Print this page
Saturday, 14 December 2013 13:41

ከተማዋን የጐበዝ አለቆች እየተቀራመቷት ነው!

Written by 
Rate this item
(11 votes)

“የጐበዝ አለቃ” እሽ ያለውን በፈቃዱ፣ እምቢ ያለውን በግድ የሚገዛ ወንዝ አፍራሽ ገዥ ነው። የጐበዝ አለቃ የመሰለውን ይፈርዳል እንጂ ሕግ የሚባል ነገር አይገባውም፤ ወይም ለሕግና ሥርዓት ደንታ የለውም፡፡
የጐበዝ አለቆች ብዙውን ጊዜ የሚከሰቱት የመንግሥት አቅም ሲላላ ወይም “መንግሥት የለም” ብለው ሲያምኑ ነው፡፡ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ማይጨው ላይ ሠራዊታቸውን ለነጭ አሞራ በትነው ወደ እስራኤል ቀጥሎም ወደ እንግሊዝ የሄዱ ጊዜ የተከሰተውን ማንሳት ለርዕሰ ጉዳያችን ጥሩ ምሳሌ ሊሆን ይችላል። ንጉሡ በመሸሻቸው አገሪቱ ያለ መሪ ቀረች፤ በአንጻሩ ጣሊያኖች ፋሽስታዊ ቅጣታቸውን በወታደሩ ላይ ብቻ ሳይሆን በህፃናትና ሴቶች፣ በመነኮሳትና እንስሳት ላይ ሳይቀር እየፈፀሙ በማስቸገራቸው ህዝቡ ተቃውሞውን ለመግለጽ መደራጀት ነበረበት፡፡ ግን የሚያደራጀውም ሆነ የተደራጀ አካል በማጣቱ የሚያስተባብሩትን የጐበዝ አለቆች መፈለግ ነበረበት፡፡ ስለሆነም በጊዜው ጉልበት ያለው ሁሉ የጐበዝ አለቃ ሆነ፡፡ በላይ ዘለቀ፣ አበበ አረጋይ፣ ገርሱ ዱኪ፣ ወዘተ የጐበዝ አለቆች ነበሩ። እንዲያውም አበበ አረጋይንማ “ራስ” የሚል ማዕረግ ያስገኘላቸው የጐበዝ አለቅነታቸው ነው፡፡
በጣሊያን ጊዜ የነበሩ የጐበዝ አለቆች ዓላማቸው ኢትዮጵያን ከፋሽስት መንጋጋ ማላቀቅ ነበር። የተሳካ እንቅስቃሴ በማድረጋቸውም ከአምስት ዓመት የሞት ሽረት ትግል በኋላ ንጉሡን ለዘውድ አብቅተዋል። በ1960 ዓ.ም ጐጃም ላይ ተከስቶ የነበረውን ህዝባዊ አመጽ የመራውም “ባምላኩ አየለ” ወይም በፈረስ ስሙ “ባምላኩ አባ ግዮን” የሚባል የጐበዝ አለቃ ነበር፡፡
ባምላኩ አባ ግዮን የሚመራው የገበሬ ጦር፣ መላ ጐጃምን ለጊዜውም ቢሆን ከንጉሡ አገዛዝ ነፃ ማውጣት ችሎ ነበር፤ ለአመጽ ምክንያት የነበረውን የብር ከሃምሳ ተጨማሪ ግብርም በጉልበቱ አስነስቷል፡፡ በትግራይም “የቀደማይ ወያኔ” አመጽ የተመራው በጐበዝ አለቆች ነው። የኃይለ ሥላሴን ሥርዓት ያንኮታከቱትም ከየወታደሩ ክፍል በጉልበት የተሰባሰቡ የጐበዝ አለቆች ናቸው፡፡ ዙሩ ሲደርስ ደርግን ራሱን የጣሉትም የኢህአዴግ የጐበዝ አለቆች ናቸው፡፡
ወያላዎች የጐበዝ አለቆች ሆነዋል
የከተማዋን የታክሲ ስምሪት ሥርዓት ለማስያዝ ሲባል የትራንስፖርት ባለስልጣኑ መሥመር አመልካች ጽሑፎች (ታፔላ) በየታክሲው አናት ላይ እንዲለጠፍ ወስኖ ነበር፤ እሱን ተግባራዊ ለማድረግም ብዙ ጊዜ አምጦበታል፡፡ ግን እርምጃው የመጓጓዣ ችግሩን ከመፍታት ይልቅ ይበልጥ አወሳሰበውና ህዝቡን ቁምስቅሉን ያሳየው ጀመር፡፡
በከተማዋ ትራንስፖርት ባለሥልጣን እርምጃ የተበሳጩት ወያላዎች፤ ከህዝቡ ትከሻ ላይ ፊጥ አሉና ሲፈልጉ ለሁለት ሰው በተዘጋጀ ወንበር ላይ “ጠጋ በል” እያሉ ሶስትና አራት ተሳፋሪ እንደ ቂጣ እየደራረቡ ያሰቃዩታል፤ ሲያሻቸውም ትራንስፖርት ባለሥልጣኑ ካወጣው ታሪፍ በላይ ይወስኑበታል። የጐበዝ አለቆችን ውሳኔ የሚጥስ ካለ፣ ክብሩንም ገንዘቡንም አጥቶ ተዋርዶና ተደብድቦ መግባት ግድ ሆኖበታል፡፡
ሰሞኑን ያጋጠመኝን ልጥቀስ፤ ከታህሳስ አንድ ጀምሮ መንግሥት “መጠነኛ ማስተካከያ አድርጌያለሁ” ያለውን ዋጋ፣ ህዳር 30 ምሽት በቴሌቪዥን ቁጭ ብዬ አስተውያለሁ፡፡ በ “መጠነኛ” ማስተካከያው መሠረት 1.40 የነበረው ወደ 1.45፤ 2፡70 የነበረው ወደ 2፡80 ማደጉ ገርሞኝ፣ ጥዋት ከመገናኛ ወደ ካዛንችስ ታክሲ ከተሳፈርን በኋላ (ያውም በሰልፍ መከራ አይተን) የጐበዝ አለቃው “ዋጋው አራት ብር ነው” የሚል አዋጅ በኩራት አሰማን፡፡ “እንዴ! ማታኮ በቴሌቪዥን 2.80 ተብሏል፤ እንዴት? ከየት የመጣ አራት ብር ነው?” ብለን ሁላችንም ስንጮህ “የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ታክሲ ይግዛላችሁ” አለን የጐበዝ አለቃው፡፡
የወያላው ሳይንስ ሹፌሩም ዳር ይዞ ቆመና “ከፈለጋችሁ ክሰሱ፤ መውረድ ትችላላችሁ፤ ጥሩንባ ሁሉ” አለና ታክሲ ሙሉ ሰው ዳቦ በቀደደ አፉ መዘርጠጥ ጀመረ፡፡ ሌላ የጐበዝ አለቃ ተጨማረ ማለት ነው፡፡ በወቅቱ የነበረው ምሬትና ሃዘን እንዲህ በቀላሉ የሚገለጽ አይደለም፡፡ ከሁሉ ትዝ የሚለኝና የገረመኝ አንዲት ወይዘሮ የተናገሩት ነው፡፡ “መክሰስ አለብን ትራፊክ ፖሊስ? እንሂድ፤ የለም ትራንስፖርት ባለሥልጣን ይሻላል ወደዚያ እንሂድ” የሚሉ ሰዎች ስለነበሩ ወይዘሮዋ ምን አሉ መሰላችሁ? “ሚስት አረገዘች? ብሎ ጓደኛውን ቢጠይቀው “ማንን ወንድ ብላ?” አለው ይባላል፡፡ ለመሆኑ መንግሥት ቢኖር ቂጡን ያልጠረገ ውርጋጥ መቀለጃ እንሆን ነበር?” ሲሉ እንባቸውን በነጠላቸው ጫፍ ጠራረጉ፡፡ እውነት ለመናገር የሴትዮዋ አባባል ልክ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ምክንያቱም ትንሹን ወያላ መቆጣጠር ካልቻለ እንዴት ነው ሌሎች ከባድ ወንጀሎችን በመቋቋም ህዝቡን ከስጋትና ከዝርፊያ መታደግ የሚችለው?
አሁን እየባሰበት የመጣው ሌላው ጉዳይ ደግሞ የእነዚህ የጐበዝ አለቆች የሥምሪት መስመር ነው “ከካዛንችስ በአራት ኪሎ ፒያሳ” የሚል ጽሑፍ ለጥፎ “ፒያሳ በአቋራጭ!” ይላል፡፡ በአራት ኪሎ ሂድ ሲባልም በፍጹም በእጅ አይልም፡፡ ይህ የአቋራጭ መንገድ በአቋራጭ ለመክበር እንጂ በአቋራጭ ህዝብን ለማገልገል እንዳልሆነ ግን ግልጽ ነው፡፡ ይህንንም የትራንስፖርት ባለሥልጣኑ መቆጣጠር አልቻለም፤ የትራፊክ ፖሊሶችም እያዩ ትንፍሽ አይሉም፡፡ የህዝብን ችግር የማይፈቱ ከሆነ ትራንስፖርት ባለሥልጣንና ሰራተኞቹ ለምን ያስፈልጋሉ? የትራንስፖርት ዘርፉ የሚመራውኮ በእነሱ ሳይሆን በጐበዝ አለቆች ነው፡፡
“ተራ አስከባሪ” የሚባሉትም ሌሎች የጐበዝ አለቆች ናቸው፡፡ ከታክሲ ሹፌሮች ጋር በመሞዳሞድ ሕዝቡን ቁም ስቅል ያሳያሉ እንጂ ለህዝቡ የፈየዱት ነገር የለም፡፡ ቀድሞ ነገር የሰውን ነው የመኪናውን ተራ የሚያስጠብቁት? የቱ መኪና ገዝቶ ነው ተራ የሚያስጠብቁት? መላ የጠፋው ተቋም!
መንገድ ጠራጊዎች የጐበዝ አለቆች ናቸው
መንገዱም ሆነ ሌላው ነገር የሚፀዳው ለህዝቡ ጤንነት ሲባል ነው፡፡ ባህርዳር፣ አዋሳም ሆነ ሌሎች የአገራችንና የውጭ አገር ከተሞች መንገዶች የሚፀዱት ህዝቡ እንቅስቃሴ ሳይጀምር ንጋት ላይ ነው፡፡ አዲስ አበባ ግን “ጽዳቱ” የሚጀመረው ነዋሪው ሥራ ለመግባት ሲጣደፍ ነው፡፡ በተለይ ደግሞ ህዝቡ የታክሲ ወረፋ ለመያዝ ረጅም ሰልፍ ይዞ ካዩት፣ ወይም ንፁህ የለበሰ ካዩ ቅናት ያለባቸው ይመስል አስፋልት ላይ የነበረውን አቧራ አንስተው ይከምሩበታል፡፡
“ለምን እንዲህ አረጋችሁ?” የሚላቸው አካልም የለም፤ በድርጊታቸው የተበሳጨ ሰው አቧራውን ከልብሱና ከሰውነቱ ላይ እያራገፈ “ለምን እንዲህ ታረጋላችሁ?” የሚል ጥያቄ ሲያቀርብላቸውም መልሳቸው የሰሌን መጥረጊያ ሊሆን ይችላል፡፡
ለመሆኑ መንገዱ የሚጠረገው ለማን ጤንነት ታስቦ ነው? ለነዋሪው ነው? ወይስ ለአስፋልቱ ታስቦለት መንገድ ጠራጊ የጐበዝ አለቆችና ኃላፊዎቻቸው (ምን አልባት ካላችሁ) እባካችሁ የጽዳት ዓላማ ይግባችሁ፡፡ መንገድ የምትጠርጉት ለነዋሪው ጤና እንጂ ለአስፋልቱ ታስቦ አይደለም፡፡
መብራት ኃይልና ቴሌም ሌሎች የጐበዝ አለቆች ናቸው
መብራት ኃይልና ቴሌ በህግ የተቋቋሙ የመንግሥት አካላት ቢሆኑም ከመንግሥት አፈንግጠው የራሳቸውን ደሴት ፈጥረዋል።  በህጋዊነት ኃላፊነታቸውን ከመወጣት ይልቅ የጐበዝ አለቅነትን የመረጡ መስለዋል፤ ያለምንም ማስጠንቀቂያ አገልግሎት ያቋርጣሉ፤ ለምን ተብለው ሲጠየቁም ሠራተኞቻቸው ደንበኛቸውን ይገላምጣሉ፤ አገልግሎቱንም ይበልጥ ያሽመደምዳሉ፡፡
የሁለቱም ተቋሞች አገልግሎት ይሻሻል ዘንድ መንግሥት በየጊዜው የመዋቅር ማሻሻያና የመሣሪያ ግዥ እንደሚያደርግና እያደረገም እንደሆነ በየጊዜው በኢቴቪ እናያለን፤ እንሰማለን፡፡ ግን አቅመ ደካማነታቸውን ሊያሻሽሉ አልቻሉም፡፡
ለምሳሌ መንግሥት ቴሌን ከኮርፖሬሽን ወደሚኒስቴር መ/ቤት አሳድጐታል፤ አገልግሎቱ ግን እየባሰ፣ እየዘቀጠ ሄደ እንጂ አንዳችም መሻሻል ሊያሳይ አልቻለም፡፡ ትላንት የተቋቋመችው ደቡብ ሱዳንና የተረጋጋ መንግሥት የሌላት ሶማሊያ፤ ከእኛ በአያሌው የተሻለ አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ እኛ ግን ገና እንድሃለን፡፡ ለመሆኑ ልናገኘው የፈለግነውን ሰው ያለምንም ድምጽ መቆራረጥና ጥሪ መሰናከል መቸ ይሆን ማናገር የምንችለው? የጐበዝ አለቆች ሆይ፤ እባካችሁ ወደነበረው ባለገመድ ስልክ መልሱን፡፡
የመብራት ኃይል ኮርፖሬሽን የሥራ ኃላፊዎች በመቅበጥ (ኪራይ ሰብሳቢነት) ተጠርጥረው ከርቸሌ መግባታቸውን ፀረ ሙስና ኮሚሽን ነግሮናል፡፡ የተከሰሱበት ወንጀል እውነት ሆኖ ከተፈረደባቸው “እሰየው” ያሰኛል፡፡ መብራቱን እያጠፉ የእኛን አንጀት ነበራ ሲያቃጥሉ የኖሩት፡፡ መንግሥት ቢቸግረው የመብራት ኃይል ባለሥልጣኑን ሰሞኑን በሌላ ቀይሯል። ግንኮ ስርዓቱን (ሲስተሙን) ማስተካከል ነው እንጂ ሰው ቢቀያየር ለውጥ ሊመጣ አይችልም፡፡ በአጠቃላይ በከተማችን ውስጥ በተለያዩ አካባቢዎችና በተለያዩ የሥራ መስኮች ላይ የጐበዝ አለቆች ተበራክተው ነዋሪውን ቁምስቅሉን እያሳዩት ነው፡፡ መንግሥት መንቃት አለበት። ክቡር ከንቲባውም በየቦታው ምን እየተሰራ እንደሆነ ተዘዋውረው ሊያዩና አፋጣኝ መፍትሔ ሊሰጡ ይገባል። አለዚያ ከተማቸውን የጐበዝ አለቆች እየተቀራመቷት ነውና የመረረው ሕዝብ…

Read 5099 times
Administrator

Latest from Administrator