Saturday, 05 October 2013 09:53

በጉምሩክ ሠራተኛው ላይ ከ15 ሚ.ብር በላይ ህገወጥ ሃብት ተገኘ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(6 votes)

    12 ቦቴዎችን በሌላ ሰው ስም ገዝተው ነበር የሁለት ዶዘሮችን ክፍያ ፈጽመው አንዱ ስራ ጀምሯል

የፌደራሉ የስነምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን የምርመራ ቡድን፤ በከባድ የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ከዋሉት የገቢዎችና ጉምሩክ መስሪያ ቤት የስራ ሃላፊዎች መካከል የአዳማ ጉምሩክ ቅርንጫፍ መስሪያ ቤት የህግ ማስከበር ኦፊሰር በሆኑት አቶ ተመስገን ስዩም ላይ ባካሄደው ተጨማሪ ምርመራ ከ15 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማውጣት ሁለት ዶዘሮችን መግዛታቸውን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ማግኘቱን አስታወቀ፡፡ ኮሚሽኑ ሐሙስ እለት ለመገናኛ መግለጫ እንዳመለከተው፤ ብዙሃን በላከው ተጠርጣሪው ቀደም ሲል በመስሪያ ቤቱ የስራ ሃላፊነት ላይ ሳሉ 12 የነዳጅ ማመላለሻ ቦቴ መኪናዎችን በሌላ ሰው ስም በመግዛት ለ3ኛ ወገን ሽያጭ የፈፀሙ ሲሆን ከሽያጩ ከተገኘው ገንዘብ ውስጥ 15 ሚሊዮን ብር በማውጣት ሁለት ዶዘሮችን ለመግዛት ክፍያ ፈጽመዋል፡፡

ክፍያ ከተፈፀመባቸው ዶዘሮች መካከል በ7.6 ሚሊዮን ብር የገዙትን አንዱን ዶዘር ቀደም ሲል ተረክበው ለድርጅት ያከራዩ ሲሆን 7.4 ሚሊዮን ብር የተከፈለበትን ሁለተኛውን ዶዘር ለመረከብ በዝግጅት ላይ እያሉ በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው መያዛቸውን ኮሚሽኑ ጠቁሟል፡፡

በአቶ ተመስገን ስዩም እጅ ላይ ተገኘ ከተባለው ህገወጥ ሃብት ጋር ግንኙነት እንዳላቸው የተጠረጠሩት አቶ ታደለ ብርሃኑ እና አቶ ወ/ሚካኤል ሃለፎም የተባሉ ሁለት ነጋዴዎች በቁጥጥር ስር ውለው ፍርድ ቤት ከቀረቡ በኋላ፣ የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸዋል፡፡ አቶ ተመስገን ስዩም በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ሲፈለጉ በነበረ ጊዜ በጋምቤላ በኩል አድርገው ወደ ሱዳን ለመሸሽ ሲሞክሩ፣ በቁጥጥር ስር መዋላቸው የሚታወስ ሲሆን በኮሚሽኑክስ ተመስርቶባቸው በማረሚያ ቤት ከሚገኙት የቀድሞ የገቢዎችና ጉምሩክ የስራ ሃላፊዎች አንዱ ናቸው፡፡ በተጠርጣሪው ላይ የቀረበውን የክስ ዝርዝር ለማዳመጥም ለጥቅምት 12 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቶ እንደነበር ይታወሳል፡፡

Read 3944 times