Saturday, 28 December 2013 11:17

የ5 ዓመት ህፃን ከት/ቤት ፎቅ ወድቃ ሞተች

Written by  ማህሌት ፋሲል
Rate this item
(8 votes)

አራት የት/ቤቱ ሰራተኞች ከስራ ታግደዋል

             የምሥራቅ ጮራ መዋለ ህፃናትና አንደኛ ደረጃ ት/ቤት የመዋዕለ ህፃናት ተማሪ የነበረችው የ5 ዓመቷ ህፃን ሳባህ አማን ከት/ቤቱ 3ኛ ፎቅ ላይ ወድቃ፣ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል በህክምና ስትረዳ ቆይታ በአራተኛ ቀኗ ባለፈው እሁድ ህይወቷ አልፏል፡፡ ጉሊት በመነገድ ከሚተዳደሩ አክስቷና ከ12ኛ ክፍል ተማሪ እህቷ ጋር ትኖር የነበረችው ሕፃን በአሁኑ ዓመት ነበር ትምህርት ቤት የገባችው፡፡ ለብቻው ከተከለለው መዋዕለ ህፃናት እንዴት ወደ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ገብታ፣ ከፎቅ ላይ እንደወደቀች እንደማያውቁ የተናገሩት ቤተሰቦች፤ ህፃኗን ስትወድቅ ማንም እንዳልነበረና የትምህርት ቤቱ የካፍቴሪያ ሰራተኛ መሬት ላይ ወድቃ እንዳገኛት ጠቁመዋል፡፡ ልጅቷ ስትወድቅ እንዴት አስተማሪዎች ወይም ሞግዚቶች እንዳላዩ ት/ቤቱን መጠየቃቸውን የገለፁት ቤተሰቦች፤ ከት/ቤቱ “ስብስባ ላይ ነበርን” የሚል ምላሽ ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡ የምስራቅ ጮራ ት/ቤት ርእሰ መምሕር አቶ ስንታየሁ አንሺሱ ስለ አደጋው ሲናገሩ፤ “ሳምንታዊ ስብሰባ የምናደርግበት ቀን ስለነበር አጠቃላይ የት/ቤቱ መምህራንና ሰራተኞች ተሰብስበን ሳለ ከቀኑ 9፡40 ላይ አንዲት ተማሪ ከፎቅ ወድቃለች ተባልን።

ወዲያው ህፃኗን አንስተን ወደ ምግባረ ሰናይ ሆስፒታል ወሰድናትና ወደ ጥቁር አንበሳ ላኩን። እዚያም ከፍለን አሳከምናት” ብለዋል፡፡ ሆኖም ህፃኗ በወደቀች አራተኛ ቀኗ ህይወቷ አልፏል፡፡ ህፃኗ እንዴት ትምህርት ቤት ውስጥ ለብቻዋ እንደቀረች የተጠየቁት ርዕሰ መምህሩ፤ ብቻውን እንዳልነበረችና 5 ህፃናት አብረዋት እንደነበሩ ተናግረዋል፡፡ ህፃናቱን ለብቻቸው ትተው ስብሰባ መግባታቸው አግባብ ነው ወይ ተብለው የተጠየቁት አቶ ስንታየሁ፤ ወላጆች ልጆቻቸውን በጊዜ እንዲወስዱ ማስታወቂያ መለጠፋቸውንና በቃልም መንገራቸውን ገልፀዋል፡፡ በህፃኗ ላይ ለደረሰው የሞት አደጋ ተጠቂው ማን እንደሆነና የተወሰደ እርምጃ ስለመኖሩ የተጠየቁት የት/ቤቱ ርዕሰ መምህር፤ “ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸውን አራት ሰራተኞች ከስራ አግደናል፤ ሁለት ሞግዚቶችና ሁለት ጥበቃዎች ደግሞ ጉዳያቸው በዲሲፕሊን ኮሚቴ እየተጣራ ነው” ብለዋል፡፡

ት/ቤቱ ለቀብር 2500 ብር ብቻ እንደሰጣቸው የገለፁት የሟች ቤተሰብ፣ ት/ቤቱ ካሣ እንዲከፍላቸው ጠይቀዋል፡፡ የት/ቤቱ ርዕሰ መምህር በበኩላቸው፤ ት/ቤቱ የመንግስት እንደሆነና ካሣ ለመክፈል ጉዳዩ በህግ መያዝ እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ “እስከዚያው ግን ክፍለከተማን አናግረን፣ በየካ ክፍለ ከተማ ባሉ ት/ቤቶች እየዞርን መዋጮ ለመሰብሰብ አስበናል” ብለዋል፡፡ ይሄ በእንዲህ እንዳለ የአዲስ አበባ ፖሊስ የህፃኗን አሟሟት በመመመርመር ላይ እንዳለ ለማወቅ ችለናል፡፡

Read 3650 times