Saturday, 05 October 2013 10:48

የተዘጋው የአሜሪካ መንግስትና የአሜሪካ ምስቅልቅል

Written by  አንተነህ ይግዛው
Rate this item
(0 votes)

የአገልግሎት፣ የቱሪዝም፣ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ክፉኛ ይጎዳሉ
የሩብ አመቱ ጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት በ0.3 በመቶ ሊቀንስ ይችላል

              ባለፈው ማክሰኞ ማለዳ በይፋ የተዘጋው የአሜሪካ መንግስት፣ መቼ እንደሚከፈት እርግጡን መናገር እንደማይቻልና የአገሪቱ ኮንግረስ የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴዎችን ማካሄጃ ገንዘብ የሚገኝበትን መላ ፈልጎ እስኪያገኝና የጋራ መግባባት ላይ እስኪደርስ ድረስ፣ መንግስት እንደተዘጋ መቆየቱ ግድ እንደሚሆን የዋሽንግተን ፖስቱ ዘጋቢ ብራድ ፕላመር ይናገራል፡፡
የአገሪቱ መንግስት መዘጋቱ በይፋ ከተገለጸበት ቅጽበት አንስቶ ጉዳዩ አለምአቀፍ መነጋገሪያ ሆኗል። የመንግስት መዘጋት በዜጎችና በአጠቃላዩ የአገሪቱ እንቅስቃሴ ላይ ምን አይነት ተጽዕኖ ያሳድር ይሆን የሚለው ጉዳይ የብዙዎች ጥያቄ ሆኗል፡፡
የአሜሪካ መንግስት መዘጋቱን ተከትሎ በቀዳሚነት የተደመጠው ተያያዥ ዜና፣ ፓንዳ ካም የተሰኘው የአገሪቱ ብሄራዊ መካነ እንስሳት መዘጋቱ ነበር፡፡ ይሄን የሰሙም ታዲያ፣ ነገሩ የእንስሳቱን ኑሮ ከማመሳቀል አልፎ፣ ይሄን ያህል የከፋና ዜጎችን የሚጎዳ መስሎ አልታያቸውም ነበር፡፡ የዋሽንግተን ፖስት ዘጋቢው ብራድ ፕላመር ግን ጉዳዩ ከዚህም የባሰ የከፋ ተጽዕኖ ያሳድራል ባይ ነው፡፡ እሱ እንደሚለው የተዘጋው መንግስት ፈጥኖ ካልተከፈተ ገና ብዙ ቀውስ መፍጠሩ አይቀርም፡፡ ብራድ ፕላመር ነገርየው የሚያሳድራቸውን ከፉ ተጽዕኖዎች በዝርዝር ዳሷቸዋል፡፡
ጉዳዩ በአፋጣኝ የሚያሳድረው ትልቁ ተጽዕኖ፣ የአገሪቱን ሰራተኞች ሰለባ እንደሚያደርግ ነው ዘጋቢው የሚናገረው፡፡ እሱ እንደሚለው፣ የአገሪቱ ኮንግረስ አፋጣኝ መፍትሄ ካልፈለገና መንግስት እንደተዘጋ የሚቆይ ከሆነ፣ ከ 2 ሚሊዮን በላይ የአገሪቱ የፌዴራል ሰራተኞች የሚገባቸውን ክፍያ በወቅቱ አያገኙም፡፡ 800 ሺህ ያህሉ ደግሞ ምናልባትም የሰሩበት ገንዘብ ሳይከፈላቸው ያለምንም ካሳ ባዶ እጃቸውን ወደቤታቸው ሊሸኙ ይችላሉ፡፡
የኢኮኖሚክስ ባለሙያው ማርክ ዛንዲ እንደሚሉት፣ በርካታ ሰራተኞች ከስራ መሰናበታቸው በአገሪቱ የመጨረሻ ሩብ አመት አጠቃላይ የምርት እድገት ላይ 0.3 በመቶ ቅናሽ ይፈጥራል፡፡ ከአገሪቱ ሰራተኞች አብዛኞች የሚገኙባት ሜሪላንድም፣ በየቀኑ በገቢና በሽያጭ ታክስ መልኩ ትሰበስብ የነበረውን 5 ሚሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ ታጣለች፡፡
ይህም ብቻ አይደለም፡፡ የአገሪቱ ተቋራጮችም እንቅስቃሴያቸው መገታቱን ተከትሎ ሰራተኞቻቸውን በገፍ ይቀንሳሉ፡፡ ይህም ተጨማሪ ቀውስ መፍጠሩ አይቀሬ ነው ተብሏል፡፡
የአገሪቱ የነባር ሰራተኞች ጉዳይ ባለስልጣናት፣ ነገሩ ክፉኛ አሳስቧቸው ለኮንግረሱ ስጋታቸውን እንደገለጹ ተነግሯል፡፡ ባለስልጣናቱ መንግስት ከሁለት ሳምንታት በላይ እንደተዘጋ የሚቆይ ከሆነ፣ ለአካል ጉዳተኞች ወይም ለጡረተኞች የሚሰጡት ቤሳቤስቲን ሳንቲም እንደማይኖራቸው አስጠንቅቀዋል፡፡ ይህ ደግሞ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ የሆኑ 3 ነጥብ ስድስት ሚሊዮን የቀድሞ ሰራተኞችን ተጠቂ ያደርጋል፡፡
ባለስልጣናቱ ከኮንግረሱ ጋር ባደረጉት ውይይት፣ አብዛኞቹ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ህይወታቸውን የሚመሩት ከመንግስት በሚያገኙት ድጎማ በመሆኑና ቀድመው እንዲዘጋጁ መረጃ ስላልተሰጣቸው ጉዳታቸው የከፋ እንደሚሆን አሳስበዋል፡፡
የአገሪቱ የጤናና የሰብዓዊ አገልግሎቶች ዲፓርትመንትም ጉዳዩ መላ እንዲበጅለት አበክሮ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡ ዲፓርትመንቱ እንደሚለው፣ የበሽታ ቁጥጥርና መከላከል ማዕከል የተባለው ድርጅት አመታዊውን የወቅታዊ ኢንፍሉዌንዛ ፕሮግራም ስራውን ለመስራት ሲዘጋጅ በተከሰተው የመንግስት መዘጋት ሳቢያ ስራውን ለማከናወን ተቸግሯል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፡፡ ድርጅቱ ለተላላፊ በሽታዎች ቁጥጥር በሚል ለመንግስትና አጋር አካላት የሚያደርገውን ድጋፍ ለማቆም እንደሚገደድ አሳውቋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በወረርሽኝ ፍተሻ፣ ቤተ-ሙከራ ድጋፍና በሃያ አራት ሰዓት የድንገተኛ ህመም ህክምና አገልግሎት ዘርፎች ይሰጥ የነበረውን አገልግሎትም በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚቀንስ ገልጧል፡፡
የአሜሪካ መንግስት መዘጋት ከሚያሳድራቸው የከፉ ተጽዕኖዎች መካከል የሚመደበው ሌላው ነገር ደግሞ፣ የአገሪቱ የምግብና መድሃኒት አስተዳደር አብዛኛዎቹን የምግብ ዋስትና ስራዎች ሊያቋርጥ መገደዱ ነው፡፡ ስራቸውን ለማቋረጥ ይገደዳሉ ተብለው የተጠቀሱት ሌሎች ተቆጣጣሪ አካላትም አሉ፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ኤጀንሲ የአየር ብክለትና የጸረ ተባይ መድሃኒቶች አጠቃቀም ቁጥጥሩን፣ የስራ ዲፓርትመንትም የክፍያና የስራ ሰዓታት ወይም የሰራተኞች ደህንነት ህጎችን በአግባቡ ተግባራዊ የማድረግ ስራውን ማቋረጣቸው አይቀሬ ነው እየተባለ ነው፡፡ እነዚህና ሌሎች መሰል ተቆጣጣሪ አካላት ስራ በፈቱበት ሁኔታ፣ የአገሪቱ እንቅስቃሴ ጤናማ ይሆናል ብሎ ማሰብ አይቻልም ይላል- የዋሽንግተን ፖስቱ ዘጋቢ፡፡
የአገሪቱ የግብርና ዲፓርትመንትም መንግስት ተዘግቶ በሚቆይባቸው ጊዜያት ሴቶች፣ ጨቅላዎችና ህጻናት ጤናማ ምግብ እንዲያገኙ የሚያደርገውን የገንዘብ፣ የመረጃና የጤና ክብካቤ አገልግሎት ድጋፍ ፕሮግራሙን ሙሉ ለሙሉ ያቋርጣል፡፡ በአገሪቱ የዚህ አገልግሎት ተጠቃሚዎች ቁጥር 9 ሚሊዮን እንደሚደርስም ዘገባው ያሳያል፡፡ ከፌደራል ድጋፍ የሚደረግላቸው ፕሮግራሞችም ቢሆኑ ከአንድ ሳምንት የዘለለ እድሜ ሊቆዩ እንደማይችሉ ተነግሯል፡፡
ለአነስተኛ የንግድ ተቋማት የሚደረገው የፋይናንስ ድጋፍና አቅርቦት ሌላው የችግሩ ሰለባ እንደሚሆን የተቀሰው ዘገባው፣ የሚመለከተው የመንግስት አካል ባለፉት አራት አመታት ከ 193 ሺህ በላይ ለሚሆኑ አነስተኛ የንግድ ተቋማት 106 ቢሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ በብድር መልክ መስጠቱን ያስታውሳል፡፡ የሰሞኑ ክስተት ግን ይሄን የገንዘብ አቅርቦት ፈተና ላይ ይጥለዋል እየተባለ ነው፡፡ ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ የተሰራ ጥናት፣ አመታዊ ገቢያቸው ከ5 ሚሊዮን ዶላር በታች ከሆነ መሰል የአገሪቱ ተቋማት 41 በመቶ የሚሆኑት ሁኔታው ከሶስት ወራት በላይ የሚቀጥል ከሆነ ሰራተኞቻቸውን ለመቀነስ እንደሚገደዱ ተናግረዋል፡፡
ሌላው ከአሜሪካ መንግስት መዘጋት ጋር ተያይዞ ተጎጂ ከሚሆኑ ዘርፎች መካከል እንደሆነ በዘገባው የተጠቀሰው የአገሪቱ የቱሪስት ንግድ ዘርፍ ነው። ከዚህ ጋር ተያይዞ የአገሪቱ ብሄራዊ ፓርኮች አገልግሎት ታዋቂዎቹን ዮስማይት፣ ግራንድ ካንዮን፣ አልካትራዝና የኒዮርኩን የነጻነት ሃውልት ጨምሮ ከ400 በላይ ብሄራዊ ፓርኮችን፣ ሙዚየሞችንና የቱሪስት መዳረሻዎችን ለመዝጋት እንደተገደደ ተነግሯል፡፡ ቱሪስቶችም ወደመጡበት እንዲመለሱ ይደረጋል ተብሏል፡፡ በቱሪዝሙ ዘርፍ የሚፈጠረው ቀውስ በአገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ ጉልህ የሆነ አሉታዊ ተጽዕኖ እንደሚያደርስ የገለጸው ዘገባው፣ እ.ኤ.አ በ1995 በተከሰተው ተመሳሳይ የአገሪቱ መንግስት መዘጋት 7 ሚሊዮን ያህል ጎብኝዎች ወደመጡበት እንዲመለሱ መደረጉን ያስታውሳል፡፡ ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ የአገሪቱ ኮንግረስ ምርምር አገልግሎት መረጃ እንደሚያሳየው፣ ክስተቱ የቱሪዝም ኢንዱስትሪውና አየርመንገዶች በየቀኑ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዶላሮችን ያሳጣቸዋል፡፡
በዋሽንግተን ፖስት ዘገባ ላይ እንደተጠቀሰው፣ በአገሪቱ አነስተኛ ገቢ ላላቸው 1 ሚሊዮን ያህል ህጻናትና ቤተሰቦቻቸው የትምህርት፣ የጤና፣ የምግብና የሌሎች አገልግሎቶች የሚሰጡ 1ሺህ ስድስት መቶ ያህል ፕሮግራሞች አሉ፡፡ እነዚህ ፕሮግራሞችም ታዲያ የመንግስትን መዘጋት ተከትሎ ቀስበቀስ ራሳቸውን መዝጋታቸው አይቀሬ ነው ተብሏል፡፡ ለነገሩ አሁንም ተጀምሯል፡፡ በኒዮርክ ካውንቲ መሰል አገልግሎት የሚያገኙ 864 ያህል የቅድመ አጸደ ህጻናት ተማሪዎች ትናንት ትምህርታቸውን አቋርጠዋል፡፡
ከመንግስት መዘጋት ጋር ተያይዞ ስጋት ውስጥ ከወደቁ ነገሮች መካከል ሌላው ደግሞ፣ የማህበራዊ ደህንነት አገልግሎት ነው፡፡ የአገሪቱ የማህበራዊ ደህንነት አስተዳደር ከአካል ጉዳተኞች የሚቀርቡ የድጋፍና ጥቅማጥቅም ጥያቄዎችን ተቀብሎ በአግባቡ የሚያስተናግድ በቂ ሰራተኛ ሊኖረው አይችልም ተብሏል፡፡ የቀድሞ ሰራተኞች የሚያቀርቧቸውን አቤቱታዎች ተቀብሎ የሚያስተናግደው ቦርድ የሚዘጋ መሆኑን ዘገባው ጠቅሷል፡፡ ይህም ከአካል ጉዳተኝነት ድጋፍና ጥቅማጥቅሞች ጋር በተያያዘ አቤቱታ ያቀረቡ የቀድሞ ሰራተኞች ውሳኔ ለማግኘት፣ የመንግስት ወቅታዊ ጉዳይ እልባት እስኪያገኝ እንዲጠብቁ ግድ ይላቸዋል፡፡
የአሜሪካ ብሄራዊ የጤና ኢንስቲቲዩትም ነገሩ መላ ይባል እያለ ነው፡፡ የተዘጋው ነገር አንዳች መፍትሄ ካላገኘ፣ የራሱን እርምጃ እንደሚወስድ ተቋሙ በይፋ ተናግሯል፡፡ መንግስት በዚህ ሁኔታ የሚቀጥል ከሆነ በህክምና ምርምር ማዕከሉ አገልግሎት ሲሰጣቸው የነበሩ ታካሚዎችን ሳያጋግሙ ከአልጋ ለማስወረድ እንደሚገደድ አስጠንቅቋል፡፡ የካንሰር ታማሚ የሆኑ ህጻናትን ጨምሮ፣ በየሳምንቱ በአማካይ 200 ታካሚዎችን ያለ ጊዜያቸው ሳያገግሙ እንደሚያሰናብት በመግለጽ፡፡
ለአገሪቱ መንግስት መዘጋት አንዳች መላ ካልተዘየደለት የሚደርሰው ምስቅልቅል መልከ ብዙ እንደሚሆን የሚናገረው የዋሽንግተን ፖስት ዘገባ፣ ብሄራዊ የጤና ኢንስቲቲዩት ለህክምና ሙከራዎች አዳዲስ ታማሚዎችን መቀበል ሊያቆም እንደሚችል ይጠቁማል፡፡ የመሬት አስተዳደር ቢሮም በህዝብ ቦታዎች ላይ የነዳጅ ዘይት ፍለጋ ለሚያከናውኑ ኩባንያዎች ፍቃድ መስጠቱን ሊያቋርጥ እንደሚችል፣ ልዕለ ሃያሏን አሜሪካ፣ ኢኮኖሚዋንና ህዝቦቿን፣ አልፎ ተርፎም ተስፋ አድርገው የተጠጓትን ስደተኞች ክፉኛ የሚጎዱ ብዙ፣ እጅግ ብዙ ነገሮች ሊሆኑ እንደሚችሉም ያትታል፡፡

 

Read 3897 times Last modified on Wednesday, 09 October 2013 12:04