Print this page
Saturday, 28 September 2013 14:00

“ሲኖዶሱ ስለመስቀሉ

Written by 
Rate this item
(5 votes)

መግለጫ እስኪሰጥ ህዝቡ በትዕግስት ይጠባበቅ”
ስለመስቀሉ ከሰማይ መውረድ በጀመሪያ መረጃው እንዴት ነው የደረሳችሁ?
መስቀሉ ከሰማይ ወረደ ስለሚባለው የሻለ መረጃ የምታገኙት ወረደ ከተባለበት ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪዎችና አገልጋዮች ነው። እኛ ከሰማይ ወረደ ከተባለ ከቀናት በኋላ ነው በስፍራው የተገኘነው፡፡ ስለዚህ እነሱ እንደነገሩን እንጂ አይተናል ሰምተናል ብለን አይደለም መረጃ የምንሰጣችሁ፡፡
እነሱ ግን እንዴት እንደወረደ አይተናል ስላሉ መረጃውን ከእነሱ ነው ያገኘነው፡፡ ከእነሱ የተነገረን እንግዲህ ነሐሴ 23 ለ24 አጥቢያ ሌሊት እንደወረደ ነው፡፡ ነሐሴ 23 የቅድስት ክርስቶስ ሰምራ ክብረ በአል ነው፡፡ ጽላቷም ከቅዱስ ገብርኤል ጋር በተደራቢነት አለ፡፡ ሌሊት ማህሌት ቆመን ሳለ ከፍተኛ ድምጽ ተሰማ ነው የሚሉን፡፡ ተደናግጠን ስንወጣ ወደ ቤተልሄሙ አካባቢ መስቀሉ ወድቆ የሚንቦገቦግ ብርሃን አየን ነው ያሉት፡፡ ወዲያውኑ ሲነጋ እንዳንነካ ፈርተን ማንሳትም አልቻልንም፤ ነገር ግን በወቅቱ ዝናብ ስለነበር እዚያው ላይ መስቀሉ ሳይነሳ ድንኳን ተከልንበት ነው ያሉን፡፡ የታቦት መጐናፀፊያ ለማልበስም ወደ መስቀሉ ሳንቀርብ፣ ወርውረን አለበስነው ብለውናል፡፡ እኛ ነሐሴ 24 ወዲያውኑ ከሰአት ነበር የሄድነው፡፡ ስንሄድ ከባድ ዝናብ ስለዘነበና ቦታውም በጣም አስቸጋሪ ስለሆነ መድረስ አልቻንም፤ ተመለስን፡፡ በ25 እንዲሁ ጥረት አድርገን ነበር፡፡ አልተሳካም። ነገር ግን በ27 ከሰዓት በኋላ ሄድን፡፡ መንገዱ እጅግ ፈታኝና በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ ምንም ማድረግ ስለማይቻል ነው እንጂ መንገዱ ከአቅሜ በላይ ነበር፤ ነገር ግን ሊቀጳጳሱ ካልመጡ ለማንሳት እንቸገራለን ስላሉ እንደምንም ቦታው ደረስን።
ህዝቡም በጣም ይጐርፍ ነበር፡፡ ፀጥታ አስከባሪዎችም በብዛት ነበሩ፡፡ ወደ 10 ሰአት አካባቢ ደረስን፡፡ የት ነው ያለው አልናቸው። ወደ ድንኳኑ መሩን፡፡ መሬት ላይ ወድቆ ተመለከትነው፡፡
በወቅቱ ከመሬቱ ላይ እንዲነሳ እነሱ ብዙም ፍቃደኞች አልነበሩም፡፡ እዚያው ላይ እያለ ቤተክርስቲያን እንዲሠራለት ነው የፈለጉት፡፡ ነገር ግን ቤተክርስቲያን የሚሰራለት ከሆነም መስቀሉ መሬት ላይ ሆኖ አይደለም የሚቆፈረውና የግድ ወደመቅደሱ መግባት አለበት አልናቸው፡፡ የእግዚአብሔር ፍቃድ ከሆነ ለወደፊት ሊሠራ ይችላል ብለናቸው ውዳሴ ማርያም ደግመን የሚገባውን ፀሎት ከካህናቱ ጋር አደረስን፡፡ ከዚያም ወደ ድንኳኑ ገብተን መስቀሉን አነሳን። መጀመሪያ እኔ ነበርኩ መስቀሉን ያነሳሁት። ከዚያም ሰባኪያኑ እንዲይዙት አድርገን ቤተክርስቲያኑ አንድ ጊዜ ዞረን፣ ወደ መንበረ ታቦቱ እንዲገባ አደረግን፡፡ እስካሁን እንግዲህ ይህ ነው ያለው ሂደት፡፡
መስቀሉ ሲነሳ ብርሃናማና የሚያቃጥል ነበረ፣ ብዙ ተአምራቶችም ታይተዋል ተብሏል? በእርግጥ እነዚህ ነገሮች ነበሩ?
ያቃጥል ነበር የሚለው እንደው የሚያቃጥል ቢሆን ኖሮ መቼ እናነሳው ነበር፤ አናነሳውም። እኔ እንደዛ መስሎኝም ነበር የሄድኩት እንጂ መነኮሳቱ ማንሳት ይችሉ ነበር፡፡ የሚያቃጥል ነበረ፣ የሚበራ ነበረ ምናልባት ጨለማ ሲሆን ታይቶ ይሆናል እንጂ እኛ ምንም አላየንም፡፡
ወርቃማና የሚያንፀባርቅ ነው የተባለ ነውስ?
እንግዲህ ወደፊት ስለመስቀሉ በስፋት የሚገለጽ ይሆናል፡፡ ሰዎችም በተለያዩ መንገዶች ስለመስቀሉ እየጠየቁን ነው ጉዳዩን ለሲኖዶሱ አቅርበን፣ ሲኖዶሱ የሚሰጠውን መመሪያ ተቀብለን ያለውን ነገር እንገልፃለን፡፡ እንግዲህ አሁን ህዝጀ ምዕመኑ ግማሹ ያለውን ነገር ተቀብሎ ይሄዳል ግማሹ ደግሞ እንዲሁ ለማታለል ነው ይላል፡፡ በዚህ ሁኔታ ህዝቡ ግራ የተጋባ በመሆኑ የግድ ሀገ ስብከታችን ሰፋ ያለ መግለጫ የሚሠጥበት ይሆናል፡፡ ብዙ የተባለለት ጉዳይ ስለሆነም የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ የግድ ያስፈልጋል፡፡ እዚያ ካሉ ሰዎች ጋርም ሰሞኑን እየተነጋገርንበት ነው፡፡
መስቀሉ በቅዱስ ሲኖዶሱ እውቅና ባላገኘበት ሁኔታ ፎቶግራፉን በ10 ብር ለሽያጭ ማቅረብና ገቢ ማሰባሰብ አግባብ ነው?
እንግዲህ ይሄን የመሳሰለውን ጉዳይ ለማስተካከል ከቤተክርስቲያኑ አስተዳደሮች ጋር እየተነጋገርን ነው፡፡ ችግሩ ምን መሰላችሁ? ቤተክህነት እውቅና ሳይሰጠው ቀድሞ ህዝቡ እውቅና ይሰጠዋል፡፡ እኔ ሄጄ በነበረ ጊዜ ስለመስቀሉ አስተያየት ብሰጥ ኖሮ ምን አይነት ትርምስ ይፈጠር እንደነበረ ትገነዘቡታላችሁ ብዬ አምናለሁ፡፡ የሆነ ሆኖ ለወደፊት በስፋት ትምህርት እንዲሰጥ ጥረት ይደረጋል፡፡ የቋሚ ሲኖዶሱ የሚሰጠው ልዩ መመሪያ ይኖራል፤ ከዚያ በኋላ መግለጫ ይሰጥበት ሲባል በኋላ መረጃ በስፋት ይሰጣል፡፡
ብዙ ጊዜ ተመሳሳይ ተአምራት ታይተዋል ይባላል፡፡ ለእነዚህ ተአምራት እውቅና የሚሰጠው የትኛው አካል ነው?
ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡
ሲኖዶሱ ካልሰጠ ተቀባይነት አይኖረውም?
አዎ አይኖረውም፡፡ ስለዚህ መስቀሉም ቅዱስ ሲኖዶሱ ውሣኔ ካልሰጠ ተቀባይነት የለውም። በመሠረቱ መስቀሉ ያቃጥላል፣ ይፋጃል የሚባለው ሃሰት ነው፤ መስቀል ይፈውሳል እንጂ አያቃጥልም፡፡ እንዲህ ከዚህ ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን በተመለከተ ለወደፊት በስፋት ትምህርት የሚሰጥበት ሊሆን ይችላል፡፡
በዚህ ላይ ሲኖዶሱ መቼ ነው ውሣኔ የሚያሳልፈው?
እንግዲህ ዛሬ ከሰአት የቤተክርስቲያኗን አስተዳዳሪዎች ጠርተናቸዋል (ይህ ቃለ ምልልስ የተደረገው ማክሰኞ ጠዋት ነው) ቅዱስ ሲኖዶሱ መረጃ ከነሱ ይጠይቃል፤ ከምን ተነስተው እንደዚህ እንዳሉ ከዚያ በኋላ ጉዳዩ በውይይት እስኪታይ ጊዜ ይወስዳል፡፡ ስለዚህ በዚህን ጊዜ ውሣኔ ይተላለፍበታል ብሎ ለመናገር አሁን አይቻልም፡፡
መስቀሉን ብፁዕነትዎ ሄደው ተመልክተውታል፡፡ ታዲያ ስለመስቀሉ በእርግጠኝነት መናገር እንዴት አይቻልም? ፓትርያርኩም ባሉበት ነው የሚታየው ብላችኋል?
ፓትሪያርኩ እሄዳለሁ አላሉም እስከመጨረሻውም ላይሄዱ ይችላሉ፡፡ አይደለም እሣቸው እኔም ላልሄድ እችል ይሆናል፡፡ ፓትርያሪኩ ውሣኔ የሚያስተላልፉ ከሆነም በየደረጃው ያሉ ፈፃሚዎች ጉዳዩን የሚከታተሉት ይሆናል፡፡ አሁን ላይ ብዙ መናገሩ ለስህተት ይዳርጋል፡፡ እንዳልኳችሁ የቋሚ ሲኖዶሱ ውሣኔ ይጠበቃል፡፡
ቢያንስ በስልጣን ደረጃ እርስዎ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀጻጳስ ነዎት፡፡ መስቀል ወርዷል ተብሎ ፎቶግራፉ ለሽያጭ ሲቀርብ ዝም ብሎ መመልከቱ ተገቢ ነው? ገንዘቡስ በምን ሞዴል ነው ገቢ የሚሆነው?
ሞዴልማ አድባራቱ ሁሉ አላቸው፡፡ በቤተክርስቲያናችን መመሪያ መሠረት፣ የአንድ አጥቢያ ቤተክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ ወሳኝ አካል ነው፤ ቤተክርስቲያኗን ወክሎ ይከሳል፣ ይከሰሳል ውል ይዋዋላል፣ የልማት ስራ ይሰራል፡፡ ስለዚህ ሰበካ ጉባኤው ሙሉ ስልጣን አላቸው፡፡ ስርቆትና ማጭበርበር ተፈፀመ የሚባል ከሆነ አጣሪ አካል ሄዶ ነው ሪፖርቱ የሚመጣው፡፡ ነገር ግን የትኛውም ቤተክርስቲያን በተቀመጠለት የአሰራር መመሪያ ገንዘብ የመሰብሰብ መብት አለው፡፡ ይሄ መስቀልም ሰበካ ጉባኤው ወስኖ ፎቶግራፉ 10 ብር ወይም 5 ብር እየተሸጠ ለህዝቡ ይሰራጭ ብሎ ነው ሊሆን የሚችለው፡፡ በትክክልም በዚህ መል/መ ገቢው ለቤተክርስቲያኑ ከሆነ ህጋዊ አሠራር ነው፡፡
ወረደ የተባለው መስቀል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የምትጠቀማቸው የመስቀል አይነት አይደለም የሚሉ አስተያየቶችም እየተሠነዘሩ ነው…
እንግዲህ ስለመስቀሉ አሁን ዝርዝር ነገር መናገር አልችልም፡፡ በእርግጥ ከሠማይ ወርዷል? የማን መስቀል ነው? ከየት የመጣ ነው? የሚለው ከቋሚ ቅዱስ ሲኖዶስ ውሣኔ በኋላ እንገልፃለን፡፡ ውሸት ሆኖ ከተገኘም ሠዎቹ ተጠያቂ ሊሆኑበት ይችላል፡፡
እርስዎ መስቀሉን ከተመለከቱት ይሄ የኦርቶዶክስ ነው አይደለም ለማለት እንዴት ከበድዎት?
እንደነገርኳችሁ የአንድ ሠው አስተያየት ተገቢ አይደለም፡፡
ቅዱስ ሲኖዶሡ መስቀሉን አስቀርቦ ከተመለከተ በኋላ የሚሠጠው ውሣኔ የግድ ነው። ለነገሩ መስቀል መስቀል ነው፤ ይሄ የእገሌ ነው ያ የእኔ ነው የሚባል አይደለም፡፡ እንግዲህ መስቀሉ ላይ የሥነ ስቅለት ምስል አለበት፡፡ ይሄ አሣሣል የኛ የኦርቶዶክሣያውያን አይደለም የሚለውን የሲኖዶሡ ውሣኔ የሚያረጋግጠው ይሆናል፡፡ ሲኖዶሡ ውሣኔ እንሠጣለን እያለ በዋዜማው እኔ ሌላ ነገር ብናገር አግባብ አይሆንም፡፡ ህዝቡንም ያምታታል፡፡
ለህዝቡ የሚያስተላልፉት መመሪያ ካለ?
እንግዲህ ይሄ በኛ ሃገር ብቻ አይደለም የሚፈጠረው፡፡ በግብፅ (ዘይቱና) እመቤታችን ታየች ተብሎ እኔም አይቸዋለሁ፡፡ አሁን በቅርቡ ደግሞ በሩሲያም ሠማይ ላይ ትልቅ መስቀል ተስሎ ታየ ተብሎ በየሚዲያው ሲነገር የሩስያ ቤተክርስቲያን መግለጫ ስትሠጥበት ነበር፡፡ እና ይሄ በኛ ብቻ ሣይሆን በሁሉም ያለ ነውና ህዝቡ እውነታውን ለማወቅ መታገስ አለበት። ሲኖዶሡ መግለጫ ቢሠጥበት እንኳ ሁሉም ህዝብ በእኩል አረዳድ አይረዳውም፡፡ ግማሹ ተአምር ነው ሊል ይችላል፡፡ ሌላው አይደለም ሊል ይችላል። ለማንኛውም ከቅዱስ ሲኖዶሡ ውሣኔ በኋላ በየሚዲያው መግለጫ የሚሠጥበት ይሆናል፡፡ ህዝቡ ሲኖዶሡ ውሣኔ እስኪሠጥበት ድረስ “ይሄ ነው ያ ነው” ሣይል፣ ተረጋግቶ የራሱን ትችትና ውሣኔ ሣይጨምርበት እንዲጠብቅ እንጠይቃለን፡፡
ውሣኔው በቅርቡ በመገናኛ ብዙሃንና በየቤተክርስቲያኑ የሚሠጥ ይሆናል፡፡ እስከዚያው መታገስ ያስፈልጋል፡፡

Read 4769 times
Administrator

Latest from Administrator