ጠብት አምቡላንስ ዝቅተኛ ኑሮ እየኖሩ የዩኒቨርስቲ መግቢያ ውጤት ላመጡ ሃያ አራት የኮርያ ሠፈር ተማሪዎች የኑሮ ክህሎት (Life skill) እና የመጀመሪያ ደረጃ ህክምና አሠጣጥ ስልጠና መስጠቱን እንዲሁም በዩኒቨርስቲ ቆይታቸው የሚገለግሉባቸዉ ቁሣቁሶች መርዳቱን አስታወቀ፡፡ ተማሪዎቹ በአብዛኛው የኮርያ ዘማች ልጆች መሆናቸውን የገለፁት የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ክብረት አበበ፤ ስልጠናውንና እርዳታውን መስጠት ያስፈለገው ማህበራዊ ግዴታን ከመወጣት አንፃር መሆኑን አመልክተው ለተማሪዎቹ የሻንጣ፣ የብርድልብስና የመማሪያ ቁሣቁሶች ከመለገሳቸውም በተጨማሪ የገንዘብ እርዳታ ማድረጋቸውንም ተናግረዋል፡፡
በሃገሪቱ ባሉ የተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች የተመደቡት እነዚህ ተማሪዎች፣ በትምህርት ቆይታቸው የሚያስመዘግቡት ውጤት እየታየ ላፕቶፕና ኮምፒዩተሮችን ጨምሮ የተለያዩ የትምህርት መርጃ መሳሪያዎች በሽልማት መልክ እንደሚሠጣቸው ቃል ተገብቶላቸዋል፡፡ ጠብታ አምቡላንስ የግል የአምቡላንስ አገልግሎት ሠጪ ድርጅት ሲሆን በሚሠጠው የመጀመሪያ ህክምና እርዳት እና የአምቡላንስ አገልግሎት ከተለያዩ ሃገር አቀፍና አለማቀፍ ተቋማት በተለያዩ ጊዜያት ሽልማት ማግኘቱን ስራ አስኪያጁ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡