ታዳጊው አምበሴ አስቻለው ሰው ለመግደል በማሠብ ተበዳይን ደረቱ ላይ ስድስት ቦታዎች ላይ በጩቤ በመውጋት የቀኝ ሳምባው ላይ የደም መፍሰስ ጉዳት እንዲደርስበት በማድረጉ በፈፀመው ተራ የሆነ የሰው ግድያ ወንጀል ሙከራ መከሠሡን የአቃቢ ህግ የክስ ዝርዝር ያስረዳል፡፡ ድርጊቱ የተፈፀመው ጳጉሜ 5 ቀን 2004 ዓ.ም ከምሽቱ 3 ሰዓት ሲሆን ቦታውም ልደታ ክ/ከተማ ቀበሌ 31 ልዩ ቦታው ቆጨ ሠፈር ነው፡፡ በአቃቤ ህግ የክስ ዝርዝር ለወንጀሉ ምክንያት የሆነው ፍሬ ሐሳብ ባይገለፅም ታዳጊው ሰው ለመግደል አስቦ የፈፀመው ነው ተብሏል፡፡ ሠሞኑን የዋለው የከፍተኛው ፍ/ቤት ልደታ ምድብ ችሎት 11ኛው ችሎት ተከሳሹ ከዚህ በፊት ወንጀል ፈፅሞ የማያውቅ መሆኑንና ዕድሜው 16 ዓመት መሆኑን ከግምት በማስገባት በ12 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣ ወስኗል፡፡ ከተፈታ በኋላም ለ2 ዓመታት ከህዝባዊ መብቱ እንዲታገድም ታዟል፡፡