር በአስቸኳይ  እልባት መስጠት ይኖርብናል፣ ካልሆነ ችግሩ የከፋ ይሆናል፡፡ የትኛውም ቢራ ሲያስተዋውቅ አግባብ በሆነ መንገድ እንጂ ሌላውን እያጥላላና ተጽእኖ እየፈጠረ መሆን የለበትም፡፡ አንዱን እየጠጡ፣ ሌላውን  ይፈልጥሃል  ይቆርጥሃል፣ ማለት ተገቢ አይደለም፡፡ ይሄ የተሳሳተ አካሄድ ነው፡፡ ዳሽን ብቻ የሚሸጥበት ወይም ሜታ ብቻ የሚሸጥበት ሆቴል የለም፡፡  ሁሉም ቢራ ይሸጣል፡፡ ሰው የሚፈልገውን መርጦ ይጠጣል ወይም የራሳቸው ቢር ጋርደን ሊኖራቸው ይገባል። በእርግጠኝነት የምነግርሽ ግን የእኛ ንግድ መምሪያ አለ፡፡  
በመምሪያው በኩል አቅጣጫ እናስቀምጣለን። በሌላ በኩል የኩባንያዎቹን ተወካዮች ጠርተን ከፍተኛ ማስጠንቀቂያ እንሰጣለን፡፡  ጉዳዩ ችላ የሚባል አይደለም፡፡ ጥቆማውና መረጃው ግን በጣም ይጠቅመናል፡፡ ይሄ ጉዳይ አይቀጥልም፡፡ በቅርቡ  ህጋዊ እርምጃዎችን እንወስዳለን፡፡
የጥምቀት እለት የቻይናውን አምባሳደር ጨምሮ በርካታ እንግዶች ሞባይል፣ ካሜራ፣ ፓስፖርትና ሌሎች ንብረቶች ተሰርቆባቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ የፀጥታና ደህንነት ስራው ላይ ክፍተት እንዳለ የሚጠቁም ነው፡፡ በበዓሉ ላይ ምን ያህል ንብረት እንደተሰረቀ መረጃው አለዎት? በዕለቱ የሶስት የካሜራ ጋዜጠኞች ሞባይል መጥፋቱንም አውቃለሁ፡፡ ይሄ የጎንደርን ገፅታ አያበላሽም?
ይህን በዓል ስናስብ በተለይ የፀጥታ አካሉ እና የአስተዳደር ፀጥታ፣ እንዲሁም ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ከፍተኛ ዝግጅት አድርገዋል፡፡ በበዓሉ ብቻ ሳይሆን ቱሪስቶች በየጊዜው ስለሚገቡና ስለሚወጡ አመቱን ሙሉ ከፍተኛ ጥንቃቄ ይደረጋል፡፡ እሱ እንደተጠበቀ ሆኖ ቀደም ሲል የጠቀስሻቸው ችግሮች ተከስተዋል፡፡ ይህም የተከሰተው ጥምቀተ ባህሩ ላይ የሚገባው ህዝብ ከመጠን በላይ የተጨናነቀ ስለነበረ ነው። እዛ ላይ የሞባይል እና የመሳሰሉ እቃዎች ንጥቂያ ተፈጽሟል፡፡ የሚገርምሽ ከሰዓት በኋላ ብዙዎቹ እጅ ከፍንጅ ተይዘዋል፡፡
ስንት ይሆናሉ እጅ ከፍንጅ የተያዙት?
27 ናቸው፡፡ የሚገርምሽ ይህን በዓል በማሰብ ከሌላ ክልል ተደራጅተው መጥተው ነው የያዝናቸው፡፡ 13 ያህል ተንቀሳቃሽ ስልክ እጅ ከፍንጅ ተይዞ ለባለቤቶቹ ተመልሷል፡፡ ፓስፖርትና መንጃ ፍቃድ ተመልሷል፡፡ ከ27ቱ ውስጥ  የዚህ ከተማ ነዋሪ ሆኖ ያገኘነው አንድ ሰው ብቻ ነው፡፡ ከ26ቱ ደግሞ 11ዱ ከአንድ ክልል የመጡ ናቸው፡፡
እኔ ጐንደር ከመጣሁ ዛሬ ዘጠነኛ ቀኔ ነው፡፡ እስካሁን መብራት ጠፍቶ አያውቅም፣ ውሃም ሄዶ አላየሁም፣ የኢንተርኔት አገልግሎቱም ግሩም ነበር፣ ነገር ግን አንዳንድ ነዋሪዎች በከተማዋ  የውሃ ችግር እንዳለና በየተራ ውሃ እንደሚያገኙ፣ መብራት እንደሚቆራረጥ የሚናገሩ አሉ፡፡ ለበዓሉ እና ለእንግዶች ሲባል በውሃና መብራት ላይ ጥንቃቄ ተደርጐ ነው? ወይስ--
Thank you! ጐንደር ላይ አንዱ ቅሬታ የውሃና የመብራት መቆራረጥ ችግር ነበር፡፡ የችግሩ መንስኤ የውሃም ሆነ የመብራት አለመጠገን ነበር። የሚገርመው ከባለፈው አመት ሚያዚያ በፊት በሳምንት በአማካይ ሶስትና አራት ጊዜ መብራት ይጠፋ ነበር፡፡ ይህንን ለማስቀረት ከሰሜን ምዕራብ ሪጂን መብራት ሃይል ጥገና ክፍል ጋር በመነጋገር ከፍተኛ ስራ ሰርተናል፡፡ በፊት መቆራረጥ ብቻ ሳይሆን  ሃይል የለውም፡፡ በተለይ ትልልቅ ሆቴሎች ላይ ደብዛዛ ሆኖ ነበር የሚበራው፡፡ በዚህ ምክንያት ለተከታታይ ሶስት ወራት ጥገና ተካሄደ፡፡ ከዚያን ጊዜ በኋላ ጐንደር ላይ መብራት አይጠፋም፡፡ በውሃም በኩል ከአንገረብ ወንዝ ውሃው የሚገፋው በኤሌክትሪክ ፓምፕ ስለነበር መብራት ሲቋረጥ ውሃም ይቋረጥ ነበር፡፡ ከባለፈው ሰኔ ወር ጀምሮ ግን የውሃም የመብራት መቋረጥም በእጅጉ ቀንሷል፡፡


Read 3310 times
Administrator

Latest from Administrator