Saturday, 28 September 2013 10:49

ኤልጂ በመኪና ባትሪ የሚሰራ ቴሌቪዥን ለገበያ አስተዋወቀ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(1 Vote)

የ600 ሺህ ብር ቴሌቪዥን ለገበያ አቅርቧል

         አለምአቀፉ የደቡብ ኮሪያ የኤሌክትሮኒክስ ኩባንያ ኤልጂ፣ ከሜትሮ ፒኤልሲ ጋር በመተባበር በመኪና ባትሪ የሚሰራ ቴሌቪዥን ለኢትዮጵያ ገበያ አስተዋወቀ፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት ለገበያ በስፋት እንደሚያቀርብም ተገልጿል፡፡ በከተማችን ሁለትና ሶስት ቀን እየጠፋ ለሚመጣው የመብራት ችግር መፍትሔ ይሰጣል፣ መብራት የሌለባቸውን አካባቢዎችም ታሳቢ አድርጓል የተባለው ባለ 22 ኢንች LED ቴሌቪዥን፤ ከፍተኛ ጥራትና ማራኪ ቀለም ያለው ሲሆን በባትሪም በኤሌክትሪክ ሀይልም መስራት ይችላል ተብሏል፡፡ የኩባንያው የሆም ኢንተርቴይንመንት ረዳት ፕሮዳክት ማናጀር ሚስተር ቢዮጃንግ እንዳብራሩት፤ የቴሌቪዥኑ መጠን 22 ኢንች የሆነው ከመኪናው ባትሪ ጋር ወደተለያዩ ቦታዎች ይዞ ለመንቀሳቀስ ቀላል እንዲሆን ታስቦ ነው፡፡

በ7500 ብር ለገበያ የሚቀርበው ይህ ቴሌቪዥን ከዚህ በፊት ያልተሞከረ የመጀመሪያው ቴክኖሎጂ እንደሆነም ሚስተር ጃንግ አብራርተዋል፡፡ “ማንኛውም የመኪና ባትሪ ሙሉ ቻርጅ ከተደረገ ቴሌቪዥኑ ለ13 ሰዓታት በጥራት መስራት ይችላል” ያሉት ረዳት ፕሮጀክት ማናጀሩ፤ በተለይ የሃይል እጥረትና መቆራረጥ በሚከሰት ጊዜ የቴሌቪዥን ሥርጭት እንዳይስተጓጐል ይታደጋል ብለዋል፡፡ የትኛውም 70 አምፒር ያለው የመኪና ባትሪ፤ ቴሌቪዥኑን እንደሚያሰራውና አጠቃቀሙም ቀላል እንደሆነ ተብራርቷል፡፡ ኤልጂ ከአንድ ወር በፊት በዓለም የመጀመሪያ የተባለውን ባለ 84 ኢንች 3D ቴሌቪዥን ለአገራችን ገበያ አቅርቧል፡፡ በ600ሺህ ብር የሚሸጠው ቴሌቪዥኑ፤ በምስል ጥራቱ እና በአጠቃላይ ይዘቱ ከፍተኛ የቴክኖሎጂ ፈጠራን ያካተተ ነው ተብሏል፡፡

ከኮምፒዩተሮች ጋር ማገናኘትና የፈለጉትን ዳታዎች ማስተላለፍም እንደሚችል ተጠቁሟል፡፡ በተያያዘ ዜና ኤልጂ “G2 ፍላግሺፕ” ስማርት ስልክ በያዝነው ወር መጨረሻ ወደ አገራችን ሊያስገባ እንደሆነ የተገለፀ ሲሆን ስልኩ ሙሉ በሙሉ 3D የሆነ ባለ አምስት ኢንች ስክሪን እንዳለው ታውቋል። ለረጅም ሰዓት የሚዘልቅ ባትሪ በውስጡ በያዘው የፕሮሰሰር አይነት ከአለም ቀዳሚ ስማርት ስልክ እንዲሆን አድርጐታል ሲሉ የኤልጂ ኤሌክትሮኒክስ ሞባይል ክፍል ሃላፊ ዶ/ር ጆንግ ሲኦክ ገልፀዋል፡፡ ባለ 13 ሜጋፒክስል ካሜራ የተገጠመላት ስማርት ስልክ፤ በየትኛውም ሁኔታ ጥርት ያለ ምስል ያስቀራል ተብሏል፡፡ ስልኩ በተጨማሪም የስልክ ጥሪ ለማስተናገድ ወደ ጆሮአችን ስናስጠጋው ራሱ የሚያነሳ ሲሆን እንደ ሪሞት ኮንትሮል (የርቀት መቆጣጠሪያ) መሳሪያም ያገለግላል ተብሏል፡፡

Read 6511 times