Sunday, 19 January 2014 00:00

“ኢትዮጵያ ቁጭ ብላለች እንጂ ወደ ኋላ አልተመለሰችም”

Written by  አበባየሁ ገበያው
Rate this item
(8 votes)

የኢትዮጵያ ታሪክ ገንኖ የሚታወቅበት ጊዜ ይመጣል
“እኔ ብቻ አውቃለሁ” የምንለው ነገር የትም አያደርስም
ዩኒቨርስቲዎቻችን በኢትዮጵያ ትምህርት አልጠነከሩም
ግዕዝ በታወቁ የዓለም ዩኒቨርስቲዎች የተከበረ ትምህርት ነው

 የአሁኑ አመጣጥዎ የተለየ ዓላማ (ተልዕኮ) አለው? ወይስ… ከ25 ዓመት በፊት “አት ሆፕ ፒስ” የሚል ድርጅት አቋቁመን ነበር፡፡ ወቅቱ የጦርነት ጊዜ ነበር። ለአገሪቱና ለህዝቡ ሰላም ለማምጣት የተመሰረተ ነበር፡፡ በኋላም ከክቡር አቶ መለስ ዜናዊ (ነፍሳቸውን ይማረውና) እንዲሁም ከፕሬዚዳንት ኢሣያስና ሌንጮም ጋር ተገናኝተን ተወያይተናል - በሰላም ጉዳይ፡፡ በተለይ ክቡርነታቸው የድርጅታችንን ስራ ወደውልን ነበር፡፡ ሰላሙን ለማጐልበት ይጠቅማል ብለውናል፡፡ ከዚያም አድጐ ጊዜያዊ ፒስ ኮሚቴ ሆነ - “ፒስ ኤንድ ዴቨሎፕመንት ሴንተር” በሚል ስያሜ፡፡ የድርጅቱ አባላት ኢትዮጵያን የምንወድ ሰዎች ነን። መንግስትም ህዝቡም እየተባበረ ይሠራል የሚል እምነት ስላለን፣ ከ20 ዓመት ጀምሮ አንዳንድ ሰዎች የጥላቻ ቃል ሲናገሩ “ጉዳዩን በፍቅር እንፈታለን” እያልን ከክቡርነታቸው ጋር እንማከር ነበር፡፡ “ፒስ ኤንድ ዲቨሎፕመንት” እያደገ ሄደና በ1993 ዓ.ም እዚህ ትልቅ ኮንፈረንስ ተደረገ፡፡ የሃይማኖት መሪዎች፣ የመንግስት ሃላፊዎች፣ የመምህራን ማህበር እና ራሱ መንግስት የተሳተፉበት ትልቅ ስብሰባ ነበር፡፡ ከውጭ አገርም ሰዎች ጋብዘን፣ የኢትዮጵያ ፍቅርና ሠላም እንዲጠናከር ፀሎት አደረግን፡፡ ብዙ ሰው የሚያውቀው አንድ የድርጅቱ መፈክር አለ፤ “ወሬ አናብዛ፤ ስራውን እንስራ” የሚል ነው።

ብዙ ጊዜ ስራችን የሚዲያ ሽፋን እንዲያገኝ አንፈልግም፤ አንዳንዴ እየሾለከ ቢፃፍም ብዙ ጊዜ ግን እንጠነቀቃለን፤ ፐብሊሲቲ (ራስን ማስተዋወቅ) አንወድም፡፡ እናም አመጣጤ ለዚህ ድርጅት ዓመታዊ የቦርድ ስብሰባ ነው፡፡ በዳያስፖራው ዘንድ ጭፍን የጥላቻ ፖለቲካ ይንፀባረቃል የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ ድርጅታችሁ በዚህ ጉዳይ ላይ የሰራው ስራ አለ? ጥሩ ጥያቄ ነው፤ ምክንያቱም በየጊዜው አሜሪካ ያለነው የቦርድ አባላት የምናውቃቸውን ግለሰቦችና ቡድኖች ለማናገርና ለማወያየት እንሞክራለን። ምንም ቢሆን አገርን ማንቋሸሽ ጥሩ አይደለም። እዚያ ተቀምጠን አገርን ማስከበር፣ ኢትዮጵያ እንድታድግ ማድረግ ነው የሚያስፈልገው፡፡ እዚያ ያሉትን ኢንቨስተሮች ሁልጊዜ እናወያያለን፡፡ የእኛ ድርጅት እንደውም በቅርቡ ስሙ ተለውጦ “ሰላምና እድገት ማዕከላዊ ማህበር” ይባላል፡፡ ሰላም ከሌለ እድገት የለም፡፡ እድገት ከሌለ ሠላም የለም። ሁለቱም የተያያዙ ናቸው፡፡ ባልና ሚስት ማለት ናቸው፡፡ እዚያ ያሉ ኢንቨስተሮች፤ ትኩረታቸውን ኢትዮጵያን በንግድና በእርሻ ለማሳደግ እንዲጥሩ እንገፋፋለን። እዚያ ቁጭ ብላችሁ መጮህ የለባችሁም እንላቸዋለን። ብዙዎቹ ሃሳባችንን ይወዱታል፡፡

ዘጠና አምስቱ ፐርሰንት ይስማማሉ። አምስቱ ፐርሰንት ደግሞ ሌላ ሃሳብ ሊኖራቸው ይችላል፡፡ በቅርቡ ደግሞ አንድ ፕሮጀክት ጀምረናል - “አፍሪካ ፒስ ሴንተር” የሚል፡፡ የአካዳሚክ ድርጅት ነው፤ “ኢንስቲቲዩት ኦፍ ሴሜቲክ ስተዲስ” ይባላል። ጆርናሎችና መጽሐፍት በየጊዜው እናወጣለን። በህዝብ ግንኙነትና በኮሙዩኒኬሽን ሰላም ለማምጣት የሚንቀሳቀስ ተቋም ነው፡፡ ለምሳሌ “ኢንስቲቱዩት ኦፍ ሴሜቲክ ላንጉጅስ” በተለይ በመካከለኛው ምስራቅ ውስጥ ይንቀሳቀሳል። ለአረቦችና እስራኤሎች ውዝግብ አንዳንዴ ቋንቋ የመግባባት በር ይከፍታል ብለን እናምናለን፡፡ አንዳንዴ ደግሞ በርም ሊዘጋ ይችላል። የእኛ ተቋም በትምህርት ላይም ተመስርቶ ህዝቡ ደግሞ እንዲቀራረብ፣ እንዲወያይ፣ እንዲግባባ፣ እንዲስማማ፣ እንዲፋቀር ይሰራል፡፡ አሁን ደግሞ መካከለኛው ምስራቅን ብቻ ሳይሆን አፍሪካንም እንጨምር ተብሎ “አፍሪካ ፒስ ሴንተር” በሚል ጀምረናል፡፡ በአፍሪካም ዓላማው ተመሳሳይ ነው? ሁለት ዓላማ አለው፡፡ አንደኛው አፍሪካ ውስጥ ያሉትንም ችግሮች ተገናኝተን እንድንወያይ፣ እንድናውቃቸው የሚል ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በአካዳሚክ መንገድ ነው፡፡ አሜሪካ ውስጥ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ አፍሪካ አሜሪካውያን ተማሪዎች አሉ፡፡ ዞሮ ዞሮ ከእነሱ መካከል ነው ወደ አፍሪካ ተመልሰው መሪዎች የሚሆኑት፡፡

ሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ፕሮፌሰር ሳለሁ፤ አፍሪካ ውስጥ የነበረውን አፓርታይድ ከማንም በፊት አጥብቀው መቃወም የጀመሩት ጥቁር አሜሪካውያንና ጥቁር አፍሪካውያን ናቸው፡፡ ሀርቫርድ ዩኒቨርስቲም ትልልቅ የተቃውሞ ትእይንቶች ያደርጉ ነበር፡፡ ይሄን እንቅስቃሴ በመላው ዓለም የገፉት በአሜሪካ ውስጥ ያሉት አፍሪካውያንና አፍሪካ አሜሪካውያን በትብብር ነው፡፡ በአሜሪካ የሚገኙ አፍሪካውያንና አፍሪካ አሜሪካውያን በአፍሪካ ውስጥ ሠላምና መረጋጋት እንዲፈጠር፣ ኢኮኖሚውም እንዲዳብር መተባበር ይችላሉ፡፡ በዚህ መንፈስ ነው የምንሠራው፡፡ ዲያስፖራ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ዛሬ እንደውም እንደሰማሁት፤ በዓመት ከ3 ቢሊዮን በላይ ዶላር ወደ ኢትዮጵያ ይላካል - ከዲያስፖራው፡፡ ይሄ ደግሞ ለአገር ቤት በእጅጉ ይጠቅማል፡፡ በአፍሪካም ሆነ በኢትዮጵያ ግጭቶች ከመከሰታቸው በፊት የምትሰሩት የመከላከል ሥራ አለ? አሁን በአገራችን ሠላም አለ፡፡ ያለው ሰላም እንዳይናድ፣ ትልቅ ዛፍ እንዲሆን እየሠራን ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ በመሠረቱ ተስማምቶ የሚኖር ህዝብ ነው፡፡ አንዳንዶቻችን አልፎ አልፎ በሀይለ ቃል ብንናገርም፤ ብንሳደብም ህዝባችን መግባባት የሚችል ህዝብ ነው፡፡ ብዙ ሀገር ዞሬ አይቻለሁ፡፡

አንድ ጊዜ ኬንያ ሄጄ፤ “ቀን ቀን አትውጣ፣ አደገኛ ነው” ተባልኩ፡፡ ደቡብ አፍሪካ ስሄድ ደግሞ “ማታ ማታ አትውጣ፤ አደገኛ ነው” አሉኝ፡፡ አዲስ አበባ ግን ይሄ ሁሉ ችግር የለም፤ ሰላም ነው፡፡ የኢትዮጵያ መሠረቱ ህዝቡ ነው፡፡ ህዝቡ ባህል አለው፤ መንፈሳዊ ህዝብ ነው፤ ሰው የሚያከብር ነው፡፡ ከመካከላችን ግን አሉ፤ ሃይለኞች፡፡ በተለይ የማኪያቬሊን መጽሐፍ ያነበቡ፣ የማርክሲዝም ትምህርት ተምረው አንጐላቸው ትንሽ የዞረ ጥቂቶች አሉ፡፡ ማዕከላችሁ ከሃይማኖት መቻቻል ጋር በተያያዘ በክልሎች ጭምር የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን ያደርጋል፡፡ በዚህ ሂደት የገጠማችሁ ችግር፣ ፈተና ወይም መሰናክል ይኖራል? እኛ ብቻ አይደለንም፤ ሌሎችም ድርጅቶች አሉ፡፡ የውጭም የውስጥም “ኢንተርፌዝ” የሚባል ህብረት አለ፡፡ ዋናው ነገር ህዝቡ ውይይት እንዲያደርግ ሁኔታዎችን ማመቻቸት ነው፡፡ ትልቅ “ኢንተርፌዝ” ስብሰባ ያደረግነው እ.ኤ.አ በ1992 ዓ.ም ነበር፡፡ እኔ እራሴ አሁን ሶስት መፃህፍት እየፃፍኩ ነው - ስለክርስቲያን፣ ስለ እስላም እና ስለ ይሁዲ፡፡ እኛ አገር የተለያዩ ሃይማኖቶች ቢኖሩም ህዝቡ ከጥንት ጀምሮ ተቻችሎ የኖረ ህዝብ ነው፡፡ አዲስ የምንፈጥረው ነገር የለም፡፡ ያ ባህል እንዳይጠፋ ማድረግ ነው ያለብን፡፡ የኢትዮጵያ ክርስቲያንም እስላምም ለብዙ ዘመን ተቻችሎ የኖረ ነው፡፡ እኔ በጣም የሚያስገርመኝ ወሎ ውስጥ አንዳንድ ቤተክርስቲያኖችን ገንዘብ አዋጥተው ያሠሩት እስላሞች መሆናቸው ነው፡፡

አንዴ የአርሲ ጳጳስ አቡነ ናትናኤል እንደነገሩኝ፤ ቤተክርስቲያን ሲያሰሩ ግማሹን ገንዘብ ያዋጡት ሙስሊሞቹ ናቸው፡፡ ከክርስቲያንም ከሙስሊምም ጥቂቶች ውጭ አገር ያለውን መንፈስ ይዘው ሊመጡ ይችላሉ፡፡ ጥቂቶች ልበል እንጂ የምፈራው ጥቂቶችን ነው፡፡ ጥቂቶችም ቢሆኑ ግን “ቁስላችሁ ምንድን ነው?” ብለን ከእነሱም ጋር ቁጭ ብለን መነጋገር፣ መወያየት ያስፈልገናል፡፡ ዛሬ ደግሞ ሌሎችም ድርጅቶች እየተነሱ ነው፡፡ አንዳንዶቹ “እኔ አውቃለሁ፤ የእኔ መንገድ ትክክል ነው” ይላሉ፡፡ እንደዚህ አይነት እንቅፋቶች ይኖራሉ እንጂ የከፋ ነገር እስካሁን የለም፡፡ በደቡብ ሱዳን የተከሰተውን ችግር ማዕከላችሁ ለመፍታት የሚያደርገው እንቅስቃሴ አለ? በሀርቫርድ ዩኒቨርስቲ “አፍሪካን ሪሊጂንስ” የሚባል ትምህርት ማስተማር የጀመርኩት እኔ ነኝ፡፡ ስለእነሱ ሃይማኖት ብዙ አጥንቼአለሁ። ጥቂቶቹን የጦርነቱ ጊዜ ኬምብሪጅ መጥተው አግኝቻቸዋለሁ፡፡ ጥሩ ባህል ያላቸው ናቸው፡፡ ህዝቡ ትዕግስተኛና ተግባቢ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ ጦርነቱና ግጭቱ የእንግሊዝ የቅኝ ግዛት ዘመን “ከፋፍለህ ግዛ” የፈጠረው ጣጣ ነው፡፡ የአፍሪካ ፒስ ሴንተር ሱዳንንም ለማገዝ የመስራት አላማ አለው፡፡ ብዙ ሰው የማይረዳው… ሰላምና ፍቅር እንደ ችግኝ ናቸው፡፡ ካልተንከባከቧቸው አይፀድቁም፤ ይደርቃሉ፡፡ ሰው ሲወለድ ህፃን ሆኖ ነው፡፡ ህፃን ደግሞ እስኪያድግ ጊዜ ይፈልጋል። ሰው ተወለደ ተብሎ ሜዳ ላይ አይጣልም፡፡ ማሳደግ ያስፈልጋል፡፡ በውጭ ያሉት ችግራቸው …የሠላም ስምምነት ተፈራረምን ብለው ቻው …ቻው ተባብለው ይለያያሉ፡፡

በኢትዮጵያና በኤርትራ ጉዳይ የሆነውም እንዲሁ ነው፡፡ አልጀሪያ ላይ ተፈራረምን ብለው ተጨባብጠው ተለያዩ፡፡ እኛ በዚህ አናምንም፡፡ የተፈራረሙት ነገር የሠላምም ቢሆን እንዲበረታና እንዲጠነክር የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱን ማጐልበት ያስፈልጋል፡፡ የታሪክ ሽሚያ ውስጥ የሚገቡት ወገኖች ናቸው ችግሩን የሚያባብሱብን፡፡ የእኛ ሰዎች መንፈሳቸው ጥሩ ነው፡፡ የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ህዝብ ቤተሰብ ነው፡፡ ቤተሰብ ከሆነ ደግሞ ባልና ሚስት እንኳን ይፋታል፡፡ ኢትዮጵያና ኤርትራ አንድ ህዝብ ነው፤ በባህል በቋንቋ፡፡ ግን ተፋታ፡፡ የተፋቱ ባልና ሚስትን ደግሞ ‹‹በአንድ አልጋ አብራችሁ ተኙ›› ብሎ ማስገደድ አይቻልም፡፡ ይኼ ጥሩ ህዝብ፤ ብዙ ጊዜ ግራ የሚጋባው በውጭ አካል ነው፡፡ ሁለቱን ህዝብ ትውት ስናደርጋቸው፣ ሰላምና መከባበር ይመጣል። ይሄንን የምለው በአለም ላይ ብዙ የታሪክ ሽሚያ ስለአለ ነው፡፡ የአፍሪካ ስልጣኔ ሲነሳ ግብጽ በቀዳሚነት ትጠቀሳለች፡፡ በቅርቡ ደግሞ ኢትዮጵያ የ10ሺ ዓመታት ታሪክ አላት የሚል መረጃ ተሰምቷል፡፡ ይሄ ነገር እንዴት ነው? በሁለት ደረጃ ነው የምናየው፡፡ ከሁለት መቶና ሶስት መቶ ዓመታት በፊት ፈረንጆቹ “አፍሪካ ታሪክ የላትም” ብለው ስለ ግብጽም ቢሆን ብዙ አይከታተሉም ነበር፡፡ ከናፖሊዮን ጊዜ ጀምሮ “ሮዜታ ስቶን” ተገኘና ስለግብጽ መማርና ማጥናት ጀመሩ፡፡ ስለ ግብጽ ብዙ ዕውቀት በዓለም ላይ ተበተነ፡፡ በጊዜው እንግሊዞች መጥተው ግብጽን አገኝዋት፡፡

እዛ ሳሉም ታሪኩን እያስፋፉ ሄዱ፡፡ በአሜሪካ ዩኒቨርስቲዎች አፍሪካ እንደውም ታሪክ የላትም ብለው ስለ እሷ አያጠኑም ነበር። በሌላ በኩል ታሪክ ያላቸውን እንደ ኢትዮጵያ ያሉትንም ራሳቸው ለማጥናት ነው የሚፈልጉት። ኢትዮጵያውያን ራሳችንን የምናከብር ሰዎች ነን፡፡ ቅኝ አልተገዛንም፡፡ በየዩኒቨርሲቲው በብዙ ሺ የሚቆጠሩ የኢትዮጵያ የግዕዝ ጽሕፈቶች አሉ፡፡ ግን ኢትዮጵያ ራሷን በአለም ላይ አላስተዋወቀችም፡፡ አሜሪካን አገር ፐብሊክ ሪሌሽንስ (ራስን ማስተዋወቅ) የሚባል ነገር አለ፡፡ በፐብሊክ ሪሌሺንስ እኛ ጐበዞች አይደለንም፡፡ ባህላችንም ስላልሆነ ይሆናል። በአንድ በኩል ቅኝ አልተገዛንም፡፡ በሌላ በኩል የራሳችን “ታሪክ አለን” ብለን ወርቅ ታሪካችንን ይዘን ቁጭ ብለናል፡፡ ኢትዮጵያ አለም ላይ እንድትተዋወቅ ከተፈለገ፣ ራስን የማስተዋወቅ ሥራ ያስፈልገናል። በመንግስትም በኩል ይሄ መጠናከር አለበት። በግልም ኢትዮጵያን ለማስተዋወቅ መጣር አለብን። በሃርቫርድ ለመጀመሪያ ጊዜ ስለ ኢትዮጵያ ሌክቸር የሰጠሁት እኔ ነኝ፡፡ ድሮ አይሰጥም ነበር፡፡ አስታውሳለሁ፤ በጃንሆይም ጊዜ እየመጣሁ እጣጣር ነበር፡፡ ግን ድጋፍ እንኳን የሚሰጠኝ አልነበረም፡፡ እስራኤል አገር ስሄድ ዩኒቨርስቲዎች ‹‹ይሄን ሌክቸር ስጥ›› እያሉ ይሻሙኛል፡፡ ኢትዮጵያ ስመጣ ግን ማንም አይጋብዘኝም፡፡ አሜሪካም ቢሆን በየቦታው ነው የምጋበዘው፡፡ ስለ አለም ታሪክ፤ ስለ አለም ሃይማኖት፤ ስለ አለም ቋንቋ ሌክቸር እንድሰጥ ይጋብዙኛል፡፡ ከ15 ዓመት በፊት አሜሪካ ኤምባሲ ዲፕሎማቶችን ጋብዘው፣ ስለ ኢትዮጵያ ባህል፣ ስለ መጽሐፈ ሔኖክ (እኔ በፃፍኩት ዙርያ) በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ሌክቸር ሰጥቻለሁ፡፡ በስልጣኔ ቀደምት ነን እንላለን፡፡

ነገር ግን ዓለም ይሄንን እምብዛም አያውቅልንም፡፡ ለምን ይመስልዎታል? ይሄ ፕሮፌሰሮችም የሚጠይቁት ጥያቄ ነው፡፡ በ1996 ዓ.ም ሀርቫርድ ዩኒቨርስቲ ውስጥ ነበር ስለ ኢትዮጵያ ማስተማር የጀመርኩት፡፡ ከአፍሪካ ቀደም ብሎ ጥናት የተጀመረው ኢትዮጵያ ውስጥ ነበር፡፡ ከአራት መቶ ዓመት አንስቶ ጀርመኖች ግዕዝ እያጠኑ፣ ስለ ኢትዮጵያ መመርመር ጀምረው ነበር፡፡ በመሃከል አውሮፓውያን አፍሪካን ቅኝ ሲገዙ፣ ኢትዮጵያ ቅኝ ሳትገዛ ቀረች፡፡ ያኔ ተዋት። ኢትዮጵያ ታሪኳ በተለይ ከቤተክርስቲያን ጋር የተያያዙ ሃይማኖታዊ ፅሁፎች ስላሉ የታወቀ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በ7 ቋንቋዎች ነው የተተረጐመው፣ አንዱ ግዕዝ ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ከመቶ ዓመት በፊት በተለያዩ የዓለም አገራት “ቼር ኦፍ ኢትዮጵያን ስተዲስ” ተቋቁመው ነበር፡፡ በኋላ አፍሪካን ቅኝ ሲገዙ፤ ስለ ሌላ አፍሪካ አገራት ማጥናት ጀመሩ። በተለይ ደግሞ ከ2ኛው የአለም ጦርነት በኋላ፣ የአፍሪካም ሁኔታ ሲለወጥ “ቼር ኦፍ ኢትዮጵያን ስተዲስ” የሚባሉት ተዘጉ፡፡ አሁን የሉም፡፡ ፓሪስም ለንደንም ይሄን ዘግተው አሁን ስለሌላ ነው የሚያጠኑት፡፡ ኢትዮጵያ ግን መሠረቱ ሃይለኛ ስለሆነ፣ ለጊዜው ያንቀላፋ ቢመስልም የሚነሳበት ጊዜ አለ። የኢትዮጵያ ታሪክ በገናናነት የሚታወቅበት ጊዜ ይመጣል፡፡ ይህንን ማድረግ የምንችለው ግን ዩኒቨርስቲያችን በምዕራብ አገራት ኢትዮጵያን ሲያስተዋውቅ ነው፡፡ ያኔ በየሙዚየሞቹ የኢትዮጵያ ሙዚየሞች ይፈጠራሉ፤ በየዩኒቨርሲቲዎቹ የኢትዮጵያ ታሪክ ይጠናል፤ ይታወቃል፡፡ የኢትዮጵያን መጪ ዘመን እንዴት ይገልፁታል? ለዚህች አገር እርስ በርስ መጋጨትና መዘላለፍ አይጠቅማትም፤ ፍቅር ነው የሚያስፈልጋት፡፡ አንዳንዴ በጣም ልቤን የሚያሳምመኝ… በኢንተርኔት የሚሰዳደቡት ነገር ነው፡፡ ይሄ መቅረት አለበት፡፡ ያለችውን ሰላም ማጠንከር አለብን፡፡

የኦነግ ግሩፕ አለ፡፡ የኦጋዴን ግሩፕ አለ… ሌሎቹም በቡድን በቡድን ተደራጅተዋል፡፡ እነዚህ ቡድኖች በሰላም ወደአገራቸው ተመልሰው ለአገራቸው እድገት መትጋት አለባቸው፡፡ ግጭትና ጠባችንን ብንተው እኮ ጉልበታችንን ለሚጠቅም ነገር እናውለው ነበር፡፡ አንድ ጠርሙስ ቤኒዚን ቢሰጠን፣ ያን ቤንዚን መኪና ውስጥ ጨምረን ብዙ ማይልስ መንዳት እንችላለን። ወይም ደግሞ እሳት ጭረን ልናቃጥለውም እንችላለን፡፡ እኛ ብዙ ጊዜ ጉልበታችንን እንደዛ ነው የምናቃጥለው፡፡ ጉልበታችንን በፍቅር፣ በሠላም፣ በስራ ላይ አናውለውም፡፡ እሱን ማድረግ አለብን። መወያየት፤ መደማመጥ አለብን፡፡ እኔ አውቃለሁ የምንለው ነገር የትም አያደርስም፡፡ ሶቅራጠስ “ብዙ ባወቅሁ ቁጥር አለማወቄን ነው ያወቅሁት” ብሏል፡፡ እኔ ራሴ ወጣት እያለሁ ብዙ ነገር አውቃለሁ እል ነበር፡፡ ሰው እያደገ፣ እያወቀ ሲሄድ ግን ገና ብዙ እንደሚቀረው እየተረዳ ይመጣል፡፡ ስለ ኢትዮጵያ የትምህርት ሁኔታ ምን ይላሉ? የእኛ ዩኒቨርስቲዎች በኢትዮጵያ ትምህርት አልጠነከሩም፡፡ የኢትዮጵያ ትምህርት መስፋፋት አለበት፡፡ በደቡብ፣ በሰሜን፣ በምዕራብ፣ በምስራቅ ያለው ህዝብ ሁሉ ታሪክ አለው፡፡ በግሪክ የጥበብ ሁሉ መጀመሪያ ራስን ማወቅ ነው ይባላል፡፡ የ10ሺ ዓመት ታሪክ የምንለው በአለም ጐልቶ እንዲታይ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

ዩኒቨርሲቲው የግዕዝ ዲፓርትመንት ያስፈልገዋል …ራሱን የቻለ ከፍ ያለ ትልቅ ሙዚየም ብናዘጋጅ፣ ይህንን አይተው የውጭ ጐብኝዎች ይሳባሉ፡፡ በተለያዩ የዓለም አገራት ዞረዋል፡፡ በእንግሊዝ ሙዚየም በርካታ የኢትዮጵያ ቅርሶች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ በሌሎች አገራትስ? ከአውስትራሊያ በቀር ሌላውን ዓለም ሁሉ አዳርሻለሁ፡፡ በእንግሊዝ አገር ሙዚየም ውስጥ አንድ ሺ ያህል የግዕዝ መፃህፍት አሉ፤ በአፄ ቴዎድሮስ ዘመን የተወሰዱ፡፡ በፓሪስም ወደ 2ሺ የሚሆኑ የግዕዝ መፃህፍቶች አሉ፡፡ በቫቲካን (ሮም) ውስጥ ወደ 2ሺ የሚሆኑ አሉ፡፡ እኔ ራሴ ሁለት ካታሎግ ጽፌያለሁ፡፡ አሜሪካ ውስጥ በየዩኒቨርሲቲው 500 የሚሆኑ የግዕዝ መፃሕፍት አግኝቻለሁ፡፡ ወደ 15 በሚሆኑ ዩኒቨርስቲዎች ማለት ነው፡፡ ዩኒቨርስቲዎቹ የግዕዝ መፃሕፍትን ለምንድነው የሚፈልጓቸው? እንደ ጌጥ ነው የሚቆጥሩት፡፡ ማንስክሪፕት አለን ብለው ያስቀምጡታል፡፡ ዋጋው ደግሞ ከፍተኛ ነው። በደርግ ጊዜ ብዙ መፃሕፍት ወደ ውጭ ወጥተዋል፡፡ አንድ ጊዜ አንድ ሰውዬ የግዕዝ መጽሐፍት ይዞ መጣ እና አየሁት፤ በጣም ድንቅ ነው፡፡ “ምን ልታደርገው ነው?” ብዬ ስጠይቀው “ሙዚየም አለኝ፤ እሸጠዋለሁ” አለኝ፡፡ “በስንት ብር ነው የምትሸጠው?” አልኩት፡፡ “250ሺ ዶላር” አለ፡፡ አያሳዝንም፡፡ ከኢትዮጵያ አውጥተው እኮ ነው፡፡ አንድ ሰውዬ ደግሞ ከዚህ መጽሐፈ ሄኖክን አምጥቶ ሸጧል አሉ፡፡ ኢትዮጵያ እነዚህ ቅርሶችዋ እንዲመለሱላት መጣጣር አለብን፡፡ ባይመለሱ ደግሞ ጥናቱ እንዲስፋፋ ማድረግ ይኖርብናል፡፡ እንቅስቃሴውን እንደዚህ ነው መጀመር ያለብን፡፡

በአሜሪካ ግዕዝን የሚያስተምሩ ዩኒቨርስቲዎች የትኞቹ ናቸው? እኔ ራሴ ግዕዝን ሃርቫርድ፣ ፕሪንስተን ዩኒቨርስቲ ኦፍ ፔኒስላቫንያ አስተምሬያለሁ፡፡ ግዕዝ እኮ የታወቀና የተከበረ ትምህርት ነው፡፡ እስራኤልም በየዩኒቨርስቲው በደንብ ያስተምራሉ፡፡ ግዕዝ፤ ከታላላቆቹ የግሪክና የላቲን ቋንቋዎች እኩል ነው የሚታየው፡፡ እኛ እኮ ነን ዋጋውን የማናውቀው፤ ሌሎቹማ ያውቃሉ፡፡ የኢትዮጵያን የጥንት ሥልጣኔና አሁን ያለችበትን ሁኔታ እንዴት ይገልፁታል? ከ1ሺ 5 መቶ ዓመት በፊት ከሮቆፒያንስ የሚባል የግሪክ ፀሐፊ፤ ከዓለም ሶስት ታላላቅ መንግስታት አንዷ ኢትዮጵያ መሆኗን ጠቅሶ ነበር፡፡ ሁለቱ ሮማና ፐርሺያ ናቸው፡፡ ያን ጊዜ ኢትዮጵያ በዚያ ደረጃ ላይ ነበረች፤ ከአለም ታላላቅ መንግሥታት አንዷ፡፡ አሁንም በጥቁር ህዝብ ዘንድ ትልቅ ተስፋ አለ፤ ኢትዮጵያ ትልቅ አገር ሆና እንደምትነሳ፡፡ ያንን ለማድረግ ህዝባችን በፍቅርና በሰላም መንግስቱን እያከበረ፣ መንግስትም ህዝቡን እያከበረ አብሮ የመስራት መንፈስ መፈጠር አለበት፡፡ ለእኔ ኢትዮጵያ ቁጭ ብላለች እንጂ ወደኋላ አልተመለሰችም (ሳቅ) አሁን ደግሞ የማደግ፤ የመመንደግ ዕምቅ አቅም አላት፡፡ የኢትዮጵያን ታሪካዊ ቦታዎች ለመጐብኘት በቂ ጊዜ አግኝተዋል? አዎ፡፡ ሁሉንም ጐብኝቻለሁ፡፡ ግዕዝ ለ2 ዓመት ተምሬያለሁ፡፡ ቅኔም ትንሽ ጊዜ ተምሬያለሁ፡፡ ያልሄድኩበት አገር የለም፡፡ በተለይ በሰሜን በኩል ደብረ ሊባኖስ፣ ላሊበላ፣ አክሱም፣ ወዘተ…ብዙ ገደማትን ዞሬአለሁ፡፡ ዶክትሬቴን የሰራሁት ስለ መጽሐፈ ብርሃን ነው፤ በአፄ ዘርያቆብ ዘመን የተፃፈ ነው፤ በውጭ አገር ታትሟል፡፡

Read 5922 times