Saturday, 31 August 2013 12:36

“መንጠልጠል”

Written by  ጤርጢዮስ - ከቫቲካን
Rate this item
(1 Vote)

ብትል “አፍሮጋዳ” ትዝ አለኝ!
ያለፈው ሳምንቱ የ “እኛና ስብሐት” ፀሐፊ፤ “ጫጫታችሁ ረብሾኛል” ለማለት ብዕሩን ሲያነሳ “መንጠልጠል” የምትለዋን ኃይለ ቃል የተዋሰው ከዚያ ቀደም ባለው ቅዳሜ “ስብሐት ላይ የመንጠልጠል ጣጣ” በሚል ርዕስ ከቀረበ ጽሑፍ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ የሁለቱ ፀሐፊዎች የጽሑፍ ይዘት ኩታ ገጥመነትም “ከእኛ በቀር ሁልሽም በገዘፉ ስሞች ላይ በመንጠልጠል ትራፊ ዝናን የመልቀም አባዜ ተጠናውቶሻል” በሚል ተአብዮ መሞላቱ ነው፡፡ ይህም ከብዕር አጣጣላቸውና ከሃሳብ አሰነዛዘራቸው ያስታውቃል፡፡ ግና ሁለቱም በስብሐት ስም ላይ ከመንጠልጠል ጣጣ የፀዱ ስለመሆናቸው ምንም መተማመኛ የለንም፡፡ ወይም አላቀረቡልንም፡፡
ጋሼ ስብሃትን የተመለከተ ነገር መፃፍና መናገር የሁልጊዜውም ትርጉም “በገዘፈ ስም ላይ የመንጠልጠል አባዜ” ከሆነ እነርሱም ከዚህ የመንጠልጠል ጣጣ የሚያመልጡበት አንዳች “ምስ” በእጃቸው መኖሩን አላሳዩንም። “መንጠልጠል” የብላጣብልጦች ዘዴ ከሆነም ለብልጣብልጥነቱ እነርሱ ብሰው ታይተውኛል፡፡ ሌሎችን “አትንጫጩ” ብለው ከተቆጡ በኋላ፣ እነርሱም ስለ ጋሼ ስብሐት ያሉት ነገር በ “ፀጥታው” መካከል የበለጠ ለመደመጥ ያላቸውን ብርቱ ጉጉት አሳበቀባቸው እንጂ ስለ ስብሐት አስቀድሞ ከተባለው የተለየ ነገር አልነገሩንም፡፡
ይልቁንም ቀድሞ መጪው ፀሐፊ፤ የአገራችንን ኪነጥበብ በተለይም ሙዚቃውንና ሥነ ጽሑፉን የተጣባውን፤ በገዘፉ ስሞች ላይ የመንጠልጠልን አባዜ መፀየፉን፤ “እንግዲህ ይህን ጽሑፍ ልጽፍ የተነሳሁበት መሠረታዊ ምክንያት እኔም ሲያደርጉ እንዳየሁት ስለ ስብሐት የመናገር ዛር ለክፎኝ አይደለም” ቢልም ገና “በቅርበት አላውቀውም” ያለውን ስብሐት፤ ከራሱ ከስብሐት በላይ ሊገልፀው መታተሩን የተመለከተ ሰው፣ እርሱም በዚያው ልክፍት መያዙን አያጣውም፡፡ ዛሬ ግን የምጽፈው ለእርሱ ሳይሆን ለ“አምሣያው” ነው፡፡ ለሌሊሣ ግርማ፡፡
ሃሳብን በመግለጽ ነፃነት የሚያምኑ የሚመስሉ አንዳንድ ሰዎች እነርሱ መስማት የማይሹትን ሃሳብ ለማፈን የሚጐነጉኑትን ሴራ፣ የሚፈነቅሉትን ድንጋይ፤ የሚፈጥሩትን ሰበብ ነፍሴ አጥብቃ ትፀየፈዋለች፡፡ “ሃሳቡ ምንድነው” ከማለት ይልቅ “አሳቢው ማነው” የሚልን ጥያቄ አስቀድመውና ፊታቸው ደቅነው ፍርድ የሚያዛቡ ሰዎችንም ዝም ማለት አልችልም፤ ይልቁንም ለጊዜው ስሙ እንደጠፋኝ እንደዚያ ሰውዬ “ነፃነቴን ስጡኝ፤ አለዚያ ግደሉኝ” በሚል ወኔ ነገሬ ለሚገባቸውም፣ ለማይገባቸውም ሃሳቤን እገልጣለሁ፡፡ በንግግርም፣ በጽሑፍም፡፡ ይህንን ለማድረግ ደግሞ “ሠፈር” አልመርጥም፡፡ ሰው ያለበት “ሰፈር” ሁሉ ሰፈሬ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ በሰውነቴ እስከተቀበሉኝ ድረስ፣ የመናገርና የመፃፍ ነፃነቱን እስከሰጡኝ ድረስ፡፡
ከሦስት ሣምንት በፊት ጋሼ ስብሐትን አስመልክቶ በተፃፈ ጽሑፍ የተፈጠረብኝን ግርታና፣ የተሰማኝን ስሜት የፃፍኩትም ይህንኑ ነፃነቴን ተገን አድርጌ ነው፡፡ ስፅፍ ደግሞ ሃሳቤን በመግለፄ መርካቴን እንጂ ከመፃፌ ስለማገኘው ሌላ ትርፍ አስቤ አላውቅም፡፡ በእርግጥ አንዳንድ ሰው ሲጽፍ ከዚያ የሚያገኘውን ትርፍና ኪሣራ እያሰላ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ አንዳንድ ርዕሰ ጉዳዮች ግን የበለጠ ትርፍ የሚገኝባቸው መሆኑንም ምሥጢሩን የማያውቁ ከላይ የጠቀስኳቸው ፀሐፊያን ነግረውኛልና አምኛቸዋለሁ፡፡ እኔም ሳላውቀው የዚህ ትርፍ ተጋሪ ሆኜም ይሆናል ጉም ጉምታው የተነሳብኝ፤ ትርፌን ተቀራማች የበዛብኝ፡፡ ከነዚያም አንዱ ሌሊሣ ግርማ ነው፡፡ (ምነዋ ምን በደልኩህ ወንድሜ? ስለምንስ “በስብሐት ላይ ተከራከርኩ” ብዬ ጉራዬን የምነፋበትን ሜዳ ልታሳጣኝ ወደ ግዛቴ መጣህብኝ?)
ሌሊሣ ለ”እኛና ስብሐት” መጣጥፉ አጫፋሪነት “ከአምሳያው” የጽሑፍ ማሣ ላይ የነቀላት “መንጠልጠል” የምትል ቃል እኔን ለመግለጽ የምትመጥን እንደሆነች ተማምኖ ያመጣት ናት፡፡ ቢሆንም እኔን አላስደነገጠችኝም፡፡ “መንጠልጠል የሚለው ቃል የበለጠ የሚገልፀው ጤርጢዮስን ነው” የሚለውን ዓ.ነገር ባነበብኩ ጊዜም “ቤቶች” ድራማ ላይ ያየሁትን ገፀ ባህሪ አባባል አስታውሼ “እኔን ነው?” ብዬ ሣቅሁ እንጂ በፍፁም አልተከፋሁም፡፡
ሆኖም ሌሊሣ “ጤርጢዮስ ሁሌም ለመፃፍ የሆነ ነገር መመርኮዝ ያስፈልገዋል” በማለቱ እስማማለሁ፡፡ ስለዚህም ደግሞ “መንጠልጠልን” ነቅፌ፣ “መመርኮዝን” ደግፌ መልስ እሰጣለሁ (እንደለመደብኝ)፡፡ እውነት ነው ለመፃፍ ብዬ ጽፌ አላውቅም፡፡ ለመፃፍ ከተነሳሁም አንዳች ምክንያት፣ አንዳች መመርኮዣ አግኝቻለሁ ማለት ነው፡፡ ሁሉስ ሰው ቢሆን ለመፃፍ የሚነቃቃበት አንዳች ምክንያት ያስፈልገው የለምን? ሁሉስ ፀሐፊ የክስተት ጥገኛ አይደለም እንዴ? ክስተትን ሳይመረኮዝ ብዕር የሚያነሳ ፀሐፊስ የትኛው ነው? ሩቅ ሳንሄድ አንተ ሌሊሣ ራስህ “እኛና ስብሃት”ን የፃፍከው ከዚያ አስቀድሞ ባነበብከው “በስብሐት ላይ የመንጠልጠል ጣጣ” ላይ ተመርኩዘህ አይደለም እንዴ? ልዩ ክስተትን አድፍጣ የምትጠባበቅ ገጣሚ ነፍስ ያለችው የአዲስ አድማሱ ነቢይ መኮንንስ በዚሁ ሰሞን “ያልነው አልቀረም ጥሩዬ፣ ነገር የገባሽ ሰጐን ነሽ” የሚለውን ልብ የሚያሞቅ “ሦስተኛ” (ቁ.3) ግጥሙን ለጥሩነሽ ዲባባ የገጠመላት የሞስኮን ኦሎምፒክ ድል ተመርኩዞ አይደለም እንዴ? (ምናልባት ጣቢያ ቀላቅዬ ካልሆነ መመርኮዝን የምረዳው እንደዚህ ነው)፡፡
እኔም እንግዲህ አንድ ሰሞን በዚሁ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ሃይማኖታዊ ክርክሮች ተነስተው በነበረ ጊዜ የክርክሩ ንቁ ተሳታፊ ነበርኩ፡፡ ሌሊሣም ይህንኑ ጠቅሷል፡፡ ሆኖም በክርክሩ ሜዳ “ጤርጢዮስ - ከቫቲካን ሁሌም መልስ ነው የሚሰጠው፣ መልሱም ላልተጠየቀበት ጥያቄ መሆኑ የለመድነው አባዜ ነው” ከሚለው ብይኑ የምቀበለው የመጀመሪያውን ዐ.ነገር ብቻ ነው፡፡ “መልስ ሰጪ” ተደርጌ መቆጠሬም እነ ሌሊሣ ጭንቅላት ውስጥ ለሚብላላው ጥልቅ የህይወት ጥያቄ ፍፁም መልስ ያለው በእግዚአብሔር ዘንድ መሆኑን በማመኔ ነው፡፡
በመሆኑም አላፍርበትም፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን የአእምሮዬን ስምምነት አልፎ ወደ ልቤ ዘልቆ የገባውን መለኮታዊ እውነት “መልስ” አድርጌ ማቅረቤንም መቼም ቢሆን የምተወው አይደለም፡፡ መንጠልጠል ካስፈለገኝም የምንጠለጠለው እሱ ላይ ነው፡፡ ሌሊሣ እንዳለው ዞሬ …ዞሬ “የምገነድሰው” አምላኬ ላይ በመሆኑ የ”ነፍሴ ጥሪ”ም እርሱን ለማግነን በመዋሉ እጅግ እኮራለሁ፡፡
በቀረው ግን ለመፃፍ ብዬ “ሳይጠሩኝ አቤት” ያልኩበት አጋጣሚ መኖሩን፣ የገነነ ስም ባላቸው ላይ ተንጠልጥዬ “እዩኝ” ያልኩበትን ርዕሰ ጉዳይ በውል አላስታውስም፡፡ ሃሳቤን ለመግለጽ ምክንያት ከሆነኝ ግን ይሉኝታን ፈርቼ የምተወው ማንም የለም፡፡ ጮክ ብሎ የሚሰማ ያለማመን ጩኸት ካልሰማሁም “መልስ ለመስጠት” አልነሳም፡፡ በዚህ ሰሞንም ሌሊሣን ዕረፍት በሚነሳ መልኩ ለተጀመረው “ጫጫታ” ቆስቋሹ እኔ አልነበርኩም፡፡ በስብሐት ላይ ለመንጠልጠል መገለጫ ልሆን የምችልበትም ምንም ምክንያት የለም፡፡ የእኔ ድርሻ ካለም የ”ዝምታው” ሰምና ወርቅ ተፈልቅቆ እስካየሁት ድረስ በ”ዝምታው” ያስደምመኝ የነበረውን፣ የወዳጄ ሚልኪ ባሻን “ስለ ስብሐት እኔን ጠይቁኝ” ዓይነት ጽሑፍ ለመሄስ መነሳቴ ብቻ ነው፡፡
ያም ከወዳጄ የማልጠብቀውን ስድብ የመጠጣትን ዋጋ አስከፈለኝ እንጂ ስብሐት ላይ “በመንጠልጠሌ” ያተረፍኩት ምንም የለም፡፡ (ሚልኪ ወዳጄ፤ እንዲያ እስከ ዶቃ ማሠሪያዬ ሞልጭኸኝ ስታበቃ “ለጢርጢዮስ መልሴ ዝምታ ነው” ማለትህ ግን እስካሁንም አልገባኝም፡፡)
ሌላውን ወዳጄን ሌሊሣ ግርማን የምለውና የምጠይቀው ደግሞ የሚከተለውን ነው፡፡ “መንጠልጠል” የሚለው ቃል የበለጠ የሚገልፀው እኔን (ጤርጢዮስን) ይሁን፣ ግና በኪነጥበቡ ዓለም በገዘፉ ሰዎች ላይ መንጠልጠል የገንዘብና የዝና ትርፍ የሚያስገኝ ከሆነ፣ አንተስ ለመጽሐፍህ “አፍሮጋዳ” የሚል ርዕሰ ለመስጠት የተነሳህበት ዓላማ ምን ነበር ይሆን? “አፍሮ” ቴዲ አፍሮን፣ “ጋዳ”ም የ “ዴርቶጋዳ” መጽሐፍ ፀሐፊን ይስማዕከን የሚመለከት ነውና፣ ሁለቱ ወጣቶች ደግሞ ለሚያጌጡባቸው ብዙዎች የጊዜው ፈርጦች መሆናቸውን አሳምረህ ታውቃለህና፣ የእነርሱን ስምና ተግባር የሚወክል ርዕስ ለመጽሐፍህ መስጠትህ፣ ብሎም እነርሱኑ መተንኮስህና ማቃለልህ “መንጠልጠልን” የበለጠ የሚገልፀው አይመስልህም? ከእነርሱ ስም በላይ ስምህን ለማግነን ሆን ብለህ ያደረግኸውስ አይደለምን?ይሄ በምን ትዝ አለህ አትለኝም፡፡ ባለፈው ሳምንት “በስብሐት ላይ የመንጠልጠል ጣጣ” ብሎ የፃፈልን ያንተ “አምሣያ”፣ የ”መልክዓ ስብሐት” መጽሐፍን አዘጋጅ አለማየሁ ገላጋይን በስብሐት ላይ በመንጠልጠል ክፉኛ ሲወቅሰው፣ በተቃራኒው ያንተን “አፍሮጋዳ”፣ የዘመናችንን መልክ ማሳያ መስታወት አድርጐ በምሣሌነት ጠቅሶት ተመልክቼ ለካስ ሁላችንም “ተንጠልጣዮች” ነን፡፡

Read 1742 times