Saturday, 21 December 2013 12:27

ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችን በማሰር ከዓለም 2ኛ ሆነች

Written by  ማህሌት ፋሲል
Rate this item
(6 votes)

መቀመጫውን በኒዮርክ ያደረገው የጋዜጠኞች መብት ተቆርቋሪ ቡድኑ /CPJ/  ባለፈው ረቡዕ  ይፋ ባደረገው ሪፖርት፤ ጋዜጠኞችን በማሰር ከአለም አስር አገሮች መካከል ኢትዮጵያን በሁለተኛ ደረጃ ያስቀመጠ ሲሆን ኤርትራ ቀዳሚ ሆና፣ ግብፅ በሶስተኝነት ተቀምጣለች፡፡
ሲፔጂ 34 አፍሪካዊ ጋዜጠኞች በሰሜንና ምስራቅ አፍሪካ በእስር ላይ እንደሚገኙ የገለፀው ሲፒጄ፤ በኢትዮጵያ ሰባት ጋዜጠኞች በጻፉት ጽሑፍ ሣይሆን “አሸባሪ” ተብለው በእስር ላይ እንደሚገኙ ጠቁሟል፡፡
አለም አቀፍ የመብት ቡድን (Global rights group) የተባለው ተቋም በበኩሉ፤ የኢትዮጵያ መንግስት ጋዜጠኞቹን ያሰራቸው ሚዲያውን ዝም ለማሰኘት ስለሚፈልግ ነው ብሏል። በኤርትራ 22 ጋዜጠኞች በእስር ላይ እንደሚገኙና አንዳቸውም ፍርድ ቤት እንዳልቀረቡ የገለፀው ሲፒጄ፤ እስረኞቹን በተመለከተ ከኤርትራ መንግስት ምንም አይነት መረጃ ለማግኘት እንደተቸገረ ጠቁሟል፡፡ ጋዜጠኞችን በማሰር የ3ኛ ደረጃን በያዘችው ግብፅም ጋዜጠኞች መታሰር የጀመሩት ፕሬዚዳንት መሀመድ ሙርሲ ወደ ስልጣን ከመጡበት ቀን ጀምሮ ነው ብሏል ሲፒጄ፡፡ የሰሜን ምስራቅ አፍሪካ ጋዜጠኞች ተወካይ ቶም ሮዲስ በናይሮቢ ለCPJ እንደተናገረው፤ በአፍሪካ ቀንድ አገራት የተለያዩ ችግሮች እንዳሉና መንግስታት ስለ ችግሩ መወያየት እንደማይፈልጉ ገልጿል፡፡ ሲፒጄ ጋዜጠኞችን በማሰር ቀዳሚዎቹ 10 አገራት በሚል ከዘረዘራቸው መካከል ቬትናም፣ ሶሪያ፣ ፓኪስታንና ቤልጂየም ይገኙበታል፡፡

Read 2460 times