Monday, 16 September 2013 08:01

“ልጃገረዷን በግድ ቢይዛት አፍንጫውን ይፎንኑት”

Written by 
Rate this item
(2 votes)

“ለግብረሰዶማውያን ግን ቅጣታቸው ሰይፍ ነው!”
“ልጃገረዷን በግድ ቢይዛት አፍንጫውን ይፎንኑት፡፡ ለእርሷም ከገንዘቡ ሲሶውን ይስጧት። አስራ ሶስት ዓመት ሳይሆናት አስቀድሞ ልጃገረዲቱን የያዛትን ሰው አፍንጫውን ይፎንኑት፡፡ ከገንዘቡም እኩሌታውን ለእርሷ ይስጧት፡፡”
ይህ ሕግ ነው፤ ሴቶችን ከእንስሳዊ ጥቃት ለመታደግ ከ570 ዓመት በፊት የተደነገገ፡፡ ዘመኑ የአገራችን ሥነ ጽሑፍ አብቦበት እንደነበረ የሚነገርለት ነው - የአፄ ዘርዓ ያዕቆብ (1434-1468) ዘመነ መንግስት፡፡ ለሥነ ጽሑፉ መዳበር ትልቁን ድርሻ የሚይዙት ከጉንዳንጉዶ ገዳም የተነሱት የአባ እስጢፋኖስና ደቀመዛሙርታቸው አዲስ ሃሳብ ማቀንቀን ነው፡፡ መነኮሳቱ ለሚያነሱት አዲስ ነገረ መለኮት መልስ ለመስጠት ሲባል በርካታ መጻሕፍት በንጉሱ እና በተቃራኒው ወይም በነባሩ አስተሳሰብ መመራትን በሚሹ መነኮሳት ይጻፉ ነበር፡፡
“ፍትሐ ነገሥት” የተባለው የሕግ መጽሐፍ ሥራ ላይ የዋለውም ከዚያ የፍትጊያ ዘመን ጀምሮ ነው፡፡ በ1923 ዓ.ም በወጣው ሕገ መንግሥት እስከተተካ ድረስም ለአራት መቶ ሰማንያ ዘጠኝ ዓመታት መንግሥትና ሃይማኖት/በተለይ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት/ በተግባር ሲያውሉት ቆይተዋል፡፡
ዛሬ “የሕግ ትምህርት ቤት” እንደሚባለው ድሮ ፍትሐ ነገሥት ራሱን ችሎ ወይም ከትርጓሜ መጻሕፍት ጋር በአንድ ጉባኤ ትምህርቱ ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ ፍትሐ ነገሥት የተማሩት ሊቃውንትም ከነገሥታቱ የፍርድ አደባባይ ላይ በመገኘት ነገሥታቱ በፍትሐ ነገሥቱ ህግጋት መሠረት የፍርድ ሥራቸውን እንዲያከናውኑ ያግዙ ነበር፡፡
የፍትሐ ነገሥቱ ድንጋጌዎች የተመሠረቱት በብሉይና አዲስ ኪዳን መጻሕፍት ላይ ሲሆን በተለይ አስገድዶ መድፈርንና ግብረ ሰዶማዊነትን በተመለከተ የሚያስገርሙና ጠንከር ያሉ ድንጋጌዎችን ይዞ ይገኛል፡፡ በነገራችን ላይ ኢትዮጵያ የሕግ ቅርስ ካላቸው ጥቂት የዓለማችን አገሮች አንዷ እንድትሆንም አስችሏታል፡፡ ህጉ (ፍትሐ ነገሥት) በተለይ ጥቃት ለሚደርስባቸው ሴቶች ተገቢ መፍትሔ እንደነበረው ከተደነገጉት አናቅጽ መረዳት ይቻላል፡፡
“ያልተነካ ግልግል ያውቃል” እንደሚባለው ምን አልባት “ሕጉ የሚጥለው ቅጣት ጠንካራ ነው፤ ኋላቀር ነው” ሊባል ይችላል፡፡ ግን በወቅቱ ልጃገረድ ደፋሪዎች አፍንጫቸው ይፎነን (ይቆረጥ) ነበር። ቅጣቱ የሚያሳየው ጭካኔን ሳይሆን ወንጀሉ ምን ያህል ትኩረት እንደተሰጠው ነው። እናም በወቅቱ አፍንጫ ፎናና (ቆራጣ) ሰው ከታየ ለምን እንደተቆረጠ ምክንያቱ ግልጽ ነበር፡፡ ወንጀል አድራጊውም ከደረሰበት የአካል ጉዳት ይልቅ የማህበረሰቡ መጠቋቆሚያ መሆኑ እያሳፈረው ዕድሜውን በሰቀቀን መግፋት ግድ ይሆንበታል። አካሉን ከማጣቱ ሌላ ግማሽ ሃብቱ በተደፋሪዋ ስለሚወረስበት የሰራው ወንጀል የአካል ብቻ ሳይሆን የምጣኔ ሃብት ጣጣ ስለሚያስከትልበት ውርደቱና የሞራል ስብራቱ ከተደፋሪዋ በላይ ይሆናል፡፡ ቅድመ 1923 የነበሩ ነገሥታት ይህን ህግ በተገቢው መንገድ ስለሚተረጉሙ ከመሰል ድርጊት ሁለመናን መሰብሰብ ግዴታ ነበር፡፡
በፍትሐ ነገሠቱ አንቀጽ 48 ላይ የተደነገገው ይህ ጠንካራ ሕግ፣ ዛሬ ተግባራዊ ቢሆን ስንቱ አፍንጫ ፎናና ይሆን ነበር? ምክንያቱም በ1949 ዓ.ም ወጥቶ ከ48 ዓመታት በኋላ በ1997 ዓ.ም የተሻሻለው የወንጀል ህጋችን አንቀጽ 620 (1) ለተመሳሳይ ጥፋት የሚጥለው ቅጣት ከአምስት እስከ አስራ አምስት ዓመት የሚደርስ እስራት ነው፡፡
የተጠቂዋ ዕድሜ ከ18 ዓመት በታች ከሆነ፣ በተከሳሹ ጥበቃ ወይም ቁጥጥር ሥር የምትገኝ ወይም የእሱ ጥገኛ ከሆነች፤ ወይም በዕድሜ መግፋት፣ በህመም፣ ወይም በሌላ ምክንያት የድርጊቱን ምንነት በውል ለይታ በማታውቅ ሴት ላይ ሲሆን፤ የተደፈረችው ከአንድ በላይ በሆኑ ወንዶች ሲሆን፣ ቅጣቱ ከአምስት እስከ 20 ዓመት በሚደርስ እሥራት እንዲሆን ይደነግጋል (620፡2) እድሜዋ ከ13 ዓመት በታች በሆነ ሕጻን ላይ ለሚፈፀም ጥቃትም ህጉ ከ15-25 ዓመት እስራት ቅጣት ይደነግጋል፡፡
አስገድዶ መድፈሩ ከባድ የአካል ወይም የአዕምሮ ጉዳትን ወይም ሞትን ያስከተለ ከሆነ ግን “ቅጣቱ የዕድሜ ልክ እሥራት ይሆናል (620፡3)” ይላል፡፡ ግን እድሜ ልክ እስራት 25 ዓመት ሲሆን ጥፋተኛው 20 ዓመት ከታሰረ አምስቱን ዓመት ሳይቀጣ በአመክሮ ይለቀቃል፡፡
ይህ ታላቁ የዘመናችን ቅጣት ነው፡፡ ቅጣቱ ከባድ ይመስላል፤ ግን ከፍትሐ ነገሥቱ ድንጋጌ አንቀጽ 48 ጋር ሲገናዘብ ደካማ ነው፡፡ ምክንያቱም ደፋሪው የህጻናትን ህይወት በዘላቂነት የተጐዳ ስለሚያደርገው፣ የፈፀመው ድርጊትም እንስሳዊ ስለሆነ ጠንከር ያለ ቅጣት ይገባው ይመስለኛል፡፡
በመገናኛ ብዙሃን በተደጋጋሚ የምንሰማውና የምንናበው ድርጊት በእጅጉ ይሰቀጥጣል፡፡ የ60 ዓመት አዛውንት የሶስት ዓመት ሕፃን መድፈሩ፣ ወይም የ20 ዓመት ወጣት የ70 ዓመት ባልቴት ማዋረዱ፤ ሶስት ወይም አራት ወሮበሎች አንዲትን ደካማ ሴት በህብረት ማጥቃታቸው ወዘተ እጅግ በጣም አሳፋሪም ነውረኛም ድርጊት ነው፡፡ ታዲያ ለእንዲህ ዓይነቱ ነውረኛና አደገኛ ድርጊት ቆንጠጥ የሚያደርግ ቅጣት ካልተጣለ እንዴት ነው “የጾታ ዕኩልነት ተከብሯል” የሚባለው?
አፍንጫ የመፎነኑ ቅጣት የሚያሳየን ትልቅ ቁምነገር በቀልን አይደለም፤ ይልቁንም በተጠቂዋ ሥነልቡና እና ዘላቂ ህይወት ላይ ምን ያህል ከባድ ጉዳት እንደደረሰ ነው፡፡ ለዚህም ነው በአጥቂው ላይ ቋሚ ምልክትና የገንዘብ ቅጣት ይወሰን የነበረው፡፡ የአሁኑ የወንጀል ህጋችን አጥፊውን ይቀጣል እንጂ ተበዳዩ እንዲካስ አያደርግም፡፡ ፍትሐ ነገሥት ግን አጥፊው ከባድ ቅጣት ተቀጥቶም ተበዳዩን ይክሳል፡፡
ሕጉ የወንጀል ብቻ ሳይሆን የፍትሐ ብሔርን ድርሻም ጨምሮ ይሰራ ነበር፡፡ ዛሬም ጥቃት የደረሰባት ሴት የሞራል ካሣ ልትጠይቅ ትችላለች። ግን ከሚጠብቃት ውጣ ውረድ ሌላ ገንዘቡም ደካማ ነው፡፡ ፍትሐ ነገሥቱ የደፋሪዎችን አፍንጫ ከመፎነን የሚያስጥል ሌላ ድንጋጌም አለው። እንዲህ ይላል “በፈቃድዋ ወይም ያለፈቃድዋ ወላጆቿ ሳያውቁ ከልጃገረድ ጋር የተገናኘ ሊያገባት የሚወድ ቢሆን ለወላጆቿ ፈቃዱን ይፈጽሙለት ዘንድ ምርጫ ይገባቸዋል፡፡ ከወላጆቿ አንዱ እንቢ ቢል የገሰሳት ሰው ቢቻለው ባለፀጋም ቢሆን ምዝን ወርቅ ይስጣት፤ በሁሉም ችግረኛ ቢሆን ገርፈው ራሱን ላጭተው ይስደዱት” (ገፅ 419) ይላል፡፡
ይህን ድርጊት በፈፀመው ሰው ላይ ህጉ ጥብቅ እርምጃ እንዳይወሰድበት የሚያደርገው ዓላማውን በመደገፍ ነው፡፡ ጋብቻ ትልቅ ማህበራዊ ተቋም ነው፡፡ እንደተቋምነቱም ህጉ ጥበቃ ያደርግለታል። ለዚህም ነው ክብረ ንጽህናዋን የገሰሰ ወንድ መጀመሪያ ድርጊቱን ለምን ዓላማ እንደፈፀመው መታወቅ የሚገባው፡፡ ጉልበት ስላለው ብቻ ከደፈረ ቅጣቱ ያው የአፍንጫ መፎነን ነው፤ ለጋብቻ ዓላማ ግን ቅጣቱ ቀላል እንዲሆን የታሰበበት ይመስላል፡፡ በተለይ ከወላጆቿ አንዱ ካልተስማማ እና አጥፊው ድሃ ከሆነ ቅጣቱም ቀለል እንዲል ተደርጓል፡፡ ሃብታም ከሆነ ግን ጋብቻውም የማይፈቀድለት ከሆነ ምዝን ወርቅ የመክፈል ግዴታ ተጥሎበታል፡፡
ምዝን ወርቅ አሁን በምናውቀው ሚዛንና መመዘኛ የሚታሰብ አልነበረም፤ የክብደቱ መለኪያ ድቡልቡል ድንጋይ ነበር፡፡ እናም ከድንጋዩ ክብደት ጋር የሚመዝን ወርቅ መክፈል ይጠበቅበታል ማለት ነው፡፡ ይህን ማድረግ ካልቻለ የገንዘቡን (የሃብቱን) ዕኩሌታ እንዲሰጣት ይገደዳል፡፡
ከዚህ አንፃር ሲታሰብም ፍትሐ ነገሥት የሴቶችን መብት በማስከበር ረገድ ትልቅ ትኩረት ይሰጥ እንደነበር እንገነዘባለን፡፡ ዛሬ በትዳር አጋራቸው ወይም በፍቅረኛቸው ገላ ላይ አሲድ እየረጩ፣ በጩቤ ዓይናቸውን እየጐለጐሉ፤ ወይም በአደባባይ በጥይት እየደበደቡ፣ ወይም በልጆቿ ፊት የእናታቸውን አንገት በቢላዋ እንደ ዶሮ የሚቀነጥሱ፣ ወዘተ ጨካኞችና ነውረኞች እንደ አሸን ሲፈሉ “ምናለ በፍትሐ ነገሥት ዘመን ተፈጥረን ቢሆን ኖሮ” ያሰኛል፡፡
ሌላውና ጠንካራው የፍትሐ ነገሥት ድንጋጌ በግብረሰዶማውያን ላይ ይጥል የነበረው ቅጣት ነው፡፡ “ግብረሰዶም የሚሰሩ ሰዎች ለአድራጊውና ለተደራጊው ቅጣታቸው ሰይፍ ነው፡፡ ተደራጊው 12 ዓመት ያልሞላው ቢሆን የዘመኑ ማነስ ከቅጣት ያድነዋል” (ገፅ 421) ይላል፡፡ ዛሬ ላይ ይህ ሕግ በአገራችን እየተሰራበት ቢሆን ኖሮ የስንቱ ብላሽ አንገት ለሰይፍ ይዳረግ እንደነበር ሳስበው “ምን አለ መንግሥት ይህን የፍርድ መጽሐፍ ቢያነብበውና የአገሪቱ የወንጀል ሕግ አካል ቢያደርገው” የሚል ብርቱ ምኞት ያድርብኛል፡፡ ይህ ደግሞ ያለምክንያት አይደለም፤ ጨካኝ ባህርይ ኖሮኝም አይደለም፡፡ ምንም በማያውቁ ህጻናት ላይ የሚፈፀመውን ዘግናኝ ድርጊት ስለምሰማ ነው፡፡ በቅርቡ እንኳ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት በመታየት ላይ ያለ የስድስት መምህራን ድርጊት ይህን አይነት ቅጣት እንድመኝ ገፋፍቶኛል። ልጅን ያህል ታላቅ አደራ ተሰጥቷቸው በትክክልና በስርዓት አስተምረው መላክ ሲገባቸው አንድን ህፃን ለስድስት መድፈር በእርግጥስ በሰይፍ ሊያስቀጣ የሚችል እጅግ ከባድ ወንጀል አይደለም?
ለእንዲህ ዓይነቶቹ ነውረኛ ግለሰቦች የልብ ልብ የሰጣቸው የወንጀል ህጋችን መላላት ይመስለኛል፤ ጉዳዩን በተመለከተ የወጣው ድንጋጌ አንቀጽ 631 (1) እንዲህ ይላል፡፡
“ማንም ሰው ከእርሱ ጋር አንድ አይነት ጾታ ባለውና ለአካለ መጠን ባልደረሰ ልጅ ላይ የግብረ ሰዶም ጥቃት የፈፀመ እንደሆነ ሀ) የተበዳዩ ዕድሜ አስራ ሶስት ዓመት ሆኖ አስራ ስምንት ዓመት ያልሞላው ሲሆን ከሶስት ዓመት እስከ አስራ አምስት ዓመት በሚደርስ ጽኑዕ እሥራት፤ ለ) የተበዳዩ ዕድሜ ከ13 ዓመት በታች ሲሆን ከ15-25 ዓመት በሚደርስ ጽኑዕ እሥራት ይቀጣል፡፡”
ሴት ለሴት የሚደረግ ግብረሰዶማዊነትንም ህጉ እንደወንዶች ባይሆንም በወንጀል ፈጻሚዎች ላይ የተለያየ የቅጣት ዕርከን ደንግጓል፡፡ ግን እንደ ፍትሐ ነገሥቱ አስተማሪ አይደለም፡፡ በ1977 ዓ.ም ወሎ ክፍለ ሃገር በደረሰው ከባድ ድርቅ ምክንያት ወላጆቻቸውን በረሃብ የተነጠቁ ህፃናትን ለመርዳት “ጃሪ የህፃናት መንደር” በውጭ አገር ሰዎች ቢመሰረትም ምንም በማያውቁ ምስኪን ህጻናት ላይ ከፍተኛ የሆነ ግብረሰዶማዊ ጥቃት ሲደርስባቸው ነበር፡፡ ከጊዜ በኋላ ጥቃቱን ራሳቸው ተጐጂዎቹ ቢያጋልጡም ከፊሉ ወንጀለኞች አገር ጥለው ሲወጡ የተያዘው አንድ ግለሰብ ግን በስምንት ዓመት እስር ብቻ እንደተቀጣ አስታውሳለሁ፡፡
በርካታ ህፃናት (ያውም ወላጆቻቸውን በጠኔ የተነጠቁ) ላይ አስነዋሪ ድርጊት የፈፀመ ወንጀለኛ ሰይፍ አይገባውም ነበር? እርግጥ ነው ዳኞች ህጉ ከሚደነግገው በላይ አልፈው ሊቀጡ ስልጣን የላቸውም፡፡ የሴቶችንና የህፃናትን ጥቃት ለመከላከል ግን ዛሬም ፍትሐ ነገሥት ያሻን ይመስለኛል፤ እንወያይ!

Read 3027 times