Monday, 16 September 2013 07:45

ሰማያዊ ፓርቲ እሁድ ያስመረቀውን ቲያትር በቪሲዲ ለህዝብ ሊያደርስ ነው

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(1 Vote)

“ታዋቂ አርቲስቶች አንሳተፍም ማለታቸው አሳዛኝ ነው” ኢ/ር ይልቃል ጌትነት
የመንግስት ሲኒማ ቤቶች ትያትሩን ለማሳየት ፈቃደኛ አልሆኑም
ሰማያዊ ፓርቲ ባለፈው እሁድ ያስመረቀውን “የነፃነት ፈለግ” የተሰኘ ቲያትር በቪሲዲ ለህዝብ ሊያቀርብ እንደሆነ የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ገለፁ፡፡
እሁድ እለት በጣሊያን የባህል ተቋም የተመረቀው ትያትሩ፤ በፕሮፌሽናል ካሜራ መቀረፁንና በቅርቡ ኤዲቲንጉ አልቆ በቪሲዲ ለህዝብ እንደሚደርስ የጠቆሙት ኢ/ር ይልቃል፤ ትያትሩን በመንግስት ሲኒማ ቤት ለማሳየት ሲኒማ ቤቶች ፈቃደኛ ባለመሆናቸው በቪሲዲ ለማውጣት ተገደናል ብለዋል፡፡
የ70 ደቂቃ ርዝመት ያለው ትያትሩ በአገሪቱ ወቅታዊ የፖለቲካና ማህበራዊ ችግሮች ላይ የሚያተኩር መሆኑንና የፓርቲው አባል በሆነው ወጣት ዳዊት ፀጋዬ እንደተፃፈ የተናገሩት ኢ/ር ይልቃል፤ ታዋቂ አርቲስቶች በትያትሩ ላይ ለመሳተፍ ለሶስት ወራት ሲለማመዱ መቆየታቸውን ጠቁመው፤ በኋላ ግን መንግስትን በመፍራት ጥለው እንደወጡና በዚህም እርሳቸውና ሌሎች የፓርቲው አባላት እንዳዘኑ ገልፀዋል፡፡ “ታዋቂ አርቲስቶች ሙያቸውን በመጠቀምና ለእውነት በመቆም ህዝቡን ማገልገል አለባቸው” ያሉት ኢ/ር ይልቃል፤ ታዋቂ የትያትር አዘጋጅና አስተማሪ የሆነው ግለሰብ “ሀላፊነት አልወስድም” ብሎ ዝግጅቱን አቋርጦ ከአገር መውጣቱንም ገልፀዋል። “አዘጋጁ ሀላፊነት አልወስድም” ያለው በተለይ ግንቦት ላይ ሰላማዊ ሰልፍ በማድረጋችንና ጉዳዩ መነጋገሪያ በመሆኑ ነው” ብለዋል፡፡
“ተዋንያኑም አዘጋጁን አምነን ነው ስራውን የጀመርነው፤ እርሱ ሀላፊነቱን ካልወሰደ እኛም አንፈልግም” በማለት ከሶስት ወር በኋላ ጥለው መበተናቸውንና እንደ አዲስ ሌሎች ወጣት ተዋንያንና አዘጋጅ ተፈልገው ልምምዱ መጀመሩን የገለፁት የፓርቲው ሊቀመንበር፤ በዚህ ምክንያት ቴያትሩን ለእይታ ለማብቃት ከስድስት ወር በላይ መፍጀቱን ገልፀዋል። ትያትሩ ትርፍን ማዕከል ባላደረገ መልኩ የተዋንያን እና የደራሲውን ወጪ ለመሸፈን በመጠነኛ ዋጋ ለህዝብ ይደርሳል ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ፓርቲዎች ለአጭር ጊዜ ገቢ ማስገኛ ስራዎችን የመስራትና ለገበያ የማቅረብ መብት እንዳላቸው አዋጁ እንደሚደነግግ ገልፀው፤ ቪሲዲውን በቅርቡ ለማከፋፈል ዝግጅት እየተጠናቀቀ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡ ትያትሩ በተመረቀ እለት ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያምን ጨምሮ በርካታ ሰዎች ተገኝተው አድናቆታቸውን መግለፃቸውን የተናገሩት ኢ/ር ይልቃል፤ ሥራው በተቃዋሚ ፓርቲ ደረጃ የመጀመሪያና አስተማሪ መሆኑን ፕሮፌሰሩ መናገራቸውን አውስተዋል፡፡
ፓርቲው ትያትሩን በመንግስት ሲኒማ ቤት ለማሳየት ፈልጎ ይሁንታ በማጣቱ በጣሊያን የባህል ተቋም ካስመረቀ በኋላ ተቋሙ ለትያትሩ ደራሲ “አገባባችሁ ትክክል አይደለም፣አታላችሁናል፣ አዳራሹም ለፖለቲካ ስራ ውሏል” የሚል ይዘት ያለው ደብዳቤ መፃፉን የተናገሩት ኢ/ር ይልቃል፤ በዚህም ማዘናቸውን ገልፀዋል፡፡

Read 18115 times