Monday, 16 September 2013 07:56

‘ልብ የመግዣ’ ዓመት…

Written by  ኤፍሬም እንዳለ
Rate this item
(3 votes)

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
እንኳን ከዘመን ዘመን በሰላም፣ በጤናና በደስታ አሸጋገራችሁማ!
(መባል ሰላለበት ነው እንጂ…አለ አይደል… “ሰላም ሲኖረን፣ ጤና ስንሆን፣ ደስ ሲለን የት ያየኸውን ነው!” ምናምን የሚል ጥያቄ ቢመጣ አስቸጋሪ ይሆናል፡፡)
እናላችሁ…ይኸው ‘ተሸጋርናል’…ቢያንስ፣ ቢያንስ ግድግዳችን ላይ ያለውን ‘አሮጌ’ ቀን መቁጠሪያ በአዲስ እንለውጣለን፡፡ ማንም መጥቶ (ወይም በሰፈር ‘ፌርማቶሪ’) “ቤቱ ግድግዳ ላይ የለጠፈው በምስጢር ምን የሚሠራው ነገር ቢኖር ነው ይሉኝ ይሆን?” ብለን ሀሳብ ሳይገባን የምንለጥፈው ቢኖር የቀን መቁጠሪያ ካላንደር ነው፡፡
ግን’ኮ… እንግዲህ ጨዋታም አይደል…እንደ ዘንድሮ ነገረ ሥራችን ከሆነ ካላንደሩ ላይ የተጻፈው የድርጅት ወይም ተቋም ስም ‘ሊያስመርዝ’ ይችላል፡፡ ልክ ነዋ…“ከመቼ ወዲህ ነው እሱ ሀይማኖተኛ የሆነው፣ ለሽፋን ንው እንጂ!” ምናምን ሊባል ይችል ሁሉ ይሆናል፡፡
የማንጫወትበትን ቡድን ማልያ የማልበስ እርግማችንን አዲሱ ዓመት ይዞት ጥርግ ይበልማ! ላለፉት ጥቂት ዓመታት…አለ አይደል… በአገር ልጅነት፣ በእምነት፣ በፖለቲካ አስተሳሰብ፣ በምንሠራባቸው ቦታዎች፣ በምናዘወትርባቸው ‘ፉት’ ቤቶች፣ አብረን በምንውላቸው ጓደኞች… ብቻ የምንፈረጅባቸው ነገሮች እየተባዙ ነው የመጡት፡፡
እናማ… መጪው ዓመት በሆነ ባልሆነው ‘የተመረጠልንን ማልያ’ እንድንለብስ የምንደረግበትን ‘እርግማን’ ያንሳልንማ!
ስሙኝማ…ያው እንደተለመደው በዓላችን ‘ምግብ ተኮር’ ነው፡፡ ቱርካውያን በአዲስ ዓመት በማህበራዊ አገልግሎቶች መሳተፍና የእርዳታ መሰብሰቢያ ዝግጀቶችን ማዘጋጀት ደስታ እንደሚያመጣላቸው ያስባሉ ይባላል፡፡ እኛ ዘንድ…አለ አይደል… በኤን.ጂ.ኦ. ምናምን ሳይሆን በዜግነታችን ብቻ በማህበራዊ አገልግሎቶች ላይ የምንሳተፍበት ጊዜ አይናፍቃችሁም! ለነገሩ… እኛ ዘንድ አንዳንድ ጊዜ በተናጥል ወይም ሰብሰብ ብላችሁ በጎ ነገር ስታደርጉ…አለ አይደል… በዚህ ወይ በዚያ ወገን ‘ቦተሊካው’ ይጠልፈውና በህልማችሁ ያላለማችሁት ‘ስክሪፕት’ ይጻፍለታል፡፡
ስሙኝማ…እንግዲህ የበዓል ማግስት ጨዋታም አይደል…ስለ ምግብ ካወራን ይቺን ስሙኝማ…ጓደኛሞቹ ጥሬ ሥጋ ሊበሉ የሆነ ቤት ይገባሉ። እናላችሁ…‘ሻሽ’ የመሰለ ሥጋ አስቆርጠው ይቀመጣሉ፡፡ ታዲያላችሁ… ከእነሱ ፊት ለፊት የነበሩ ሰዎች ፍጥጥ ብለው ያዩዋቸዋል፡፡ እናማ…ጓደኛሞቹ “እኛ ቁርጥ ልንበላ ብንመጣ ሰዎቹ ቁርጥ ሊያደርጉን ነው እንዴ!” ምናምን ተባባሉና ከመሀላቸው አንዱ ምን ቢያደርግ ጥሩ ነው… ወፈር ያለ ሥጋ ይቆርጥና መሬት ላይ ይጥለዋል፡፡ ጓደኞቹም ምን እያደረገ እንደሆነ ሲጠይቁት ምን ቢል ጥሩ ነው…“ግራውንድ ላደርግ ነው!” አሪፍ አይደል፡፡ ጦስ ጥብምቡሳሳችንን ይዞ ምድር ይግባ አይነት መከላከያ ነው፡፡ (እኔ የምለው…ከዚች በፊት ያነሳናትን ጥያቄ እንደገና እናንሳትማ…አፍጥጠው የሚያዩ ሰዎች በጣም፣ እጅግ በጣም አልበዙባችሁም! ትንሽ ግራ የሚያጋባ ነገር ነው፡፡ ሰው አፍጥጦ ማየት ‘ጎጂ ኋላ ቀር ባህል’ ስለሆነ በመጪው ዓመት የአፍጣጮች ዒላማ ከመሆን ይሰውረንማ!
ስሙኝማ…የተለያዩ አገሮችን የአዲስ ዓመት መልካም ምኞቶች የፈረደበት ‘በይነ መረብ’ ላይ ሳይላችሁ…ያገኘኋቸውን ስሙኝማ፡፡ ይሄ ለወላጆች የሚጻፍ ነው…“ወደ ህልሞቼ የምበርባቸውን ክንፎች ሰጥታችሁኛል፣ የመጣሁበትን እንዳልረሳም ስረ መሰረቴን አሳይታችሁኛል፡፡ ምንም ያህል ወደላይ ብመጥቅም ስረ መሰረቴን እንዳልረሳና እንዳልለቅ አስተምራችሁኛል፡፡ ሁልጊዜ በአጠገቤ በመሆናችሁና ስለምታግዙኝም በዚህ በአዲሱ ዓመት ምስጋናዬ ይድረሳችሁ፡፡”
አሪፍ አይደል!…የዚሀ አገር አንዱ ትልቁ ችግር ምን መሰላችሁ…ስረ መሰረታችንን በራስ አነሳሽነት የምንረሳ መአት መሆናችን፡፡ የምር ግን…ከትንሽ ቦታ ተነስቶ ትልቅ ቦታ የመድረስን ያህል የሚያኮራ ነገር አለ!
እናላችሁ…ሲወለድ በ‘ወርቅ ማንኪያ’ ወተት ይጠጣ የነበረውማ…አለ አይደል… ‘ጣጣው ያለቀለት፣ ካርታው የወጣለት፣ ሊዙ ሙሉ የተከፈለለት’ ህይወት ውስጥ ነው የገባው፡፡ አንዳንድ ሰው ግን በአቅም ማነስ በሦስት ቀን አንዴ እንኳን በማይበላበት ቤተሰብ ተወልዶ በኋላ ላይ ስኬት ላይ ሲወጣ…“እኔ ስወለድ እኮ ድፍን ሰፈር ሠርግና ምላሽ ነበር…” አይነት ነገር ቀሺም ነው፡ መጪውን ዓመት ስረ መሠረታችንን ያልረሳን ይዘን እንድንቆይ፣ የረሳነውም መልስን የምንይዝበት ዓመት ያድርግልንማ! ‘ራስን ከማጣት’ የበለጠ ውድቀት የለም፡፡
ሩስያ ውስጥ የሚኖር አንድ አይሁዳዊ ወደ አሜሪካ ለመሄድ የቪዛ ማመልከቻ ያቀርባል። ወደ አሜሪካ ለመሄድ የፈለገበትን ምክንያትም ይጠይቃል፡፡
አሜሪካ ያለው ወንድሙ እንዳመመውና ሊያስታምመው እንደሆነ ይናገራል፡፡ የፓስፖርት ሰዎቹ እንግዲያው አንት እዛ ከምትሄድ ወንድምህ ለን እዚሀ አየመጣመ አሉት፡፡
አይሁዳዊው ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው…“አሞታል አልኩ እንጂ አብዷል አላልኩም!” መጪው ዓመት ከውጪ ለመምጣትም ውስጥ ሆኖ ለመክረምም “አሞታል አልኩ እንጂ አብዷል አላልኩም!” የማንልባት ዓመት ትሁንልንማ!
ስሙኝማ…ስለ መልካም ምኞት መግለጫ ስናወራ አልነበር…እናማ ለአዛውንቶች ደግሞ እንዲህ አይነት የመልካም ምኞት መግለጫ አለላችሁ…“እርሶ በብዙ ዘመናት ያጠራቀሙት እውቀትና ጥበብ እኔን ወደ ግቦቼ ለመድረስ በማደርጋቸው ጉዞዎች መንገድ መሪዎቼ ናቸው፡፡ እርሶ በህይወት ባገኟቸው ትምህርቶች ክፉ ጊዜን ለመሻገር ይርዱኝ፡፡ መልካም አዲስ ዓመት፡፡”
ስሙኝማ…እዚህ አገር አንድም የጎደለን ነገር በኑሮ ልምድ የሚመጣ ጥበብና ተሞክሮ ነው፡፡ አንድ ሰሞን ሁሉንም ዕድሜ ጠገብ ነገር የማውገዝና “ኋላ ቀር!” የማለት ነገር እንደ ወረርሽኝ በሚዲያው ጭምር ተባብሶ ነበር፡፡ አሁን፣ አሁን በትንሽ፣ ትንሽም የትናንቱ ነገር ሁሉም መጥፎ እንዳይደለ፣ የዛሬውም ነገር ሁሉም መጥፎ እንዳልሆነ…ሁሉም ዘመናት የየራሳቸው መጥፎና ጥሩ ነገሮች እንዳሏቸው ባይበዛም እየተቀበልን መሰለኝ፡፡ አዲሱ ዓመት ከወዲያኛው ዘመን ማድነቅና መውረስ ያለብንን እንድናደንቅና እንድንወርስ የመንፈስ ጥንካሬውንና በራስ መተማመኑን የምናገኝበት ይሁንልንማ!
የምር ግን…ለምሳሌ ብዙ የሬደዮ ፕሮግራሞች ላይ የምናየው ችግር…አለ አይደል… ለረጅም ዓመታት ከመኖርና፣ በብዙ ህይወት ተሞክሮ ከማለፍ የሚገኙ እስተምህሮቶች መሳሳታቸው ነው፡፡ በአዲስ ዓመት ከህይወት ልምዳቸው ትምህርት የምናገኝባቸውን የዕድሜ ባለጸጎች እንፈልጋለን፡፡ እናማ መጪውን ዓመት…“እናንተ በህይወት ባገኛችኋቸው ትምህርቶች ክፉ ጊዜን ለመሻገር እርዱን፣” የምንልበት ዓመት ያድርግልንማ! (በሬድዮ የምትሠሩ አቅራቢዎች…ፕሮግራሞቻችሁ ‘ሚዛን እንዲደፉ’ና ይበልጥ ተደማጭ እንዲሆኑ ከ‘ቁም ነገር ንባቡ’ ጨመርመር የምታደርጉበት ዓመት ያድርግላችሁማ!)
እናላችሁ… ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…በየትኛውም ስርአት ‘ቦተሊከኞች’ ያለፉ ትውልዶችን እንዳለ ጥምብርኩሳቸውን የሚያወጧቸው …..አንድም ከታሪክ መጽሐፍት ይልቅ የውስኪ ስም ማንበብ ስለሚቀላቸው (ቂ…ቂ…ቂ…) ወይም የራሳቸውን ቅሽምና ለመሸፈን መስዋእትነት የሚያቀርቡት ‘የአብረሀም በግ’ ስለሚፈልጉ ይመስለኛል፡፡ በቃ መሰለኝ…ደግሞም አበቃሁ፡፡ )
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…በቀድሞዋ ሩስያ ነው አሉ…የመሥሪያ ቤቱ ካድሬ ሠራተኞቹን ሰብስቦ ስለወደፊቷ ሩስያ ብሩህ ጊዜ እየሰበካቸው ነው፡፡
አያችሁ ጓዶች፣ ይህ የአምስት ዓመት ፕላን ሲጠናቀቅ፣ እያንዳንዱ ቤተሰብ አፓርትመንት ይኖረዋል፣ የሚቀጥለው የአምስት ዓመት ፕላን ሲጠናቀቅ ደግሞ እያንዳንዱ ሠራተኛ የየራሱ መኪና ይኖረዋል! ሦስተኛው የአምስት ዓመት ፕላን ሲጠናቀቅ ደግሞ እያንዳንዱ ቤተሰብ የየራሱ አውሮፕላን ይኖረዋል!” ይላቸዋል፡፡
ከተሰብሳቢዎቹ አንዱ “አውሮፕላን ምን ያደርግልናል?” ሲል ይጠይቃል፡፡ ካድሬው ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው…“ጓዶች፣ አይታያችሁም እንዴ! በከተማችሁ የድንች እጥረት አለ፡፡ አታስቡ፣ ችግር የለም፡፡ አውሮፕላኖቻችሁን ታስነሱና ሞስኮ ሄዳችሁ ድንች ገዝታችሁ ትመጣላችሁ!” አንዳንዴ የዚቹ የእኛ አገር እንደ ወረደ የሚበተን ‘ብሮባጋንዳ’ በአውሮፕላን ሞስኮ ሄዶ ድንች እንደመግዛት አይመስላችሁም!
ብቻ መጪውን ዓመት ለሁላችንም ‘ልብ የመግዣ ዓመት ያድርልግንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Read 3725 times