Print this page
Saturday, 26 October 2013 14:01

የአረጋውያኑን ትጋት የሚያስቃኘው አውደርዕይ

Written by  መልካሙ ተክሌ
Rate this item
(2 votes)

“በአንድ ቀን ትምህርት ፎቶ አንሺ ሆኜ ቁጭ አልኩ” - የ69 ዓመቷ አረጋዊ ወ/ሮ ባዩሽ

ካዛንቺስ አካባቢ በልመና የሚተዳደሩ አንድ አይነሥውር ሽማግሌ አሉ፡፡ የሚለምኑት ከካዛንቺስ ስድስት ኪሎና ፒያሳ ለመሄድ ታክሲ ከሚጠብቁ ተሳፋሪዎች ነው፡፡ አንድ ቀን በእለቱ የለመኑትን ገንዘብ ታክሲ እየጠበቅሁ ባለሁበት ቁጠርልኝ አሉኝ፡፡ እስከ ቀኑ 11 ሰዓት አርባ ብር ለምነዋል፡፡ በሌላ ቀን ተመልሼ ጠየቅኋቸው። በልመና ከሚያገኙት ገንዘብ ልጃቸውን ኮሌጅ አስተምረዋል፡፡ ልጃቸው ሥራ ከያዘ ከዓመታት በኋላም ግን ልመና አላቆሙም፡፡ አሁንም እዚያው ካዛንቺስ እየለመኑ ነው፡፡
“ለምን ልመና አያቆሙም?” አልኳቸው፡፡
“ምን ላድርግ ቁጭ ልበል እንዴ?” በማለት እኔኑ መልሰው ጠየቁኝ፡፡ እዚያው ካዛንቺስ የሚለምኑ ሌላ አረጋዊ ከፍተኛ የእይታ ችግር አለባቸው፡፡ በምፅዋት የሚያገኙትን ሳንቲም ይዳብሱና አምስት ሳንቲም ከሆነ መልሰው ይወረውሩታል፡፡
በአንፃሩ የእይታም የአቅምም ችግር ያለባቸው የማይመስሉ አንዲት አሮጊት፤ ኡራኤል ቤተክርስትያን አካባቢ ከጥቂት ወራት በፊት አገኘሁ፡፡ የእሳቸው የአለማመን ዘይቤ ከተለመደው የተለየ ነው፡፡
“ቤቴ ልደታ ነው፤ መሳፈርያ አልያዝኩም” አሉኝ፡፡
“ኑ፤ እኔ እከፍልሎታለሁ፤ በዚያ አቅጣጫ ነው የምሄድው” አልኳቸው፡፡
“ባትሰጥ አትተወውም” ብለው እየተቆጡ ትተውኝ ሄዱ፡፡
ከቀኑ 11 ሰዓት ግድም ብሔራዊ ትያትር አካባቢ ሲለምኑ ያገኘኋቸው መስራት የሚችሉ ሴት ለልመናው ምክንያት የሰጡት “ልጄ ታሞብኝ ማሳከሚያ አጣሁ” የሚል ነው፡፡ እኒህኑ ሴት ከምሽቱ አንድ ሰዓት አካባቢ ኡራኤል ቤተክርስትያን አካባቢ ሲለምኑ አገኘኋቸው፡፡
አሁን ደግሞ “ገንዘቤን ዘረፉኝ” ሲሉ ሰማኋቸው፡፡
በየቦታው መሥራት እየቻሉ ልመና የወጡ አረጋውያን አያሌ ናቸው፡፡ አንዳንዶቹ አመል ሆኖባቸው ነው እንጂ ሠርተው በገቢ ራሳቸውን መደጐም ይችላሉ፡፡ ለዚህም ይመስላል “ኸልፕ ኤጅ ኢንተርናሽናል”፣ የኢትዮጵያ አረጋውያን ማህበር እና ሌሎች አጋሮቻቸው ባለፈው ሳምንት አረጋውያን ሰርተው መጠቀም የሚችሉ መሆኑን የሚያሳይ የአራት ቀናት አውደርእይ ቦሌ አካባቢ በትሮፒካል ጋርደን ያዘጋጁት፡፡ ሰርተው ራሳቸውን በመደጐማቸው ደስተኞች መሆናቸውን ያነጋገርኳቸው አረጋውያን ይገልፃሉ፡፡
በ1993 ዓ.ም የተመሰረተው የኢትዮጵያ አረጋውያን ማህበር፤ 38 አባል ማህበራት ያሉት ሲሆን “ጤነኛ አረጋውያን ሰርተው መኖር ይችላሉ” በሚል መርህ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ ማህበሩ፤ በአረጋውያን ሊተገበሩ የሚችሉ ፕሮጀክቶችን የሚቀርፅ ሲሆን አረጋውያንን በስልጠናና በልምድ ልውውጥ ያግዛል፡፡
የልምድ ልውውጡ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት ይከናወናል፡፡ ባለፈው ዓመት ለምሳሌ በእንግሊዝ የፖትስማውዝ ከተማ አረጋውያን ማህበር የአዲስ አበባ አቻውን ለልምድ ልውውጥ ጠርቶ ነበር፡፡ ነገር ግን ለማህበሩ ፕሮጀክት ኦፊሰር ብቻ ሲፈቀድ የአረጋውያን ማህበር ፕሬዚደንቱ፤ “የከተማ ቦታ የለዎትም፤ ጡረታዎም ሃያ ፓውንድ አይሞላም፤ ሄደው ሊቀሩ ይችላሉ” በሚል የእንግሊዝ ኤምባሲ ቪዛ መከልከሉ ቅሬታ አሳድሯል፡፡ እናም የፖትስማውዙ ማህበር ለእንግሊዝ ፓርላማ ክስ አቅርቧል፤ ምላሹ ባይታወቅም፡፡ ቪዛ የተሰጠው ፕሮጀክት ኦፊሰር ግን እንግሊዝ ቀርቷል፡፡
የአረጋውያን ማህበር አባላት፤ ህብረተሰቡ ለአረጋውያን ያለው አመለካከት የተዛባ መሆኑ ችግራቸውን የከፋ እንዳደረገባቸው ይናገራሉ፡፡ ይሄን አመለካከት ለማስወገድም ትግል ላይ ናቸው፡፡ የህብረተሰቡ የተዛባ አመለካከት እንዲወገድ እየሰራን ነው የምትለው የ”ኼልፕ ኤጅ ኢንተርናሽናል” የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ኤርና ምንተስኖት ሃንዝ፤ በአረጋውያን ላይ የሚደርስባቸው መብት ረገጣ እንዲቆም ፊርማ እያሰባሰቡ መሆኑንና ቅሬታቸውን ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እንደሚያቀርቡ ተናግራለች፤ ሕግ እንዲበጅለት፡፡በሰሞኑ አውደርእይ ብዙ መንቀሳቀስ የማይችሉ አረጋውያን አትክልት ውሃ ሲያጠጡ፣ ለራሳቸው ምግብ ለማሰናዳት ሽንኩርትና ድንች ሲልጡ የሚያሳዩ ፎቶግራፎች ቀርበዋል፡፡ ሥራዎቻቸው ከቀረቡላቸው ማህበራት አንዱ “እንረዳዳ” የአረጋውያን ማህበር ሲሆን አረጋውያን የተረጅነት ስሜት እንዳይሰማቸው እያደረግሁ ነው የሚለው ማህበሩ፤ የተወሰነ ሥራ እንደየአቅማቸው እየሰሩ መሆኑን ገልጿል፡፡ የማህበሩ አባላት የሰሯቸው የሽመና ውጤቶችም በአውደርእዩ ላይ ቀርበዋል። አረጋውያኑ እንደየስራቸው መጠንም ገንዘብ ያገኛሉ፡፡ ጋቢ የሰራ የጋቢ ዋጋ፣ ፎጣ የሰራ የፎጣ ዋጋ ያገኛል፡፡ አባላቱ ዱቄት፣ ዘይት፣ ሳሙናና የመሳሰሉትም ይሰጣቸዋል፡፡ ተቀጥረው የመስራት አቅም ያላቸው ደግሞ በወጥ ቤትነት፣ በጥበቃ፣ በአትክልተኝነትና በፅዳት ሥራዎች እንደሚቀጠሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡የአረጋውያኑ ምርቶች ወደ ገበያው ገብተው የሚሸጡበት ሁኔታ የጠየቅኋት የአውደርዕዩ አስጐበኚ፤ “በባዛር እና በዕቁብ ይሸጣል፡፡ ለምሳሌ ብርጭቆ ፋብሪካ በወር ስምንት ጋቢ ይገዛል” ብላለች፡፡
የ75 ዓመቱ አረጋዊ አቶ መኩርያ፤ የጉለሌ አካባቢ ነዋሪ ሲሆኑ በፊት ገበሬ ነበሩ፡፡ አሁን ግን ሸማኔ ሆነዋል፡፡
በቀን ሦስት ክንድ እና ከዚያ በላይ እየሸመኑ በሳምንት አንድ ጋቢ እንደሚያደርሱ የተናገሩት አረጋዊው፤ “እኔ ተሯሩጬ መሸጥ ስለማልችል ማህበሬ ነው የሚሸጥልኝ” ብለዋል፡፡
ሌላው የ70 ዓመት አረጋዊ አቶ ኃይሌ ሀብተማርያም፤ ከበቾ አካባቢ ያርሱ ነበር፡፡ አቅም እያነሳቸው ሲሄዱ እየተረዱም ቢሆን አምራች አረጋዊ በመሆን አንዳንድ ወጪዎቻቸውን ራሳቸው እንደሚችሉ ገልፀውልኛል፡፡
“ውድ የአረጋውያን በጐ አድራጐት ድርጅት” በየወሩ ለእያንዳንዱ አረጋዊ 100 ብር የሚሰጥ ሲሆን አረጋውያኑ አትክልትና ፍራፍሬ በመነገድ ተጨማሪ ገቢ ያገኛሉ፡፡
የ69 ዓመቷ ወይዘሮ ባዩሽ ወልደአረጋይ፤ እድሜያቸው ሳያግዳቸው ፎቶ አንሺ ሆነዋል፡፡
“ፎቶ ማንሳት መቼ ጀመሩ?” ብዬ ጠየቅኋቸው፤ ወይዘሮ ባዩሽን፡፡ “እዚህ አረጋውያን ድርጅት ውስጥ እየሰራሁ “ኼልፕኤጅ ኢንተርናሽናል” ለልምድ ልውውጥ የውጭ ሰዎች አመጣ፡፡ በማግስቱ ካሜራ ሰጡን፤ ለማስተማር፡፡ እዚያው አስተማሩን። ሦስት አረጋውያን ነን በእለቱ ስልጠና የተሰጠን። አሰልጣኛችን እንዴት እንደምናነሳ አሳይቶን “ነገ ታሳዩኛላችሁ” ብሎ ሄደ፡፡ ራሳችን ያሳነውን የታጠበ ፎቶም ለኛ አሳይቶን ካሜራው ለእያንዳንዳችን ቀረ። ይኸውልህ ልጄ፤ በአንድ ቀን ትምህርት ፎቶ አንሺ ሆኜ ቁጭ አልኩ፡፡ ከዚያን ወዲህ ሠርግ ላይ ‘እቴቴ እስቲ ፎቶ አንሺን’ ተብያለሁ”
“እና ለወደፊት ምን አሰቡ ታዲያ?”
“ጥሩ ነው፤ ደግሞም ፎቶ እያነሳሁ ገንዘብ ማግኘቱም ይጠቅማል፡፡ እግዚአብሔር ካለ በዚህ ካሜራዬ ተአምር እሰራበታለሁ፡፡ ትልቅ ሥራ እሰራበታለሁ፤ ራሴንም እደጉምበታለሁ” ብለዋል፤ ወ/ሮ ባዩሽ፡፡ከ86 ሚ. የኢትዮጵያ ሕዝብ ውስጥ አምስት ሚሊዮን ያህሉ አረጋውያን እንደሆኑ የ”ኼልፕ ኤጅ” መረጃ ይጠቁማል፡፡

 

Read 1915 times