Saturday, 12 October 2013 12:15

የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች በትራንስፖርት እጦት ተጉላሉ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(2 votes)

            የዩኒቨርስቲ የምዝገባ ቀን እንዳያመልጣቸው የሰጉ ተማሪዎች ሰሞኑን ከሌሊቱ 10 ሰዓት ጀምሮ የአውቶቡስ ትኬት ለመቁረጥ እየጣሩ መሆናቸውን ገልፀው፤ የትራንስፖርት ታሪፍ በግማሽ ተጨምሮበትም ትኬት ሊያገኙ አልቻሉም፡፡
ወደ ጅማ ለመሄድ የ177 ብሩ ትኬት ሃምሳ በመቶ ተጨምሮበት ከ260 ብር በላይ ሆኖበት የተቸገረ ተማሪ፤ ያም ሆኖ ትኬት አልቋል በሚል እንደተንገላታ ገልጿል፡፡
በተለይ በአዲስ አበባ በኩል ወደየተመደቡበት ዩኒቨርሲቲ ለመሄድ ከተለያዩ ክልሎች የመጡ ተማሪዎች፤ ባልተጠበቀ የታሪፍ ጭማሪና በትኬት እጦት እንደተንገላቱ ገልፀዋል፡፡
በአዲስ አበባ የአውቶቡስ መነሃሪያ የትራንስፖርት ስምሪት ተቆጣጣሪ በበኩላቸው፤ የትራንስፖርት እጥረት የተፈጠረው ሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች በተመሳሳይ ቀናት ተማሪዎችን ለምዝገባ በመጥራታቸው ነው ብለዋል፡፡
በየማለዳው ወደ አውቶቡስ መናሃሪያ ሲመላለስ ከሰነበቱት ተማሪዎች መካከል አንዷ የሆነችው ሰላማዊት ይፍሩ፣ የአርባ ምንጭ ትኬት ለመቁረጥ ከሌሊቱ 10 ነው አውቶቡስ ተራ የደረሰችው፤ ትኬት ሻጮች በቢሯቸው አልነበሩም፡፡ እስከ ረፋድ 3 ሰዓት ድረስ ብትጠብቅም ትኬት ሻጮች ከነአካቴው ባለመምጣታቸው ግራ እንደገባት ተናግራለች፡፡ ዲላ ዩኒቨርስቲ የተመደበ ሌላኛው ተማሪም፣ ማክሰኞ እለት ለሁለተኛ ቀን ቲኬት ለማግኘት በሌሊት መጥቶ አልተሳካለትም፡፡ ሰኞ እለት መናሃሪያው ውስጥ ለወረፋ ከተሰለፉ ተማሪዎች አንዱ እንደነበረ ገልፆ፣ አንድም ቲኬት ሳይሸጥ፣ አንድም ተማሪ ትኬት ሳይቆርጥ የመደበኛ ቲኬት አልቋል እንደተባለ ገልጿል፡፡ የፈለገ በ”ፐርሰንት” የሚሸጠውን ትኬት መግዛት ይችላል” ተብሎ እንደተነገራቸው ጠቅሶ፣ አቅም ያላቸው የተወሰኑ ሰዎች በመደበኛ ታሪፍ ላይ ግማሽ ያህል ጨምረው እየከፈሉ ትኬት እንደቆረጡ ተናግሯል፡፡ በጭማሪ ክፍያ የሚቆረጠው ትኬትም ቢሆን ወዲያው “አልቋል” ተብሎ ተቋርጧል፡፡ ነገር ግን ከመነሃሪያው ቅጥር ግቢ ውጭ የ50 ብር ጭማሪ እየተደረገባቸው ትኬቶች እንደሚሸጡ ይገልፃል - ወደ ዲላ ለመሄድ የተቸገረው ተማሪ፡፡
ቀድሞ መኪና ሲያመልጥ ወይም ሲበላሽ ቲኬቱን መልሶ ገንዘብ መቀበል እንደሚቻል የሚገልፁት ተጠቃሚዎች፤ አሁን ግን መደበኛው ታሪፍ እንጂ 50 በመቶ (የፐርሠንት) ጭማሪው እንደማይመለስ ገልፀዋል፡፡
ከተለያዩ ክልሎች በአዲስ አበባ በኩል ወደየተመደቡበት ዩኒቨርስቲ የሚጓዙ ተማሪዎች ይበልጥ ተቸግረዋል፡፡ አርባ ምንጭ ዩኒቨርስቲ ተመድቦ እሁድ ማምሻውን ወደ አዲስ አበባ የመጣ የደብረ ብርሃን ተማሪ፤ ሠኞ እለት ወደ አርባ ምንጭ እሄዳለሁ የሚል ተስፋ የነበረው ቢሆንም፤ በማግስቱም ትኬት ስላላገኘ የምዝገባ ቀን እንዳያልፍበት መስጋቱን ተናግሯል፡፡
ብዙ መንገደኞች እየተጉላሉ መሆናቸውን ያመኑት የመነሃሪያው የህዝብ ትራንስፖርት ተቆጣጣሪ አቶ ሃይሌ ገብሬ፤ የመነሃሪያው አስተዳደር ሃላፊዎችና ሠራተኞች በተቻላቸው አቅም ችግሩን ለመቅረፍ እየሠራን ነው ብለዋል፡፡ የትራንስፖርት እጥረት የተፈጠረው ዩኒቨርስቲዎች በተመሣሣይ ጊዜ ተማሪዎቻቸውን በመጥራታቸው ነው የሚሉት አቶ ሃይሌ፤ በቲኬት አቆራረጥ ላይ ለሚነሱ ቅሬታዎች ተጨባጭ ማስረጃ እንዳልቀረበላቸው ገልፀዋል፡፡ ከሌሊቱ 10፡30 ጀምሮ መነሃሪያው እንደሚከፈትና የቲኬት ቢሮዎችም (ፉካዎች) ደንበኞቻቸውን እንደሚያስተናግዱ የገለፁት አቶ ሃይሌ፤ ቲኬት ቆራጮች የትራንስፖርት ቢሮው ሠራተኞች ሣይሆኑ በመነሃሪያው ውስጥ ያሉት ከ20 በላይ የትራንስፖርት አገልገሎት ሠጪ ማህበራት ሠራተኞች ናቸው ብለዋል፡፡ የዩኒቨርሲቲ ምዝገባ ሲቃረብና በበአል ወቅቶች የተጓዦች ቁጥር ስለሚጨምር የቲኬት መቁረጫ ቢሮዎቹ እየተጣበቡ ከቢሮ ውጭ ቲኬት ለመቁረጥ ይገደዳሉ የሚሉት አቶ ሃይሌ፤ “በዚህ መሃል አልፎ አልፎ ህገወጥ ተግባራት ሊፈፀሙ ይችላሉ” ብለዋል፡፡ የመነሃሪያው አስተዳደር በውስን የቁጥጥር ሠራተኞች በተቻለው አቅም ቁጥጥር ያካሂዳል፤ ከመነሃሪያው ውጪ ትኬት ይቆረጣል የሚባለው ቅሬታ ግን፣ በአካል ሳናይ ወይም ተጨባጭ ማስረጃ ሳይቀርብልን የትራንስፖርት ማህበራት ሠራተኞችን ጥፋተኛ ማድረግ አንችልም” ብለዋል፡፡
የ“ፐርሠንት ጭማሪ” የሚባለው ክፍያ ምን እንደሆነ የተጠየቁት አቶ ሃይሌ፤ በአንድ መስመር የሚመደቡት አውቶብሶች በቂ በማይሆኑበት ጊዜ ተጨማሪ አውቶቡሶች በጊዜያዊነት እንዲመደቡ የሚደረግበት አሠራር እንደሆነ ጠቁመው፣ በጊዜያዊነት የተመደቡ አውቶቡሶች ተሣፋሪውን አድርሠው ባዶአቸውን ስለሚመለሱ ቢያንስ የነዳጅ ወጪ ለመሸፈን በመደበኛው ታሪፍ ላይ ማካካሻ ክፍያ ይጨመርበታል ብለዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ከ400 ኪ.ሜ በላይ ለሚርቁ ቦታዎች 35 በመቶ፣ ከዚያ ለሚያንሡት ደግሞ 50 በመቶ ጭማሪ ይደረጋል ሲሉም አስረድተዋል፡፡
ቲኬት የሚመልሱ ደንበኞች ከከፈሉበት መደበኛ እና ጭማሪ ታሪፍ ላይ 10 በመቶ ተቀናሽ ተደርጐ ገንዘባቸው እንደሚመለስላቸው አቶ ሃይሌ ጠቅሰው፤ 10 በመቶ የሚቀነሠውም መኪናው ነዳጅ አቃጥሎ በተቆረጠ ቲኬት ስለሚጓዝ ነው ብለዋል፡፡

 

Read 2793 times