Monday, 18 November 2013 10:48

ከሳኡዲ የተመለሱ ኢትዮጵያውያን ሰቆቃ

Written by  አበባየሁ ገበያው
Rate this item
(6 votes)

ሰሞኑን በህገወጥ መንገድ ሳኡዲ አረቢያ ከገቡ ብዙ ሺ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች መካከል ዓለም አቀፍ የስደተኞ ተቋም ከ350 በላይ የሚሆኑትን ወደ አገራቸው መልሷቸዋል፡፡ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው በተቋሙ መጠለያ ጣቢያ ያገኘቻቸውን ሦስት ተመላሾች አነጋግራለች፡፡
“ሳኡዲ ወርቅ እየዘነበ ነው ቢሉኝ አልሰማም” አብዱ እንድሪስ
“ኢትዮጵያውያን በእስር ቤት እየተሰቃዩ ናቸው” እንድሪስ መሃመድ
“አበሻ ለእነሱ ርካሽ እቃ ማለት ነው” እንድሪስ የሱፍ

አብዱ እንድሪስ እባላለሁ፣ ከኮምቦልቻ ተነስቼ ከጓደኞቼ ጋር ነው የሄድኩት---መንገዳችን ጥሩ ነበር፡፡ የመን ከዛም ሳኡዲ ደረስን። ከስምንተኛ ክፍል ነው የሄድኩት..ቤተሰቦቼ ድሆች ነበሩ --- የእነሱን ችግር እያየሁ መቀመጥ አላስቻለኝም፡፡
ስንት ጊዜ ቆየህ ሳኡዲ?
አስር ወር ቆይቼ ነው የመጣሁት፡፡ አምስቱን ወር በእስር ቤት፣ አራት ወር ጎዳና ተዳዳሪ ሆኜ ስንከራተት---አንድ ወር ብቻ ነው ተቀጥሬ የሰራሁ፡፡
ምን ነበር የምትሰራው?
በግ እጠብቅ ነበር፡፡ ደሞዜ ስምንት መቶ ሪያድ ነበረ፡፡ ደሞዜ እንደነገ ሆኖ እንደዛሬ ፍተሻ ሲያደርጉ አገኙኝና ወሰዱኝ፣ አምልጫቸው ጎዳና ለጎዳና ስንከራተት---መንገድ ለመንገድ ስተኛ-- በመጨረሻ ምግብ እየለመንኩ መኖር ጀመርኩ፡፡ ለማኝ ነበርኩ፡፡
አራት ወር ጎዳና ተዳዳሪ ሆነህ ምግብ የሚሰጥህ ማን ነበር?
በህጋዊ መንገድ የመጡ የእኛ ሴቶች አሉ፣ ሥራ የሚሰሩ፡፡ አልፎ አልፎ ምግብ ደብቀው ይሰጡኛል፡፡ ሴቶችም ወንዶችም ብዙ ጎዳና ተዳዳሪዎች አሉ፣ ብዙ እብዶችም አሉ፡፡ ቆም ብለሽ ዞር ስትይ ኢትዮጵያዊ ለማኝ፣ ጎዳና ተዳዳሪ፣ እብድ---አለ በየመንገዱ፡፡ አንዳንዴ ፖሊሶች ከመንገድ አንስተው ያስራሉ፡፡
አንተም ጎዳና ላይ ተገኝተህ ነው የታሰርከው?
አምስት ወር ሙሉ በእስር ቤት ነበርኩ፡፡ እስርቤቱ እንዴት ነበር ብለሽ እንዳትጠይቂኝ--ማስታወስ አልፈልግም፣ ያመኛል፡፡ ዱላውንና ድብደባውን..ማንጓጠጡንና ማንቋሸሹን…አልነግርሽም፡፡ ግን የሰው ዘር ናቸው? እኔ አላውቅም፡፡ ኢትዮጵያኖች እኮ እስር ቤት ሁሉ ይሞታሉ፡፡ ረሃብማ ተይው፡፡ እንኳን ብቻ ለአገራችን አበቃን፡፡
ቤተሰብህ ያለህበትን ሁኔታ ያውቅ ነበር?
እንደገባሁ ደውዬ ነበር፡፡ ከዛ ግን አስር ወር ሙሉ የት እንዳለሁ --- ልሙት ልዳን የሚያውቁት ነገር የለም፡፡ አሁንም ዝም ብዬ ነው ተሳፍሬ የምሄደው፡፡
በአሁኑ ሰዓት ሳኡዲ ውስጥ ኢትዮጵያኖች እየተንገላቱ ነው ይባላል..
ድብደባ ቢሉሹ ድብደማ መሰለሽ፡፡ ዝግንን በሚል ሁኔታ ነው የሚደበድቡበት፡፡ ዱላ እኮ መፈንከት ብቻ ሳይሆን የደምስርሽ እንዲቋረጥ ያደርጋል፡፡ ሽባ ነው የሚያደርጉት---.በጣም ይጠሉናል፡፡
ከዚህ በኋላ ተመልሰህ አትሄድም?
እንኳንም መጣሁ፡፡ አላህ ለአገሬ ምድር አበቃኝ፡፡ አሁን አገሬ ስገባ የምሰራውን ስራ እኔ ነኝ የማውቀው፡፡ ለእኔ ብቻ ሳሆን ለጓደኞቼም ትምህርት ነው የምሆነው፡፡ ይጠቅመኛል ያለ ይከተለኛል፣ ያለዚያ የራሱ ጉዳይ፡፡
ምን ልትሰራ አሰብክ?
በንግድም ሆነ በሚያዋጣኝ ወጥሬ ነው የምሰራው፡፡ ሳኡዲ አረቢያ ወርቅ እየዘነበ ነው ቢሉኝ -- ከአሁን በኋላ ስሙን እንኳን መስማት አልፈልግም፡፡ የቅጣታቸው አከፋፍ ምን እንደሆነ ታውቂያለሽ… አውራ ጣትና አውራ ጣትን በገመድ ያስሩና ርቆ ከተሰቀለ ባላ ላይ ያቆማሉ፡፡ ከስር የተቆመበትን ወንበር ጎትተው ሲጥሉት ..ስቃዩና ሰቆቃው አይጣል ነው፡፡ ስንቱ የጀርባ ህመምተኛ፣ ስንቱ መሽናት አቅቶት እየተንፏቀቀ እንዳለ ብታይ …አየሽው /ክብዱን እያሳኝ ለምጥ/ ይሄ ለብዙ ጊዜ ያሰቃየኝ ቁስል ነው ደብድበውኝ፡፡ የእኔ ጓደኛ ተደብድቦ ተደብድቦ በሽተኛ ሲሆን ወደ ኢትዮጵያ መለሱት---በተመለሰ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ሞተ። መቼም ብዙ መከራ አሳለፍን፡፡

=================

ስምህ ማን ነው ?
እንድሪስ መሃመድ፡፡
እድሜህ ?
ሀያ ዓመት ሆኖኛል፡፡
ወደ ሳኡዲ አረቢያ እንዴት ሄድክ ?
ገና የስምንተኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ ከጓደኞቼ ጋር መከርን፡፡ ለምን እንደሌሎች ጓደኞቻችን ሳዑዲ አንሄድም አልን፡፡ ሳኡዲ ሄደው ለወላጆቻቸው ባጃጅ ስለገዙ፣ ቆርቆሮ ቤት ስለሰሩ፣ ንግዱን ስለሚያጧጡፉ --- የአካባቢያችን ልጆች ካወራን በኋላ ለመጓዝ ወሰንኩ፡፡ ለደላላ አራት ሺህ ብር ከፍዬ በእግሬ ዘጠኝ ቀን ተጉዤአለሁ - ባህር ድረስ፡፡ በመጨረሻ ሳኡዲ የገባሁትም በእግሬ ነው፡፡
መንገድ ላይ ችግር አልገጠማችሁም ?.
እሱ እንኳን ስቃይ ነበረው፡፡ የመን ድንበር ላይ ተኩሰውብን፣ ግማሾቹ ሲያዙ ግማሾቻችን አመለጥን፡፡
ሳኡዲ ከገባህ በኋላ ሥራ አገኘህ ?
አዎ የፕላስቲክ ማምረቻ ውስጥ ነበር የምሰራው፣ ፕላስቲክ ሰሃን፣ ፕላስቲክ ወንበር --- እነሱን ቅርፅ ማስያዝ ነበር የእኔ ሃላፊነት፡፡
ገንዘብ ለቤተሰብ ትልክ ነበር ?
አዎ---በወር 2ሺ ሪያድ እልክ ነበር፡፡ እሱስ የድካሜን ያህል ኮምቦልቻ ቦታም ገዝቻለሁ፡፡ እድሜ ለሳውዲ---.ያጠራቀምኳትን እየበላሁ ወጥሬ እሰራላሁ፡፡
አሁን እንዴት ነው የመጣኸው ?
ተይዤ ነው የመጣሁት፡፡
በመገናኛ ብዙኃን ብዙ ኢትዮጵያኖች ስቃይ ላይ እንደሆኑ ተዘግቧል ---
ከተማው ሰፊ ስለሆነ እዚህ ለቅሶ እዚያ ጩኸት ነው፡፡ እኔ አልተመታሁም ግን ሰምቻለሁ---በአይኔም አይቻለሁ፡፡ እስር ቤት ደግሞ መከራውና እንግልቱ ከባድ ነው፡፡ ጃዋዛ (ወታደሮች) እየጠረነፉ እስር ቤት ያስገቡ ነበር፡፡ በርካታ ኢትዮጵያውያን በእስር ቤት እየተሰቃዩ ናቸው፡፡
አንተም ታስረህ ነበር ?.
አዎ--- ወር ከሶስት ቀን
ከአሁን በኋላ ተመልሰህ መሄድ ትፈልጋለህ ?
በቃኝ ካላስ፡፡

=============

ስሜ እንድሪስ የሱፍ ይባላል፡፡ ትውልዴ ሃይቅ ነው፡፡ ወደ ሳኡዲ የሄድኩት ትንሽ ለውጥ ፈልጌ ነበር፡፡ በጅቡቲ በኩል ነው የሄድኩት- በባህር፡፡ ጅቡቲን የሚያሳልፈን መሪ ነበረን፡፡ ያውም እኮ የመጨረሻ ልጅ ነኝ፡፡ አባቴም እናቴም እያለቀሱ ነው የሰደዱኝ፡፡ የእነሱ እንባ ነው መሰለኝ አላስቆም አላስቀምጥ ብሎኝ ነበር፡፡
ጉዞው እንዴት ነበር?
ምን ትያለሽ? ድካሙንማ ተይው! ወንድም ሴትም በየመንገዳችን ስንቀብር ነበር፡፡ እየደከማቸው ሲወድቁ እየጣልናቸው ነው የሄድን። ባህር ድረስ ዘጠኝ ቀን ነው የፈጀብን፡፡ ለታመሙት እንኳን ውሃና ምግብ እንዳንሰጥ እልም ያለ በረሃ ነው፡፡ ሁላችንም ደግሞ ስንቃችንን ጨርሰናል፡፡ እኔ በበኩሌ የራሴን ነፍስ ማትረፍና ወርቅ እና ገንዘብ ይታፈስበታል ከተባለው አገር--- ሳኡዲ መድረስ ነበር የማስበው፡፡
ወርቅና ገንዘብ እንደሚታፈስ ማን ነገረህ?
እዛ የሄዱ ጓደኞቼ ሲደውሉሉኝ፣ ገንዘብ ለቤተሰቦቻቸው-- ለወገኖቻቸው ሲልኩ ሳይ እየተጎመጀሁ መጣሁ፡፡ ከዛ የመጣው ይምጣ ብዬ በረሃና ባህር ተሻግሬ ሄድኩ፡፡
ግን በህጋዊ መንገድ መሄዱ አይሻልም ነበር?
አይ አንቺ! በህጋዊ መንገድ የሄዱትስ ብትይ የትኛው ክብር ሲኖራቸው ..በባህር ሄድሽ በአየር ኢትዮጵያዊ እንደሆነ ኢትዮጵያዊ ነው፡፡ እስር ቤት አብረውኝ ሲማቅቁ የነበሩት እንደኛ ያሉት ብቻ መሰለሽ---በፓስፖርት በአየር ሄደውም እኮ ዋጋቸው የኛን ያህል ነው፡፡
ሁለት ሺህ ብር ከፍዬ ጅቡቲ ተሰብስበው ከሚጠብቁ ሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር በመርከብ ተሳፍረን ስንሄድ የነበረውን ድካም፣ የዘጠኝ ሰዓት ጉዞ ውስጥ የነበረውን ሰቆቃ---አልነግርሽም፡፡ ማዕበል ተነስቶ --- ጀልባዋ ልትደፋን ደርሳ --- ብታይ ልትጨርሰን፡፡ የመን ወደብ ስንደርስ መሸዋት ከተባለች ስፍራ በመኪና ተጭነን ተጓዝን፡፡ ግን የየመን ፖሊሶች አግኝተውን ቀጠቀጡን፡፡ ‹‹ጅዳ ወይንም ሌላ አገር ደውላችሁ ገንዘብ ሃዋላ አስደርጉ›› ብለው ደበደቡን፡፡ ደሞ ሴቶችን ሶስት አራት ሆነው ነው የሚደፍሩዋቸው፡፡
ከየመን ወደብ ተነስተህ እንዴት ሳኡዲ ወደብ ደረስክ?
ገንዘብ ያላቸው ከፍለው ነው በመኪና የሄዱት፡፡ እኔ ግን ገንዘብ ከሌላቸው ወጣቶች ጋር ሆኜ በረሃ ለበረሃ አስር ቀን ተጓዝን፡፡ በመሃል የሚሞት አለ፤ ለመቅበር እንኳን አቅም አልነበረንም፣ ጥለነው ነው የምናልፍ። ባለፍንበት መንገድ ክፉኛ ሽታ ያለበት ያጋጥመን ነበር፡፡ ምን መሰለሽ? እንደኛ ሳኡዲ ለመግባት ተሽሎክሉከው መንገድ የሚያሳብሩ ሰዎች ሞተው፤ የሚቀብራቸው አጥተው በየስፍራው ተጥለዋል፡፡ ውይ…አጥንታቸው ብቻ ቀርቶ--.ስናይ እናለቅስ ነበር፡፡ አብረውኝ የነበሩ ጓደኞቼም ሞተው አልቀዋል፡፡
/በረዥሙ ተንፍሶ ለአፍታ ቆዘመ/ አንዱ ከሃገሬ አብሮኝ ተነስቶ ሳኡዲ ድንበር ሲደርስ ሞተ፡፡ አሁን ለቤተሰቦቹ ምን እንደምናገር እንጃ?
እንዴት ወደ ሳኡዲ ገባህ?
እንደምንም ተሽሎኩልኬ ሳኡዲ ገጠር ገባሁና በእረኝነት ስራ ጀመርኩ፡፡
ስንት ይከፍሉህ ነበር ?.
አራት መቶ ሪያድ ተቀጥሬ ነበር፤ ግን የሰራሁት ለሁለት ወር ነው፡፡ እሱንም በኪሴ ይዤ ወደ ጓደኞቼ ስሄድ ሌባ ቀማኝ፡፡ ጓደኞቼ ጋ ስሰራም እንዲሁ ያገኘሁትን ገንዘብ ተነጠቅሁ፡፡ እና የሚመስለኝ አበሻ ለእነሱ ርካሽ እቃ ማለት ነው፡፡ ጢባ ጢቤ የሚሉት፡፡ አንድ ማዳም ‹‹ባሌን ልትቀማኝ ነው፣ ይዛብኛለች›› ብላ ያሰበቻትን ኢትዮጵያዊ ፣ እጅዋን እንደቆረጠቻት አውቃለሁ፡፡ አሰርተው ገንዘባቸውን ይከለክሏቸዋል፡፡ ስንቱ ኢትዮጵያዊ ነው መንገድ ለመንገድ እያደረ የሚኖር--
እስር ቤት ነበርክ ?
አዎ ሁለት ወር እስር ቤት ነበርኩ፡፡ ጠዋት አንድ ቂጣ፣ ማታ አንድ ቂጣ ነበር የሚሰጡን፡፡ ብዙ እስር ቤት አላቸው፣ ብዙ አበሻም እስር ቤቱን አጣቦታል፡፡ ስንናገር ‹‹ዝም በሉ ከብቶች›› ተብለን እንደበደባለን፡፡ ባህሬንና ፓኪስታኖች ሲያወሩ ያዳምጧቸዋል..እኛን ግን ንቀታቸው የትየሌሌ ነው።
አሁን ወደ ትውልድ አገርህ ነው የምትመለሰው?
ደውዬላቸዋለሁ፡፡ ወደ ቤት ነው የምመለሰው።

Read 6790 times