Saturday, 07 September 2013 10:29

ቅዳሴ የፆታ እኩልነት ጉዳይ አይደለም

Written by  መልካሙ ተክሌ
Rate this item
(4 votes)

                        ለዚህ ፅሁፍ መነሻ የሆነኝ ባለፈው ሳምንት በወጣው አዲስ አድማስ ጋዜጣ “ኅብረተሰብ” አምድ ላይ ካሌብ ንጉሤ የተባሉ ፀሃፊ “ሴቶች ለምን አይቀድሱም?” በማለት ራሳቸው ጠይቀው ራሳቸው የ”መለሱበት” ፅሁፍ ነው፡፡ ፀሐፊው ለሴቶች መቆርቆራቸው ያስመሰግናቸዋል፡፡
መፅሐፍ ቅዱስን አንብበው ከሆነ የፃፉት፣ በኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ 2 ቁጥር 18 “ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም፤ የሚመቸውን ረዳት እንፍጠርለት” ይለናል እንጂ እርሳቸው “ይመስለኛል” በማለት እንደገለፁት የመጀመርያው ሰው ብቻውን መኖር ስላቃተው “ኧረ ረዳት ፍጠርልኝ” አላለውም፡፡ የፈጣሪ ቅዱስ ፈቃድ ሆኖ ነው አዳም እና ሔዋን የተፈጠሩት፡፡
ነገር ግን ሄዋን የአምላክ ትእዛዝ እንዲጣስ በር ከፈተች፡፡ በከፈተችው በር አዳምም ገብቶ አታድርጉ የተባሉትን ስላደረጉና አትብሉ የተባሉትን ስለበሉ በሰዎች ላይ ሞት መጣ፡፡ ፍጥረቱን የማይረሳ እግዚአብሔር በሄዋን ስህተት የመጣውን ይህን ሞት ዳግማዊት ሄዋን ከሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያም ከ5500 ዓመታት በኋላ ተወልዶ አድኖናል፡፡ ሰለዚህ ሴቶች ምንም እንኳ በመስቀል ምእመናን ባርከው፣ በጥና ፀሎት አሳርገው ባይቀድሱም ቅድስናን ግን አልተነፈጉም፡፡

ድንግል ማርያም ወላዲት አምላክ ለሴቶች ቅድስና አቻ የሌላት መገለጫ ብትሆንም ሌሎችም ቅዱሳት እንስት አሉ፡፡ ቅዱሳት ስለሆኑ፣ ሴቶች መቅደስ ገብተው መቀደስ አለባቸው ብሎ መሟገት መፅሐፍ ቅዱሳዊ መሰረት የለውም፡፡ ስለዚህ አቶ ካሌብ ፅሁፋቸው ነገረ ሃይማኖት ላይ አተኮረ ይበሉን እንጂ ከነገረ ሐይማኖት መነሻዎች አንዱ የሆነውን መፅሐፍ ቅዱስን አለያም ሌላኛውን መነሻ ተፈጥሮን በቅጡ አልዳሰሱም፡፡ ቢዳስሱማ ኖሮ መፅሐፍ ቅዱሳዊ ያልሆነ እሳቤ ባላመጡ፣ ተፈጥሮን ከማስተዋልም ባልወጡ ነበር፡፡ ተፈጥሮን የተመለከተ ሰው፣ ተፈጥሮ የራሷ የሥራ ክፍፍል እንዳደላደለች ይረዳል፡፡ ከነዚህ ኃላፊነቶች አንዱ “መቅደስ ገብቶ መቀደስ ነው” ልክ የመውለድ ፀጋ ለሴቶች የተሰጠውን ያህል ቀድሶ መባረክም ለወንደች ከአምላክ የተሰጠ ኃላፊነት ነው፡፡

ዛሬ ሴቶች መቀደስ አለባቸው ያሉን ፀሐፊ፤ ነገ ደግሞ ወንዶች አርግዘው መውለድ ይችላሉ ላለማለታቸው እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ ይህ በራሳቸው ቃል ልጠቀምና “የፈጣሪን ትእዛዝ በአግባቡ አለመተግበር ወይም ያላዘዘውን የእሱ ቃል አስመስሎ የመተርጐም አባዜ ያለ ስለሚመስለኝ ነው” እንዳሉት ፀሐፊው ራሳቸው በይመስለኛል እየተረጐሙ ሌሎችን አጣመው ተረጐሙ ለማለት ይችላሉን? የራሳቸውን ዝሆን ሲያጠሩ የሌላውን ትንኝ ውጠዋልና አይችሉም፡፡
“ሴቶች ለምን አይቀድሱም?” በሚለው ፅሁፍ ውስጥ እስራኤላውያንን ከግብፅ ለማውጣት ከሰው ወገን ትልቁን ሚና ስለተወጣው ሙሴ ከመፅሐፍ ቅዱሳዊ እውነታ የማይገኝ የተሳሳተ መረጃ ተቀምጧል፡፡ ለእስራኤላውያኑ ሕግ ያወጣው አምላከ እስራኤል እግዚአብሔር እንጂ ሙሴ አይደለም፡፡ የሙሴ ሚና ከሲና ሕጉን ለሕዝብ ማድረስ ነበር፡፡ ታዲያ እግዚአብሔር ሙሴን ሲያስነሳ ታላቅ እህቱ ማርያም እና ወንድሙ አሮን ነበሩ፡፡ ቢፈልግ ኖሮ ልክ እነ አስቴር፣ ዮዲት… እንደተጠሩት ማርያምንም “ሕዝቤን ከግብፅ አውጭልኝ” በማለት ለሙሴ የተናገራቸውን ህግጋት በሙሉ በነገራት ነበር፡፡ ፀሐፊው ሙሴ ሕጉን ሴቶችን ለማርከስ እንደተጠቀመበት አስመስለው ፅፈዋል፡፡ እውነታው ግን እሳቸው እንደሚሉት አይደለም፡፡
እዚያው በኦሪት መፃህፍት ወዳለው እውነታ ከማምራቴ በፊት አለቃ ገብረሐና አደረጉ የተባለውን መጥቀስ ፈለግሁ፡፡
አለቃ ከሴቶች ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት እየፈፀሙ በቅዳሴ ሰዓት ሳይነፁ ቤተክርስትያን ገቡ፡፡ ይህን ከጊዜ በኋላ የተረዱት ካህናት በመቋሚያ ደብድበው አባረሯቸው፡፡ በዚህ ቂም የያዙት አለቃም በሌላ የቅዳሴ ቀን ማልደው ወደ ቤተክርስትያን በመሄድ በሴቶች መግቢያ በኩል ቆሙና ሴቶቹን “ዛሬ ቅዳሴ የለም” እያሉ መመለስ ያዙ፡፡ ቅዳሴ ሲጀመር አንዲትም ሴት ዝር አላለችም። ይህ ያደናገጣቸው ቀሳውስት ጉዳዩን ሲመረምሩ፣ የአለቃ ተንኮል መሆኑን ደረሱበት፡፡ አለቃንም በማፋጠጥ “ምነው?” ብለው ሲጠይቋቸው “ከምንጩ የቀመሰ ከረከሰ፣ ምንጩ ራሱ ርኩስ፤ ነው ከሴት ጋር ተኛህ ብላችሁ መቅደስ አረከስክ ካላችሁኝ፣ ራሳቸው ሴቶቹ ረከሱ ማለታችሁ ነው” አሉዋቸው፡፡
ሙሴ አርባ ቀን በሲና ተራራ ከፆመ በኋላ ነው ሕገ ኦሪት ከእግዚአብሔር የተሰጠው፡፡ በእነዚህ ሕጐች ክህነት ለተወሰኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ብቻ የተሰጠ ፀጋ ነው፡፡

በወቅቱ ከነበሩት ነገደ እስራኤል የሌዊ ልጆች ብቻ አገልግሎቱን እንደሚሰጡ፣ ከነሱም አሮን ክህነቱን እንደሚመራ ተጠቅሷል፡፡ እግዚአብሔር ይህን ሕግ ሲሰጥ ሴቶች መኖራቸውን ዘንግቶት ወይንም ሴቶችን ለመበደል አይደለም፡፡ አገልግሎቱ የሚጠይቀውን ንፅህና ወንዶች ራሳቸው ካላሟሉ ቤተመቅደስ አይገቡም፡፡ መግባትም አይችሉም፡፡ ምክንያቱም ቅዳሴ የመብትና የዲሞክራሲ ጉዳይ ሳይሆን የአገልግሎት ጉዳይ በመሆኑ ነው፡፡ በዚያው በሙሴ ጊዜ የነበረውን ዳታን ከወንድሙ ከአቤሮን ጋር በመሆን ገብተን ካላጠንን ብለው በማመፃቸው መቀሰፋቸውን እንዴት ዘነጉት አቶ ካሌብ? ዳታንና አቤሮን ወንዶች ናቸው፡፡
ወንዶች ብቻ መቀደሳቸው የአገልግሎት እንጂ የፆታ ጉዳይ ባለመሆኑ ለዘመናት ዘልቋል። ይህንንም በየዘመኑ የነበሩ ወንዶች እና ሴቶች ምእመናን ሲተገብሩት ቆይተዋል፡፡ አሁንም እየተገበሩት ነው። ለወደፊትም ይህንኑ ይቀጥላሉ፡፡
በታሪክ የተነሱ እና የዘመናቸውን ሕግ ለመቀየር አቅም የነበራቸው ሴቶች ሳይቀሩ ቅዳሴ ለወንድ ብቻ የተተወ መሆኑን አምነው ተቀብለዋል፡፡ ይህ ግን ሴቶች በቅዳሴው የራሳቸው ሚና የላቸውም የሚያሰኝ አይደለም፡፡ የራሳቸው የሥራ ድርሻ አላቸው፡፡
ገዳማት ለሴቶች ክፍት የሚሆኑበትና የማይሆኑበት ሕግም አለ፡፡ ገዳማት የሴት፣ የወንዶች ወይም የአንድነት በመባል ይከፈላሉ፡፡ ከነዚህ ወንዶችንም ሴቶችንም የሚያስተናግደው የአንድነት ገዳም ነው፡፡ የወንድ ገዳም ሴት፣ የሴት ገዳም ወንድ አይገባበትም፡፡
በሴት ገዳም ወንድ ሊገባ የሚችለው በቀዳሽነት ብቻ ነው፡፡ ከወንድ ገዳማት አንዱ የሆነውን ሴቶች ፈፅሞ የማይገቡበትን የደብረዳሞ ገዳም የማየት ጉጉት ያደረባት አንዲት ፈረንጅ እንደወንድ ለብሳ ለመግባት ባደረገችው ጥረት ገመዱ ተበጥሶ መከስከሷ የቅርብ ጊዜ ታሪክ ነው፡፡
መፅሐፍ ቅዱስን አንብቤአለሁ፤ ክርስትናን እቀበላለሁ ያሉት ፀሐፊ “ማረጥ… መጠውለግ…” የሚሉትን ቃላት ከየት እንዳመጡት ፈፅሞ አልገባኝም፡፡ ምክንያቱም እነ ሳራ ካረጁ በኋላ ሌሎችም በመካንነት ከቆዩ በኋላ ለመውለድ በቅተዋልና፡፡ እኔ የምለው የት ሀገር ይሆን ወላጅ (እመጫት) ሴት መቅደስ ገብታ የምትቀድሰው?
እርስዎ ያነሱት ጥያቄ ተገቢ ቢሆን ኖሮ ያነሱዋት ልጆች ከወለደች በኋላ ቅድስና ያገኘችው ቅድስት ክርስቶስ ሰምራም አምላኳን ጥያቄዎን በጠየቀች ነበር፡፡ እሷ ግን ሴቶች መቅደስ ገብተው ይቀድሱልኝ ብላ ሳይሆን ባህር ገብታ የፀለየችው እንደ እርስዎ እና እኔ አይነቶችን እንዳያስት ሰይጣንን ማርልኝ ነው ያለችው፡፡
እርሷም ሆነች ሌሎች እንስቶች እርስዎ እንዳሉት፤ ጀግና ወልደዋል፡- የጀግና እናት፣ የቄስ እናት፣ የጳጳስ እናት፣ የአምላክ እናት… ናቸው፡፡ ጉልበት ስለሌላት አይደለም ቄስ፣ ጳጳስ፣ ያልሆነችው፡፡ የእግዚብሔር ምርጫ ነው፡፡ ጉልበትም የሚሰጥ እግዚአብሔር ነው፡፡ አላዩም እንዴ እቴጌ ጣይቱን? አላዩም እንዴ የቀድሞዋን የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ማርጋሬት ታቸርን ከአጀንዳ እንዳልወጣ፡፡ አጀንዳዬ አሁንም ሴቶች መቅደስ አልተፈቀደላቸውም የሚል ነው፡፡ አልተፈቀደላቸውም ማለት ቅዱሳን አይደሉም ማለት ግን አይደለም፡፡
ስለዚህ ሴቶች የክርስቶስን ትንሣኤ ቀድመው ስላዩ መቅደስ ገብተው መቀደስ አለባቸው በሚል ያቀረቡት መከራከሪያ የሚያዋጣ አይደለም፡፡
ጌታችን፣ መድሃኒታችን፣ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስራሁለት ሐዋርያት ሲመርጥ ሁሉም ወንዶች ነበሩ (ሐዋርያነት የፆታ ጉዳይ ባይሆንም) ሰላሳ ስድስት ቅዱሳት እንስትም መርጧል ከሴቶች። ሰባ ሁለት ሌሎች አርድእትም ነበሩ ከሁለቱም ፆታ፡፡ በደብረታቦር ምስጢረ መለኮቱን ሲገልፅ ከሐዋርያት ሦስቱ ብቻ ናቸው ተራራው አናት ላይ አብረው የነበሩት፡፡ ዘጠኙ ሐዋርያትና ሰላሳ ስድስቱ ቅዱሳት ሴቶችም ሆኑ አርድእት አልነበሩም፡፡ ሞትን ድል ነስቶ ሲነሳ አቶ ካሌብ ንጉሤ እንዳሉት ቀድመው ያዩት ሴቶች ናቸው፡፡ ከሴቶችም የመጀመርያዋ መቅደላዊት ማርያም ነበረች፡፡ ነገር ግን “ረቡኒ (መምሕር)” ብላ ስትጠጋው ዳስሳው የተፈወሰችውን ሴት “አትንኪኝ” ብሏታል፡፡ በጥርጣሬ ተኮማትሮ በጌታ ምህረት ቢፈወስም ቶማስ ነበር የዳሰሰው፡፡ ምን ያህል ተረዱልኝ አቶ ካሌብ?

 

Read 4462 times