Saturday, 07 September 2013 10:33

እኛና አውሮፓውያን በዘመን አቆጣጠር ለምን ተለያየን?

Written by  ኦርዮን ወ/ዳዊት
Rate this item
(15 votes)

ዘመን መቁጠር የተጀመረው “በዚህ” ወይም “በዚያ ጊዜ ነው” ማለት ይከብዳል፡፡ ምክንያቱም የተለያዩ አገሮች እንደየእምነታቸውና የሥልጣኔ ደረጃቸው ልዩ ልዩ የዘመን ቀመር ሊኖራቸው ይችላል፤ አላቸውም፡፡ ብዙውን ጊዜ ግን የዘመን አቆጣጠር ከሃይማኖቶች አነሳስና ዕድገት ጋር ይያያዛል፡፡
ባቢሎናውያን፣ ግሪካውያን፣ ህንዳውያን፣ ግብፃውያን፣ ቻይናውያን፣ ሮማውያን፣ ኢትዮጵያውያን፣ የአረብ አገሮች ወዘተ የተለያዩ የዘመን ቀመሮችን የሚከተሉ ሲሆን የአብዛኞቹ ቀመሮች መነሻ ሃይማኖት ነው፡፡ አገራችንን ጨምሮ በርካታ የአውሮፓ አገሮች የዘመን አቆጣጠራቸው መነሻ አዳም ነው፡፡ የሥነ ፍጥረት ተመራማሪዎች “የሰው ልጅ በምድር ላይ ኖረ” የሚሉት በሚሊዮኖች ከሚቆጠሩ ዓመታት በፊት ጀምሮ ቢሆንም የክርስትና እምነት ተከታዮች ግን ዘመንን ከአዳም መፈጠር ጋር ያያይዙታል፡፡
ይህ ማለት ሰው በዚች ዓለም ላይ መኖር ከጀመረ በእኛ አቆጣጠር 7505 ዓመት ሞላው ማለት ነው፡፡ በአውሮፓውያኑ ቀመር ደግሞ 7513 ዓመት ይሆናል፡፡ የሁለቱም መነሻ ፍጥረተ አዳም ነው፡፡ ግን በመሀላቸው የሰባት ዓመት ከስምንት ወራት ልዩነት አለ፡፡ ለምን? የዛሬ ጽሑፌ ዓላማም ይህን ጥያቄ ማጉላትና ለልዩነቱ ሰበብ የሆነውን ሰውና ጊዜውን ማሳወቅ ነው፡፡
አውሮፓውያንም ሆኑ ኢትዮጵያውያን ለዘመን ቆጠራቸው መነሻ የሚያደርጉት አዳምን ነው ብያለሁ፡፡ ለዚህ ማስረጃ ይሆናቸው ዘንድ መጽሐፍ ቅዱስን እንደሚከተለው ይጠቅሳሉ
ከአዳም እስከ ኖህ 2256 ዓመት፤
ከኖህ እስከ ግንብ ሥራ (ባቢሎናውያን ዘመን) 531 ዓመት፣
ከግንብ ሥራ አብርሃም እስከ ተወለደበት 551 ዓመት
ከአብርሃም እስከ ሙሴ ልደት 425 ዓመት፤
ከሙሴ እስከ ዳዊት ልደት 684 ዓመት፤
ከዳዊት እስከ ናቡከደነጾር ምርኮ 469 ዓመት፣
ከናቡከደነጾር እስከ ታላቁ እስክንድር 265 ዓመት
ከታላቁ እስክንድር እስከ ኢየሱስ ልደት 319 ዓመት፤
ድምር 5500 ዓመት በማምጣት ከኢየሱስ ልደት በኋላ እና በፊት እያሉ ዘመኖቻቸውን ያሰላሉ፡፡
በመስኩ የተደረጉ ጥናቶች እንደሚያስረዱት፤ የመጀመሪያውን የዘመን መቁጠሪያ ቀመር ያወጡት “ሱሜሪያውያን” በመባል የሚታወቁት ጥንታውያኑ የባቢሎን ዜጐች ናቸው፡፡ የሱሜራዊውያኑ የቀን አቆጣጠር ዋና መነሻ የጨረቃ እንቅስቃሴ (ዑደት) ነው፡፡ የጨረቃን ዑደት በማጤን አሥራ ሁለት ወራትን ሰይመው ነበር፡፡ በአራት ዓመት አንድ ጊዜ የሚጨመር 13ኛ ወርም ነበራቸው። ይህን ያደረጉበት ምክንያት ዓመቶቹን ለመለየት እንዲረዳቸው ነበር፡፡
ግሪኮች፣ ግብጾችና የሴም ዝርያ ያላቸው ሌሎች ህዝቦችም በሱሜሪያውያን የቀን መቁጠሪያ ይጠቀሙ ነበር፡፡ ሆኖም ቀስ እያሉ የራሳቸውን ምርምር ማድረግ ቀጥለዋል፡፡ ከጊዜ በኋላ ግብጾች ምንም እንኳ የቅመራ መሠረታቸውን ጨረቃ ላይ ቢጥሉም የራሳቸውን የቀን መቁጠሪያ ለማዘጋጀት ቻሉ፡፡ ቅመራቸው በዓመት ውስጥ የሚውሉ ባህላዊ የእምነት በዓላትንና ወቅቶችን ግምት ውስጥ ያስገባ ስለነበር ከሱሜራውያኑ ቀመር የተሻለ ጥቅም አስገኝቷል፡፡
የቀን መቁጠሪያው ከባቢሎናውያኑ የሱሜራውያን የተሻለ ነበር የሚባለው ከዓባይ ወንዝ መሙላትና መጉደል ጋር የተያያዘ ስለነበር፣ የሀገሪቱን መንግሥት ስሜት መግዛት በመቻሉ ነው፡፡
በዚህ መሠረት የግብጽ መንግሥት ከሥራውና ከመንግሥታዊ አደረጃጀቱ ጋር የሚስማማ የቀን መቁጠሪያ እንዲዘጋጅ አደረገ፡፡ አይሁዳውያንና ሙስሊሞች ደግሞ የጨረቃን ዑደት የተከተለ የቀን መቁጠሪያ ሥርዓት አዘጋጁ፡፡ ሮማውያንም ልክ እንደ አይሁዶችና ሙስሊሞች የዘመን ቆጠራ ስርዓታቸውን ያዘጋጁት በጨረቃ እንቅስቃሴ ላይ ተመሥርተው ሆኖ፣ ቀመራቸው በዓመት ውስጥ 355 ቀናትን እንዲይዝ ተደርጐ ተቀረፀ፡፡ ሮማውያን የዘመን አቆጣጠራቸውን የወሰኑት ልክ እንደሱሜራውያኑ በአራት ዓመት አንድ ጊዜ 13ኛ ወር እንዲያካትት በማድረግ ነው፡፡
ጥቅምት፣ መጋቢት፣ ግንቦትና ሐምሌ እያንዳንዳቸው 31 ቀናት እንዲኖራቸው ሆኖ የተቀረፀው የሮማውያን ቀመር፤ ለየካቲትም 28 ቀናት መድቦ ነበር፡፡ ለቀሩት ወሮች ግን ለእያንዳንዳቸው 29 ቀናት ተወስኖላቸው እንደነበር ሻለቃ አባይነህ አበራ “ካዘና” በሚለው መጽሐፋቸው ያስረዳሉ፡፡
ይሁን እንጂ በወቅቱ የሮማ ሊቃውንት የቀመሩት ያ ቀመር፣ መሬት በፀሐይ ዙሪያ የምታደርገውን ኡደት (መሽከርከር) ግምት ውስጥ ያስገባ ስላልነበር ውሎ አድሮ ችግር ማስከተሉ አልቀረም፡፡
ችግሩም በተቀመረው የዘመን ስሌት መሠረት ከመግባትና ከመውጣት ይልቅ ወቅቶች በተቃራኒው የሚከሰቱበትና የሚጠፉበት አጋጣሚ እየበዛ መሄዱ ነበር፡፡
ለምሳሌ በቀን መቁጠሪያው ላይ “በጋ ነው” ተብሎ በተመለከተው ወር ክረምት ይገባል፤ ወይም በፀደይ ወራት በልግ ይከሰታል፡፡ ችግሩን በአግባቡ የተገነዘበው የወቅቱ የሮማ ንጉሠ ነገሥት ቄሳር ዘላቂ መፍትሔ ማፈላለጉን ተያያዘው፡፡ እናም በ46 ዓመተ ዓለም የተሻለ የቀን መቁጠሪያ አዘጋጀና ችግሩን በመጠኑም ቢሆን ማቃለል ቻለ፡፡ የዓመቱ ቀናትም 366 ከስድስት ሰዓታት እንዲሆኑ ደነገገ፡፡
በዚህ የተነሳ ቀድሞ “ኩዊንቲሊስ” ይባል የነበረው ወር ለጁሊየስ ቄሳር መታሰቢያነት ሲባል “ጁላይ” እንዲባል ተወሰነ፤ ቀመሩም “የጁሊያን ቀመር” እየተባለ መጠራት ጀምሮ ነበር፡፡ በጁሊየስ ቄሳር የተቀመረው የዘመን መቁጠሪያም የበዓላትንና የወቅቶችን መፈራረቅ በማስከተሉ የመስኩን ሊቃውንት ማሳሰቡ አልቀረም ነበር፡፡ የዚህ ችግር ዋናው ምክንያት በየአራት ዓመት አንድ ጊዜ የካቲት ላይ የሚጨመረው አንድ ቀን ለበዓላት፣ ዕለታትና ለወቅቶች መለዋወጥ (መግቢያና መውጫ ጊዜያቸው መለዋወጥ) ጉልህ አስተዋጽኦ ማድረጉ ነበር፡፡
ከብዙ ጊዜ በኋላ ችግሩን ያጤኑት “አባ ጐርጐርዮስ 13ኛ” የተባሉ ሊቀ ጳጳስ፤ ሌላ ቀመር አወጡና በነበረው የጊዜ መቁጠሪያ ላይ 10 ቀናት (ሻለቃ ዓባይነህ አበራ 11 ቀናት ተጨመሩ ይላሉ) በመደመር እ.ኤ.አ ጥቅምት 5 ቀን 1575 ዓ.ም “ነገ ጥቅምት 15 ቀን ነው” ብለው አወጁ፡፡ የአባ ጐርጐርዮስን ሃሳብ ብዙ የካቶሊክ እምነት ተከታይ አገሮች ቢቀበሉትም የኦርቶዶክስና የፕሮቴስታንት እምነትን የሚከተሉ አገሮች ግን በሃሳቡ ሊስማሙ አልፈለጉም ነበር፡፡
አባ ጐርጐርዮስ ይህን የ10 ቀን ልዩነት ያገኙት ከ375 ዓመተ ምህረት ጀምረው በማስላት መሆኑን ጥናታቸውን ይፋ ባደረጉበት ወቅት ተናግረዋል፡፡ በጥናታቸው መሠረት፤ አንድ ዓመት 365 ቀናት፣ ከስድስት ሰዓት የነበረው የዩሊየስ ቄሳር ቀመር፤ በደቂቃ፣ በሰዓትና በዕለት ሊከፋፈል ይገባል፡፡ እናም አንድ ዓመት ማለት 365 ቀናት፣ ከአምስት ሰዓት፣ ከአርባ ስምንት ደቂቃዎችና ከአርባ ስድስት ሰኮንዶች ይሆናል፡፡ በመሆኑም “11 ደቂቃዎችና 14 ሰኮንዶች ሳይኖሩ እየተኖረባቸው አልፈዋል” በማለት አባ ጐርጐርዮስ ከሰባት እስከ አስር ቀናትን በመጨመር ነው ከላይ የተገለፀውን ቀመር ይፋ ያደረጉት፡፡
ኢትዮጵያውያኑ የሐሳብ ዘመን ሊቃውንትም ጥቃቅን የሰከንድና የደቂቃ ሽርፍራፊዎች መኖራቸውን ያምናሉ፡፡ የሁለት ሺህ በዓልን ምክንያት በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ባወጣችው ልዩ እትም ላይም፣ ይኸ አስተሳሰብ እውነት መሆኑ ተረጋግጧል፡፡
“የዓመቱ አንድ ሳልሲት ሶስት መቶ ስልሳ አምስት ነው፤ አምስቱን ድቁቅ ደቃዲቅ ብለህ ተወው፡፡ ሶስት መቶ ስልሳ ሳልሲት ስድስት ካልኢት ይሆናል፤ ስድስት ካልኢትን እስከ 10 ዓመት ቢወስዱት ስሳ ካልኢት ይሆናል፡፡
ስሳ ካልኢት አንድ ኬክሮስ ይሆናል፤ እስከ መቶ ዓመት ቢወስዱት አስር ኬክሮስ ይሆናል፡፡ እስከ ሁለት መቶ ዓመት ቢወስዱት ሃያ ኬክሮስ ይሆናል፤ እስከ ሶስት መቶ ዓመት ቢወስዱት ሰላሳ ይሆናል። እስከ አራት መቶ ዓመት ቢወስዱት አርባ፣ እስከ አምስት መቶ ዓመት ቢወስዱት ሃምሳ፣ እስከ ስድስት መቶ ዓመት ቢወስዱት ስሳ ኬክሮስ ይሆናል፤ ስሳ ኬክሮስ አንድ ዕለት ይሆናል፡፡ እነዚህ በጣም አነስተኛ የሆኑ የጊዜ ትርፍራፊዎች በስድስት መቶ ዓመት አንድ ዕለት ይሆናሉ፡፡ በዚህም ጊዜ ዐቀድ የሚባል ኮከብ ይወጣና ፀሐይን ይጋርዳል” በማለት ይቀምራሉ፤ የፀሐይ ግርዶሽ ምክንያቱንና ጊዜውንም ያብራራሉ፡፡
ከላይ ማየት እንደሚቻለው ኢትዮጵያውያኑ የሐሳብ ዘመን ሊቃውንት የጊዜ ሽርፍራፊዎችን “ድቁቅ” እና “ደቃደቅ” በማለት ጀምረው በእነዚህ ሽርፍራፊዎች ምክንያት ከስድስት መቶ ዓመት በኋላ ሊከሰት ስለሚችለው ኮከብና ስለ ፀሐይ ግርዶሽም የተለያዩ የቅመራ ዘዴዎችን በመጠቀም ይነግሩናል፡፡ እነዚህ “ጥቃቅን” የተባሉ የጊዜ ሽርፍራፊዎች የዕለታት ልዩነትን እንደሚያመጡም ያስረዳሉ፡፡
አባ ጐርጐርዮስ በቀመሩት የጊዜ መቁጠሪያ ላይ የዓመታትና የዕለታት ልዩነት የመታየቱ ምስጢርም ይኸው ይመስላል፡፡ ሆኖም አባ ጐርጐርዮስ የተነሱበት ሐሳበ ዘመን፣ ነባሩን አቆጣጠር ማፋለሱ አልቀረም፡፡ ለዚህም ነው ከጥቅምት 5 ቀን 1575 ዓ.ም ጀምሮ በእኛና በአውሮፓውያን ቀመር ላይ አሁን የሚታየው የቀን ልዩነት የመጣው፡፡
የዕለታቱ ልዩነት የአባ ጐርጐርዮስ ቀመር ከሆነ የሰባት ዓመት ከስምንት ወራት ልዩነቱን ምን አመጣው?
የእኛም ሆነ የምዕራባውያን የዘመን አቆጣጠር መነሻው የኢየሱስ ልደት ነው፡፡ የኢየሱስ ልደት መነሻቸው ከሆነ ለምን ተለያዩ? የሚለው ጥያቄ መነሳት ያለበት ነው፡፡ ኢየሱስ አንድ ነው፤ የተወለደውም “ቤተልሄም” በተባለ አንድ ቦታ ነው፡፡ በዚህ ምዕራቡም ሆነ ምስራቁና የቀረው ዓለም ሁሉ ይስማማበታል፡፡ ከዚህ እውነት በመነሳትም እስከ 532 ዓ.ም ድረስ የምዕራባውያንና የእኛ ዘመን አቆጣጠር አንድ ነበር፡፡
በ532 ዓ.ም ግን “ዲዮናስዮስ” የተባሉ ሮማዊ መነኩሴ፣ አዲስ ቀመር በማውጣት ነባሩን የዘመን አቆጣጠር ከመሠረቱ አናጉት፡፡ ይህም በእኛና በአውሮፓውያን አቆጣጠር መሃል የሰባት ዓመት ከስምንት ወር ልዩነትን አመጣ፡፡ በአባ ዲዮናስዮስ ቀመር መሠረት፤ ኢየሱስ የተወለደው በ5492 ዓመተ ዓለም ላይ ነው ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ በመጽሐፍ ቅዱስ ተመስርተው ቀመራቸውን ላወጡ እንደ ኢትዮጵያ ላሉ አገሮች የሚዋጥ አልሆነም፡፡
ምክንያቱም እግዚአብሔር ለአዳም “በ5500 ዓመት ተወልጄ…” ብሎ የገባለትን ቃል በማሰብ “የእግዚብሔር ቃል አይለወጥም፤ እግዚአብሔርም አይዋሽም፡፡ የተወለደውም በገባው ቃል መሠረት ልክ በ5500 ዓመተ ዓለም ላይ ነው” በማለት የአባ ዲዮናስዮስን ሐሳበ ዘመን ውድቅ ያደርጉታል፡፡ ይህ ዐቢይ ጉዳይም ነው የልዩነቱ መነሻ፡፡
ስለሆነም ለሰባት ዓመት ከስምንት ወራት ልዩነት የተፈጠረው በ532 ዓ.ም አባ ዲዮናስዮስ በቀመሩት ሂሳብ ምክንያት ሲሆን የዕለታቱ ልዩነት የተከሰተው ደግሞ በ1575 ዓ.ም አባ ጐርጐርዮስ ባወጡት ቀመር መሠረት ነው፡፡
የዓመት መጀመሪያችን ለምን መስከረም እንደሆነ የተለያዩ ማስረጃዎች አሉ፡፡ መምህር አፈወርቅ ተክሌ በ2005 ዓ.ም “መጽሐፈ ታሪክ ወግስ” በሚል ርዕስ ባሳተሙት መጽሐፋቸው፤ “እግዚአብሔር ለእስራኤል ከግብጽ የወጣችሁበት ወር የዓመት መጀመሪያ ይሁናችሁ (ዘፀዓት 12፡1) እንዳላቸው ሁሉ፣ የካም ልጆችም ወደ ኢትዮጵያ የገቡበትን ይህንን ወር የዓመት መጀመሪያ ይሁነን ብለው ርዕሰ አውደ ዓመት አድርገው ሰይመውታል” ይላሉ፡፡ ከክርስቶስ ልደት በፊት የሌሎች አገሮች ሁሉ የዘመን መለወጫ ወር መስከረም እንደነበረም እኒሁ መምህር ያስረዳሉ፡፡ መልካም አዲስ ዓመት!

Read 15098 times