Saturday, 05 October 2013 10:56

እንግሊዝኛና አስተርጓሚ

Written by 
Rate this item
(8 votes)

...በጊዜው ያጋጥመን ከነበረው አስቸጋሪ ሁኔታ አንዱ የአስተርጓሚዎች በእንግሊዝኛ ቋንቋ ያለመብሰል ነው፤ ቀደም ብዬ እንዳስረዳሁት ከስንዴ፣ እንክርዳድ እንደማይታጣ ከአስተርጓሚዎችም መካከል አንዳንድ ደካሞች (ሞራለ ቢሶች) ሲኖሩ አብዛኛዎቹ ግን፤ በተማሩት የተጠቀሙበትና ጥሩ ኢትዮጵያዊነታቸውን ያሳወቁበት ስለሆኑ ውለታቸው የሚዘነጋ አይደለም፡፡ በዚህ ላይ ልገልፀው የፈለግሁት ግን በጊዜው እንግሊዝኛ እናውቃለን፣ ብለው በአስተርጓሚነት የተቀጠሩት ብዙዎች ሲሆኑ ባለችሎታ ሆነው የተገኙት ግን ጥቂቶች ነበሩ፡፡ ይሁን እንጂ ለመግደርደርና ዐዋቂ ናቸው ለመባል ያህል ባላቸው ቁንጽል ዕውቀት እንግሊዝኛ እናውቃለን የሚሉና በተለይ ከዚህ እንደሚከተለው፤
…የስ ሰር (YES SIR)፣ ኦል ራይት ሰር (ALL RIGHT SIR)፣ ቬርይ ጉድ ሰር (VERY GOOD SIR) በሚለው አነጋገር ብቻ አዘውትረው በመጠቀም የሚብለጠለጡም ነበሩ፡፡

እነዚህ አስተርጓሚዎች ነን የሚሉት ሰዎች፤ በነዚህ ሦስት ቃላቶች አዘውትረው የሚጠቀሙበት ምክንያት ሁለት ነው ይኸውም አንደኛው በተመልካች ዘንድ እንግሊዝኛ ያለመቻላቸው እንዳይታወቅባቸው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ እንግሊዞቹ ለሚያቀርቡላቸው የቃል ጥያቄ ወይንም ለሚሰጧቸው ትእዛዝ ተቃዋሚ መልስ የሰጡ እንደሆነ (ኖ ሰር NO SIR) ያሉ እንደሆን ይህን ሊሉ የቻሉበት (የተቃወሙበትን) ምክንያት በእንግሊዝኛ አብራርቶ የማስረዳት ግዴታ ስለሚኖርባቸው፣ ከዚህ ሁሉ ጣጣ ለመራቅ የሚሻለው ነገሩ ቢገባቸውም ባይገባቸውም ጐላ ባለ ድምጽ የስ ሰር፤ ኦል ራይት ሰር ቬርይ ጉድ ሰር” ብሎ ዘወር ማለቱ የሚጠቅም ዘዴ መሆኑን ስላመኑበት ነው፡፡
ይሁን እንጂ ይህን የመሳሰሉት በእንግሊዝኛ ንግግር ደካማ የሆኑት አስተርጓሚዎች ትክክለኛ የሆነውን የሥራ ጉዳይ ስለሚመለከት ሁኔታ እንግሊዝኛውን ወደ አማርኛ ወይንም አማርኛውን ወደ እንግሊዝኛ በሚያስተረጉሙበት ጊዜ ንግግሩ አይሳካላቸው እንጂ “ትንሽ ዕውቀት መርዝ ነው” እንደተባለውና “የታሪክ ማስታወሻ” በተባለው መጽሐፍ በገጽ ፬፻፵ እንደተመለከተው ያልሆነውን ሆኗል ያልተባለውን ተብሏል በማለት፣ እንግሊዞቹንና እንግሊዝኛ የማናውቀውን ለማጋጨት፣ ባንዳንድ ሁኔታዎች ለማወናበድ አስችሏቸዋል፡፡ ከዚህ በስተቀር አማርኛና እንግሊዝኛ ቋንቋ ወዲያና ወዲህ እየሆኑ አንዳንድ አስፈላጊ ጉዳዮች በሚተረጐሙበትም ጊዜ ብዙ የሚያስቁ ሁኔታዎችን አድርሰው እንደነበረ በሚከተለው መስመር እገልጻለሁ፡፡
1ኛ፤ ሰዓት እላፊ (CURFEU) በሐምሌ ወር ፲፱፻፴፫ ዓ.ም አሥራ አንድ ሰዎች በሰዓት እላፊ ተይዘው 2ኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው ካደሩ በኋላ በጊዜው ለነበረው የኦ.ኢ.ቲ.ኤ ፍርድ ቤት ቀርበው በሚጠየቁበት ጊዜ፣ የፍርድ ቤቱ ዳኛ (እንግሊዛዊው) የተከሰሱበትን የነጋሪት ጋዜጣ አዋጅ ተመልክተው “የተከሰሳችሁት ስለሰዓት እላፊ የወጣውን ዐዋጅ ተላልፋችሁ በመገኘታችሁ ነው፤ ጥፋተኛ ናችሁ አይደላችሁም?” ሲሉ ለተከሳሾቹ ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡ አስተርጓሚውም ኬርፊው (CURFEU) የሚለውን የእንግሊዝኛ ቃል “ኩርፊያ” ብሎ በመተርጐም “እናንተ በኩርፊያ ወንጀል ተከሳችኋል፤ ጥፋተኞች ናችሁ አይደላችሁም?” ሲል በማስተርጐሙ፣ በአደባባዩ የነበሩት እንግሊዝኛ ቋንቋ የሚያውቁትና የማያውቁትም (ተከሣሾቹ) ጭምር አደባባዩን በሳቅ ከሞሉት በኋላ፣ ካሥራ አንዱ ተከሳሾች አንደኛው ባነጋገሩ ዝግ ያለው የባላገር ሰው ላስተርጓሚው በሰጠው መልስ “እኛ የታሰርነው በሰዓት እላፊ እንጂ በኩርፊያ አይደለም ደግሞስ ከዚያን በፊት የማንተዋወቅ ሰዎች በምን ተገናኝተን እንኳረፋለን፤” ጣሊያንም የፈጀን እርስዎን በመሰሉ አስተርጓሚዎች አሳሳችነት ነውና ይልቁንስ ነገሩን የጣሩልን” ሲል ስለተናገረ፣ ባደባባዩ ያለውን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን እንግሊዛዊውን ዳኛ ጭምር አስቋቸዋል፡፡
2ኛ፤ የ2ኛ ፖሊስ ጣቢያ አዛዥ የሆኑት እንግሊዛዊ መኮንን በሰልፍ አቁመውን “ከሦስት ቀን በኋላ ግርማዊ ጃንሆይ ይገባሉ፤ በጥበቃው በኩል ጥንቃቄ ማድረግ አለባችሁ፤ ስለዚህም ጉዳይ ከበላይ መሥሪያ ቤት ፕሮግራም ይደርሰን ይሆናል፤ ያለበለዚያም በነገው ቀን በአውሮፕላን ወረቀት ስለሚጣል ትክክለኛውን ከዚያ መረዳት ይቻላል” ሲሉ ፀጥታውን ማስከበር አለባችሁ፤ ይህን ባትፈጽሙ አውሮፕላን ቦምብ ይጥልባችኋል ብሎ በማስተርጐሙ ሁላችንም በነገሩ ከተደናገጥንና ጥቂት ካሰብን በኋላ፣ ምንም እንግሊዝኛ ባንችል አስተርጓሚው የተሳሳተ መሆኑ ስለገባን ሁላችንም ስቀንበታል፤ ስህተቱን የተረዱት የጣቢያው አዛዥም ገስፀውታል፡፡
ምንጭ (በብርጋዲየር ጄነራል ሞገስ በየነ
“ጊዜ እና ፖሊስ” በሚል ርዕስ ከተዘጋጀ መጽሐፍ የተቀነጨበ፤ ከ1935-1963)

 

Read 6300 times