Print this page
Saturday, 21 December 2013 12:17

አርቲስት ዳንኤል ተገኝ ኢትዮፒካሊንክንና አንዲት ግለሰብን ከሰሰ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(5 votes)

“ለሁለቱም እኩል ጊዜ ነው የሰጠነው፤ መካሰሳችንን ከአንቺ ነው የሰማነው” ኢትዮፒካሊንክ
“በስም ማጥፋት ሊከሰኝ የሚችልበት የህግ አግባብ የለም” - ወ/ሮ ቤተልሄም አበበ


በተለያዩ ፊልሞች፣ የመድረክ ድራማዎችና በተለይም በ “ገመና” አንድ ድራማ ላይ የዶ/ር ምስክርን ገፀ ባህሪ ወክሎ በመጫወት ተወዳጅነትን ያተረፈው አርቲስት ዳንኤል ተገኝ፤ “የስም ማጥፋት ዘመቻ ከፍተውብኛል” በሚል በኢትዮፒካሊንክ የሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጆች እና ወ/ሮ ቤተልሄም አበበ በተባሉ ባለሀብት ላይ ክስ መመስረቱን ለአዲስ አድማስ ገለፀ፡፡
“የዛሬ ሳምንት ምሽት ላይ ወ/ሮ ቤተልሄም አበበ፤ እኔን በሚመለከት በኢትዮፒካሊንክ ፕሮግራም ላይ ከፍተኛ የስም ማጥፋት ዘመቻ ሲያካሂዱ ነበር” ያለው አርቲስት ዳንኤል፤ ለዚህ ዘመቻቸው የኢትዮፒካሊንክ አዘጋጆች 15 ቀን ያህል ጊዜ ሲሰጡዋቸው፣ ለእኔ ግን ወደስቱዲዮ ሊገቡ ጥቂት ሰዓታት ብቻ ሲቀራቸው ደውለው፣ ስሜ ለጠፋበት ጉዳይ ምላሽ እንዳልሰጥ አድርገውኛል፤ በዚህም ክስ መስርቼባቸዋለሁ ብሏል፡፡
ከኢትዮፒካሊንክ ፕሮግራም አዘጋጆች አንዱ የሆነው ጋዜጠኛ ግዛቸው እሸቱን በጉዳዩ ዙሪያ አነጋግረነው በሰጠው ምላሽ፤ ለቅሬታ አቅራቢዋም ሆነ ለአርቲስቱ እኩል እድል ሰጥተናቸዋል፣ መከሰሳችንን ግን ገና ከአንቺ መስማቴ ነው ብሏል፡፡
ግንቦት 17 ቀን 2003 ዓ.ም በማስታወቂያ ድርጅቴ እና በካም ግሎባል ፒክቸርስ አማካኝነት ከአርቲስት ሀረገወይን አሰፋ ጋር “ፋየር ፕሩቭ” የተሰኘ የውጭ ፊልም ወደ አማርኛ መልሼ ለመስራት  ጀምሬ ነበር” ያለው አርቲስቱ፤ ይህን ፊልም በመሪ ተዋናይነት ከሀረገወይን ጋር ለመስራት ስምንት የፊልሙ ክፍሎች መቀረፃቸውን አርቲስቱ ይናገራል፡፡ በወቅቱ “የሴም ወርቅ” የተሰኘ ፊልም እየሰራ እንደነበር የተናገረው አርቲስቱ፤ በመሀል “ፋየርፕሩቭን”  መቅረጽ ያስፈለገበት ምክንያት አርቲስት ሀረገወይን ነፍሰጡር ስለነበረች፣ ከመውለዷ በፊት ትክክለኛውን እርግዝና ለመቅረጽ እንደሆነ ገልጿል፡፡
ከዚህ በኋላ ጐንደር ቀረፃ ላይ እንዳለ በተደጋጋሚ ወ/ሮ ቤተልሔም መደወላቸውን፣ ስልኩን ባለማወቁና ስራ ላይ ስለነበር እንዳላነሳው የገለፀው አርቲስት ዳንኤል፤ ከ20 ቀን በኋላ አዲስ አበባ እንደተመለሰ ይሄው ስልክ በድጋሚ መደወሉንና ማንሳቱን አስታውሶ፤ “አብረን ፊልም እንድንሰራ እፈልጋለሁ” የሚል ጥያቄ ማቅረባቸውን ገልጿል፡፡
“ስክሪፕት ስጭኝና አይቼ እወስናለሁ የሚል ምላሽ ሰጠሁ” ያለው አርቲስቱ፤ ወ/ሮ ቤተልሄም ስለ ፊልሙ ስክሪፕብት አንዳንድ ነገሮችን ሲነግሩኝ፤ እኔ ስምንት ክፍል የቀረጽኩት “ፋየር ፕሩቭ” መሆኑን አወቅሁኝ ሲል ገልጿል፡፡
“ወይ እኔ ልስራ አለበለዚያ እናንተ ስሩት” ብያቸው ነበር ያለው አርቲስት ዳንኤል፤ “አብረን እንስራው” በሚል ስምምነት ላይ መድረሳቸውንና  “በኋላ ግን ወ/ሮ ቤተልሄም፤ በስራዬ ጣልቃ እየገቡና የስነ ምግባር ጉድለት እያሳዩ በመምጣታቸው ስራዬን ለማቆም ተገድጄያለሁ” ያለው አርቲስቱ፤ ይህን ስላደረግሁ በሚዲያ ስሜን የማጥፋት ዘመቻ ተከፍቶብኛል፤ ጉዳዩንም ወደ ህግ ወስጄው ህግ ይዞታል ብሏል፡፡
“እስከዛሬ የወ/ሮ ቤተልሄም ቤተሰብና ማህበራዊ ግንኙነት እንዳይረበሽ በሚል ብዙ ምስጢሮችን ይዤ ቆይቻለሁ” ያለው አርቲስቱ፤ በህግ የያዘው ጉዳይ ሲፈፀም ምስጢሮቹን ይፋ እንደሚያደርግ ተናግሯል፡፡
ኢትዮፒካሊንክን የከሰሰበትን ምክንያት የተጠየቀው አርቲስቱ፤ “ኢትዮፒካሊንክ የእኔን ስም በየደቂቃው ሲጠሩ፣ የወ/ሮ ቤተልሄምን ስም ላለመጥራት ጥንቃቄ ሲያደርጉ አስተውያለሁ፤  ይህም ሚዲያውን እኩል እንደማያገለግሉበት ያሳያል” በማለት መልሷል፡፡
ጋዜጠኛ ግዛቸው በበኩሉ፤ “ቅሬታዎቹ አግባብ አይደሉም፤ ስቱዲዮ ገብቶ ምላሽ ሰጥቷል፡፡ እኛም መረጃዎችን የምናጣራው በራሳችን መንገድ ነው ለሁለቱም እኩል ዕድል ሰጥተናል፤ በህግ ክፍላችን በኩልም ያሰራል አያሰራም የሚለውን ለማጣራት ሞክረናል” ሲል ገልጿል፡፡ “እንደውም በሰባት አመት የስራ ጊዜያችን ያላደረግነውን፣ እሱ ምላሽ መስጠት ስላለበት አድርገናል” ብሏል፤ ጋዜጠኛ ግዛቸው፡፡
የቅሬታ አቅራቢዋን ስም አልጠቀሱም የተባለውን በተመለከተ ሲመልስም፤ “የግለሰቧ ስም ይነሳ አይነሳ አላስታውስም፤ ያም ቢሆን የውስጥ አዋቂ ዋና አላማው የታዋቂ ሰዎች ጉዳይ ስለሆነ የእርሱን ስም ጠቅሰናል” ብሏል፤ ጋዜጠኛ፡፡
በጉዳዩ ላይ ያነጋገርናቸው ወ/ሮ ቤተልሔም አበበ በበኩላቸው፤ “እኛ ስሙን አላጠፋንም፤ በስም ማጥፋት ሊከሰን የሚችልበት የህግ አግባብ የለም” ካሉ በኋላ “ገንዘብ ወስዷል፤ ለዚህም ማስረጃ ስላለን ካራማራ ፖሊስ ከሰነዋል፤ ቀሪውን በጠበቃዬ በኩል አጣሩ” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡  

Read 6284 times