Saturday, 21 September 2013 11:30

በፑሽኪን አዳራሽ መጻሕፍት ይመረቃሉ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

“የፍቅር ኬምስትሪ” ተመረቀ፤ “የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ገመና” ለንባብ በቃ

በቶሌራ ፍቅሩ ገምታ የተፃፈው “Raayyaa Dhugaa” የተሰኘ የኦሮምኛ ረዥም ልቦለድና የሙሉጌታ ጌቱ “ሰይጣን አሳስቶኝ” የአማርኛ የግጥም መድበል ዛሬ እና ሰኞ በፑሽኪን አዳራሽ እንደሚመረቁ ተገለፀ፡፡ ዛሬ ከቀኑ 8 ሰዓት በማዕከሉ ፑሽኪን አዳራሽ የሚመረቀው የቶሌራ ፍቅሩ ገምታ የኦሮምኛ ረዥም ልብወለድ፣ በኦሮሞ ሕዝብ ማህበራዊ እውነታ ላይ ተንተርሶ የተፃፈ ሲሆን የምረቃ ሥነስርዓቱን የሩስያ ሳይንስና ባህል ማእከል ከኢትዮጵያ ደራስያን ማሕበር እና ከኦሮሞ ደራስያን ማህበር ጋር እንዳዘጋጁት ለማወቅ ተችሏል፡፡

ደራሲው ካሁን ቀደም ‘Immimman Hadhaa’ የተሰኘ ሌላ መጽሐፍ አዘጋጅተው አሳትመዋል፡፡ “ሰይጣን አሳስቶኝ” የተሰኘው የግጥም መድበልም እንዲሁ የፊታችን ሰኞ ምሽት በ11፡30 በማዕከሉ የሚመረቅ ሲሆን የመፅሃፉ ገጣሚ አቶ ሙሉጌታ ጌቱ፣ የባሕል ማእከሉና የኢትዮጵያ ደራስያን ማሕበር አባል ናቸው፡፡ በሌላም በኩል በብርሃኔ ንጉሤ የተዘጋጀው “የፍቅር ኬምስትሪ ሴቶችን የመማረክ ጥበብ” የተሰኘው መጽሐፍ፣ከትላንት በስቲያ ምሽት ተመረቀ፡፡ የመፅሃፉ አዘጋጅ “ኢትዮፒካሊንክ” የተባለው የሬዲዮ ፕሮግራም መስራችና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ብርሐኔ ንጉሴ ሲሆን በ250 ገፆች የተቀነበበው መፅሃፉ፣ በ55 ብር እንደሚሸጥ ለማወቅ ተችሏል። በተማሪዎች አንደበት ተነገሩ የተባሉ እውነታዎችን ያካተተና በሄለን መልካሙ የተዘጋጀ “የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ገመና” የተሰኘ መጽሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ 134 ገፆች ያሉት መጽሐፍ፣ ለገበያ የቀረበው በ35 ብር ነው፡፡

Read 2890 times