Saturday, 05 October 2013 11:11

ለዓለም ኮከብ አትሌቶች ምርጫ ሶስት ኢትዮጵያውያን ታጭተዋል

Written by 
Rate this item
(3 votes)

               ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር (አይ.ኤ.ኤ.ኤፍ) በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ለ2013 የዓለም ኮከብ አትሌቶች ምርጫ በሁለቱም ፆታዎች የሚፎካከሩ እጩዎችን ስም ሲያስታውቅ ከእጩዎቹ መካከል ሶስት የኢትዮጵያውያን አትሌቶች ተካትተዋል፡፡ መሃመድ አማን ፤ ጥሩነሽ ዲባባ እና መሠረት ደፋር ናቸው፡፡ አትሌት መሃመድ አማን በ800 ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ከመሆኑም በላይ በርቀቱ የዳይመንድ ሊግ አሸናፊ ለመሆን የበቃ እና በዓመቱ ካደረጋቸው 11 ውድድሮች አስሩን ያሸነፈ ነው፡፡ ዘንድሮ በ5ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን የበቃችው አትሌት መሰረት ደፋር በርቀቱ የዳይመንድ ሊግ አሸናፊ እንደሆነች ሲታወቅ በ3ሺ ሜትር እና በ10ሺ ሜትር የዓመቱን ፈጣን ሰዓት በማስመዝገብ ተሳክቶላታል፡፡ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ በበኩሏ በ10ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ከመሆኗም በላይ በ10 ኪሎሜትር የዓመቱን ፈጣን ሰዓት አስመዝግባለች፡፡

በኮከብ አትሌት ምርጫው በሁለቱም ፆታዎች ለመጨረሻ ምዕራፍ የሚደርሱትን ሶስት እጩ ተፎካካሪዎች ለመለየት በድረገፅ በሚሰጥ የድጋፍ ድምፅ ይሰራል፡፡ የዓለም የአትሌቲክስ ማህበረሰብን በማሳተፍ የሚከናወነው የምርጫ ሂደት ከተጀመረ ሶስት ቀን አልፎታል፡፡ ለሶስቱ የኢትዮጵያ ምርጥ አትሌቶች በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ድረገፅ (www.iaaf.org) አስፈላጊ የሆነውን ድምፅ በመስጠት ድጋፍ ሊሰጥ ይቻላል፡፡ እድሉ ለሚቀጥሉት ሶስት ሳምንታት ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡ በዓለም ኮከብ አትሌቶች ምርጫ ታሪክ ሶስት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ተሸላሚ ሆነው ያውቃሉ፡፡ እነሱም በ1998 እኤአ የተሸለመው ኃይሌ ገብረስላሴ፤ በ2004 እና በ2005 እኤአ አከታትሎ ያሸነፈው ቀነኒሳ በቀለ እና በ2007 እኤአ ላይ የተመረጠችው መሰረት ደፋር ናቸው፡፡

Read 3020 times