Saturday, 31 August 2013 12:23

ዘፍመሽ ግራንድ ሞል

Written by  መንግሥቱ አበበ
Rate this item
(5 votes)

“የስኬት ምስጢራችን ትጋትና ለችግር ያለመሸነፍ ነው”
አራት ሲኒማ ቤቶች አራት ሲኒማ ቤቶች
አንድ ፎቅ የቤተሰብ መዝናኛ

በአሁኑ ሰዓት በዓለም ግዙፍ የመገበያያ ሞሎች ባለቤት በመሆን ቻይናን የሚወዳደራት አልተገኘም፡፡ በ892ሺህ ካ.ሜ ወለል ላይ ያረፈው ትልቅ የገበያ ማዕከል በዓለም ቀዳሚ ነው፡፡ እዚያው ቻይና ውስጥ በ680ሺህ ካ.ሜ ወለል ላይ የሰፈረው የቤጂንግ ሞል በዓለም የሁለተኝነትን ደረጃ ይዟል። በ480ሺህ ካ.ሜ ወለል ላይ ያረፈው የፊሊፒንስ ሞል ሦስተኛ፣ በ465ሺህ ካ.ሜ ወለል ላይ የሰፈረው የማሌዥያ ሞል ደግሞ አራተኛ ነው፡፡ ቀደም ሲል ከ1986 -2004 ድረስ በዓለም 1ኛ የነበረው የካናዳው ዌስት ኤድመንተን ሞል፣ አሁን አራት ደረጃዎችን ተንሸራትቶ 5ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በአገራችንም ትላልቅ የገበያ ማዕከላት ብቅ ብቅ እያሉ ነው፡፡ ለአብነት ደንበል ሲቲ ሞል፣ ጀሞ ሞልና ኤድና ሞልን… መጥቀስ ይቻላል፡፡ በቅርቡ ደግሞ መገናኛ አደባባይ አካባቢ በ4ሺ ካ.ሜ ወለል ላይ ያረፈው ዘፍመሽ ግራንድ ሞል በአገራችን የሞል ታሪክ አዲስ ነገር ይዤ መጥቼአለሁ ይላል፡፡ ስምንት መውጫና መውረጃ ተሽከርካሪ ደረጃዎች (ስካሌተርስ)፣ ሁለት ከውስጥም ከውጪም የሚያሳዩ የመጓጓዣ አሳንሰሮች (ሊፍት)፣ አንድ ግዙፍ የዕቃ ማጓጓዣ ሊፍት፣ 250 ሱቆች መያዛችን እንዲሁም በአንድ ጊዜ ከ1,200 ሰዎች በላይ የሚያስተናግዱ አራት ሲኒማ ቤቶች፣ 12 የተለያዩ አገራት ሬስቶራንቶች (food courts) ማካተታችን በአገራችን የመጀመሪያው ያደርገናል ይላሉ - የዘፍመሽ ግራንድ ሞል ሥራ አስኪያጅ አቶ ነጋ አስፈሃ፡፡
አቶ ነጋ፣ በአሜሪካ ለ22 ዓመት ከኖሩ በኋላ ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት ከሰባት ዓመት በፊት እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከአሜሪካ በማርኬቲንግ ማኔጅመንት አግኝተዋል። በሙያቸው በግል ድርጅቶች ውስጥ በመሥራት ሰፊ ልምድ ከማካበታቸውም በላይ ከቤተሰብ ጋር አነስተኛ ቢዝነስ አቋቁመው መርተዋል፡፡ አሜሪካ እያሉ ሞሎችን የማማከር ልምድ እንደነበራቸው የሚናገሩት አቶ ነጋ፤ ከአሜሪካ ጓዛቸውን ጠቅልለው ወደ አገራቸው ከተመለሱ አራትና አምስት ዓመት ሆኗቸዋል፡፡ እዚህ ከተመለሱ በኋላ ዘፍመሽ ግራንድ ሞልን በተለያየ ደረጃ ሲያማክሩ ቆይተው፣ ሥራ አስኪያጅ የሆ ኑት ከስድስት ወር በፊት እንደሆነ ገልፀዋል፡፡


ዘፍመሽ ግራንድ ሞልን አስመልክቶ ከአቶ ነጋ ጋር ያደረግነውን ቃለ - ምልልስ በዚህ መልኩ አቅርበናል፡፡ ለመሆኑ ሞል በአማርኛ እንዴት ይገለፃል? አልናቸው፡፡
ሞል በቀላል አነጋገር የመገበያያ ማዕከል ሊባል ይችላል፡፡ በዓለም ደረጃ ሞል ሲባል አንድ አማካይ ቦታ ሰብሰብ ባለመልኩ የተለያዩ የንግድ ዘርፎች ተሰብስበው አገልግሎት የሚሰጡበት የገበያ ማዕከል ነው፡፡ የሞል ባህል ከ10 እና ከ15 ዓመት ጀምሮ በአገራችንም እየተለመደ ነው፡፡
ሞል ከሌላው የገበያ ስፍራ የሚለየው ባህርይ አለው?
አዎ! አማካይ የሆነ ቦታ ተፈልጐ፣ የሚከፈት የንግድ ማዕከል ነው፡፡ በንጉሡ ዘመን፣ መርካቶ “አዳራሽ” የሚባል የንግድ ማዕከል ተከፍቶ ነበር፡፡ አሁንም ድረስ አለ፡፡ የሞል ሐሳብ፣ ድሮም በአገራችን የነበረ ሊሆን ይችላል፡፡ የአገር ባህል ጥበብ፣ ጫማ፣ ቦርሳ፣…የተለያዩ ዕቃዎችን የሚሸጡ ሰዎች አሉ። ስለዚህ ሞል የተለያዩ የመገልገያ ዕቃዎችን ምቹና ደህንነቱ በተጠበቀ ቦታ ቤተሰብ የሚገበያይበት ቦታ ማለት ነው፡፡ የተለያዩ አነስተኛ ሱቆች በተራራቀ ስፍራ ተበታትነው ከሚነግዱ፣ አንድ ቦታ ሰብሰብ ብለው ምርትና አገልግሎታቸውን ሲያቀርቡ፣ ሸማቹ ከውጣ ውረድና ከድካም ይድናል ማለት ነው፡፡ ይህ ለየት ያደርገዋል፡፡
ዘፍመሽ ምንድነው?
ዘፍመሽ ፒኤልሲ መሠረቱ የቤተሰብ ንግድ ነው፡፡ ዋና ባለአክሲዮኖች (ሼር ሆልደርስ) ሁለት ናቸው፡፡ ወ/ሮ ዘውዲቱ አህመድና አቶ መሐመድ አህመድ ናቸው፡፡ ሁለቱም ማኔጂንግ ዳይሬክተሮች ናቸው፡፡ ሁለቱ ዋነኛ ይሁኑ እንጂ ሌሎችም ሼር ያላቸው የቤተሰብ አባላት አሉ፡፡ እንግዲህ ዘፍመሽ የባለአክሲዮኖቹ ስም የመጀመሪያ ፊደል ተገጣጥሞ የተፈጠረ የቤተሰብ ቢዝነስ ነው ማለት ነው፡፡
ዘፍመሽ መቼና እንዴት ተጀመረ?
ዘፍመሽ ሲመሰረት እዚህ አልነበርኩም፡፡ ቢሆንም ሲነገር እንደሰማሁት ከ15 ዓመት በፊት ነው የተመሰረተው፡፡ የፋሽን ጨርቆችን (ልብሶች) ከውጭ በማምጣትና በመለስተኛ ዋጋ በመሸጥ ነበር የጀመረው፡፡ ከዚያም ሥራው ውጤታማ በመሆኑ በተለያዩ አካባቢዎች ሱቆች ከፍቶ መንቀሳቀስ ቀጠለ፡፡ በአንድ ወቅት ዘፍመሽ 20 ሱቆች ነበሩት። ስኬታማ እየሆነ ሲሄድ የንግድ ዘርፉን ወደ ኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች (ቲቪ፣ ፍሪጅ፣ የተለያዩ የመብራት ዓይነቶች…) በመለወጥ መንቀሳቀስ ጀመረ፡፡ ከዚያም የስኬት ጐዳናው እያማረ ሲሄድ አሁንም የንግድ ዘርፉን በመለወጥ ወደ ፈርኒቸር ዘርፍ በመግባት፣ የቤትና የቢሮ ዕቃ ማቅረብ ጀመረ። በዘርፉ ከፍተኛ ጥራት ያለው ዕቃ ከሚያቀርቡ ድርጅቶች አንዱ ሆኗል፡፡ አሁን ገርጂ ጃክሮስ አካባቢ ትልቅ ሾው ሩም (ስቶር) አለው፡፡ ካለፈው አምስት ዓመት ጀምሮ ደግሞ ወደዚህ ግራንድ ሞል ግንባታ ገባ፡፡
ይህን ሞል ለመገንባት ምን አነሳሳቸው?
በንግዱ ምክንያት ዕቃ ለማምጣት በሚሄዱባቸው አገራት፡- በቻይና፣ በዐረብና በአፍሪካ አገራት ሲንቀሳቀሱ ትላልቅ ሞሎች ያያሉ። እኛስ ለምንድነው እንደቻይና፣ ዱባይ… ትላልቅና ዘመናዊ ሞል የማይኖረን የሚል ሐሳብ አደረባቸው። ያሰቡትን ተግባራዊ ለማድረግ ወሰኑና ዲዛይን አሰሩ፡፡ ለገበያ አማካይ የሆነ ቦታ ተፈልጐ ከመገናኛ ድልድይና ከዲያስፖራ አደባባይ መኻል ያለው ቦታ ተመርጦ ግንባታ ተጀመረ፡፡
ቦታው ምን ያህል ነው? በግዢ ነው? በምሪት?
በሊዝ ተገዝቶ ነው፡፡ ጠቅላላው የመሬቱ ስፋት 11ሺህ ካ.ሜ ሲሆን፣ ሞሉ ያረፈው 4ሺ ካ.ሜ ላይ ነው፡፡ ሞሉ መገበያያ ብቻ ሳይሆን ሰው ዕቃውን ሲያማርጥና ሲገዛ ቆይቶ ሲደክመው አረፍ ብሎ የሚመገብበትና የሚዝናናበት የመገበያያ ስፍራ ነው። ይህን ያደረግነው በማስፋፊያ ሳይሆን ገና ዲዛይኑ ሲሰራና ሕንፃው ሲገነባ ጀምሮ ለሞል ነው የተሰራው፡፡ ከሱቆችና ከመዝናኛ በስተቀር የቢሮ ክፍሎች የሉንም፡፡ ያለው ቢሮ የዘፍመሽ የአስተዳደር ቢሮና አስፈላጊ አገልግሎት የሚሰጡ የባንክና የፋርማሲ ቢሮ ብቻ ናቸው፡፡
ይህን ሞል በአገራችን ካሉ ሌሎች የመገበያያ ማዕከላት ለየት የሚያደርገው ነገር ምንድነው?
ሞሉ በቂ ብርሃንና የአየር ማስተንፈሻ አለው። ሱቆቹም ጣራቸው ረዣዥም ነው፡፡ ውስጥ ከተገባ በኋላ እንደልብ የሚያንቀሳቅሱ ኮሪደሮች፣ 8 ተንቀሳቃሽ ደረጃዎች (ስካሌተርስ)፣ ተሳፋሪው ሱቆቹንና አካባቢን እያየ፣ ከውጪም ሰዎች ተሳፋሪውን እያዩ የሚጓዝበት 2 የመስተዋት አሳንሰሮች (ሊፍቶች)፣ ግዙፍ የዕቃ ማጓጓዣ አሳንሰር አለን፡፡ በየመኻሉ በርካታ ደረጃዎችና መላለፊያዎች፣ በየፎቁ በርካታ የወንዶችና የሴቶች መፀዳጃ ቤቶች አሉ፡፡ እነዚህ ነገሮች ለየት ያደርጉናል ብለን እናምናለን፡፡
ሌላው ደግሞ እዚህ የሚመጣ ሰው የፈለገውን ነገር ማግኘት አለበት ብለን እናምናለን፡፡ 250 ሱቆች ሲኖሩ በ40 ዘርፎች የተሰማሩ ናቸው፡፡ ሽቶ፣ ጫማ፣ መኪና ማስዋቢያ፣ የስጦታ ዕቃዎች፣ መጻሕፍት፣ የወንዶችና የሴቶች ፋሽን፣ የኤሌክትሮኒክስ ዞን (የተለያዩ ሞባይሎች፣ ቴሌቪዥኖች፣ ካሜራዎች፣ የልጆች ልብስና መጫወቻ…) ብዙ ዘርፎች አሉ፡፡ ከእነዚህ ዘርፎች ሸማቹ የሚፈለገውን ያገኛል ማለት ነው፡፡ ሌላው ደግሞ የሸማቹ ደህንነትና ምቾት የተጠበቀ ነው፡፡ በስውር ካሜራና በግልጽ ጥበቃ ደህንቱን እንከታተላለን፡፡
ሸማቹ አማራጭ (Choice) እንዲያገኝም አድርገናል፡፡ ለምሳሌ የአልባሳትን ዘርፍ ብናይ 50 ሱቆች አሉ፡፡ ከእነዚህ ሱቆች ሸማቹ በዋጋና በጥራት እንደአቅሙ የሚመቸውን መምረጥ ይችላል፡፡
ዋጋቸውስ እንዴት ነው?
ለምሳሌ ከ50 ሱቆች መካከል ጃኬት በ600 ብርና በ1500 የሚሸጡ ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ በእነዚህ ዋጋዎች መካከል ያለው ልዩነት ሰፊ ነው፡፡ ከ900 ብር እስከ 1000 ብር የሚሸጡ ሊኖሩ ይችላል፡፡ ስለዚህ ሸማቹ እንደአቅሙ መምረጥ ይችላል፡፡
ሌላው ልዩ የሚያደርገን የሲኒማ ማዕከላችን ነው፡፡ 250፣ 350ና 700 ሰዎች ማስተናገድ የሚችሉና ሰቨን ዲ ሲኒማ ቤቶች አሉን፡፡ 700 ሰው በሚያስተናግደው ትልቁ ሲኒማ ቤት ቪ አይ ፒ አለው፡፡ በአንድ ጊዜ በአራቱ ሲኒማ ቤቶች የተለያዩ ፊልሞች ስለሚቀርቡ፣ ተመልካቹ እንደፍላጐቱ የአገር ውስጥ ወይም የውጭ አገር ፊልም የመምረጥ ዕድል አለው፡፡
አንድ ሙሉ ፎቅ የቤተሰብ መዝናኛ ማዕከልም አለን፡፡ ፎቁ በሞላ፣ ከትናንሽ ሕፃናት እስከ ታዳጊዎች ያሉ ልጆች የሚዝናኑባቸው ዘመናዊ መጫወቻዎች ይኖሩታል፡፡ ስለዚህ እንደየ ዕድሜያቸውና ፍላጐታቸው መርጠው ይጫወታሉ ማለት ነው፡፡ ልጆቹን ይዘው የሚመጡ እናቶች የሚያርፉበትና ለሕፃናቱ ዳይፐር የሚቀይሩበትም ክፍል ተዘጋጅቷል፡፡
7ኛ ፎቅ ላይ ሆኖ አካባቢውን 360 ዲግሪ እያዩ የሚዝናኑባቸውና የሚመገቡባቸው የ12 አገራት ሬስቶራንቶች አሉ፡፡ በእነዚህ ሬስቶራንቶች የተለያየ አገር ምግቦችና ባህላዊ ምግቦች አማርጦ መመገብ ይቻላል፡፡ የአገራችን፣ የቻይና፣ የዐረብ፣ የሕንድ፣ …ምግቦች ይሰናዱባቸዋል፡፡
ዘፍመሽ መነሻ ካፒታሉ ምን ያህል ነበር
15 ዓመት ወደኋላ ሄጄ የተጀመረበትን ካፒታል ማስታወስ አልችልም፡፡ ነገር ግን በመለስተኛ ትንሽ ካፒታል እንደሆነ መናገር እችላለሁ፡፡ የሰውን ፍላጐት በማጥናት ያንን ትንሽ ካፒታል በአግባቡ በመጠቀም፣ አነስ ያሉ ሱቆችን በመከራየት፣ ቤተሰቡ በሙሉ በመሥራት ነው ለእዚህ ደረጃ የበቁት፡፡
የዘፍመሽ ግራንድ ሞል ግንባታ ምን ያህል ብር ፈጀ?
በጣም ብዙ ሚሊዮን ብር ነው፡፡ 4ሺ ካ.ሜ ላይ ሳይሆን 1,000 ካ.ሜ ላይ ያረፈ ሕንፃ እንኳ ብዙ ሚሊዮን ብር እንደሚፈጅ መገመት ይቻላል፡፡ ሕንፃውን ማቆም ሳይሆን ፊኒሺንጉ ቀላል አይደለም፡፡ በመጀመሪያው ምዕራፍ የተከፈቱት ሃይፐርማርኬቱ፣ ሱቆቹና የ400 መኪና ማቆሚያ ስፍራ ነው፡፡ እስከ 3ኛ ፎቅ ያሉትን 250 ሱቆች አደራጅተን ሥራ ጀምረዋል፡፡ ሲኒማ ቤቱ፣ የልጆች መጫወቻውና ፉድ ኮርቱ፣ 5ኛ ፎቅ ላይ የሚሠራው የባህል ማዕከል ጋለሪ እያዘጋጀን ነው፡፡ እነዚህን ከ6-8 ወራት ውስጥ ለመጨረስ እየሰራን ነው፡፡ የልጆች መጫወቻዎቹንና የሲኒማ ቤቶቹን ዕቃ ለመግዛት ጨረታ ወጥቷል፡፡ ወጪው ቀላል አይደለም፡፡ ምን ያህል እንደፈጀ የሚታወቀው እነዚህ ሥራዎች ሲጠናቀቁ ነው፡፡
ዘፍመሽ በሞሉ ውስጥ የራሱ ሱቆች አሉት?
ሱቆቹ በሙሉ ለነጋዴ የተከራዩ ናቸው፡፡ እኛ ሱቅ የለንም፡፡ ሲኒማ ቤቶቹ፣ የልጆች መጫወቻውና ሬስቶራንቶቹ ከፍተኛ ወጪ ስለሚጠይቁ እኛው እንመራቸዋለን፡፡
የዘፍመሽ የስኬት ምስጢር ምንድነው?
ጠንክሮ መሥራትና ለችግር ያለመሸነፍ ነው። ቤተሰቡ በሙሉ ኃይለኛ ሥራ ወዳድ ነው፡፡ ባለቤቶቹ ራሳቸው ይሰራሉ፡፡ ሌላው ደግሞ ቅንነትና ኅብረተሰቡ ምን ይፈልጋል? ብሎ በማጥናት በቀላል ዋጋ ሰው የሚፈልገውን ማቅረብ ነው፡፡ በጣም ሳይደክም የከበረ ባለሀብት ካለ ገንዘቡን ያገኘው በሌላ መንገድ ነው ማለት ነው፡፡ የዘፍመሽ የስኬት ምስጢር፣ ትጋት፣ ቁርጠኝነትና የገበያ ሁኔታን አጥንቶ ማቅረብ ናቸው፡፡
ለምን ያህል ሠራተኞች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል?
የተጀመሩት ሥራዎች በሙሉ ሲጠናቀቁ፣ 280 ያህል ሠራተኞች ይኖሩናል፡፡ አሁን ከ75-80 ሠራተኞች አሉን፡፡

 

 

Read 5920 times