Print this page
Saturday, 31 August 2013 12:04

ሴቶች ለምን አይቀድሱም?

Written by  በካሌብ ንጉሤ
Rate this item
(12 votes)

የወር አበባ የርኩሰት ምልክት ነው?

መጽሐፍ ቅዱስም ሆነ ቅዱስ ቁርዓን እንደሚነግሩን (ሳይንሱ የሚለውን እናቆየውና) የመጀመሪያው ሰው አዳም ነው፡፡ አዳም ብቻውን መኖር ስለማይችል፤ ስላልቻለም ሄዋን ተፈጠረችለት፤ ይኸ ማለት ወንድ ብቻውን ምሉዕ ሰው ሆኖ በተድላና ደስታ ህይወቱን መግፋት ስለማይችል የህይወቱ ሁነኛ አጋር ታስፈልገዋለች ማለት ነው፡፡ 

ፈጣሪ “ብዙ፤ ተባዙ፤ ምድርን ሙሏት” አለ እንጂ፤ አዳም ብቻውን ምድርን እንዲሞላት አልተፈቀደለትም፡፡ ለነገሩማ “ጽድቁ ቀርቶ በወጉ በኮነነኝ” እንደሚባለው ምድርን መሙላቱ ቀርቶ ራሱን ችሎ መኖር ስላቃተው ይመስለኛል ፈጣሪ ሴትን ለአዳም የፈጠረለት፡፡
የጽሑፌ ዓላማ ነገረ ሃይማኖት ላይ ያተኮረ ስለሆነ አንባቢያን እንዲገነዘቡልኝ የምሻውም በዚያው መሠረተ ሃሳብና ግልብጣዊ አተረጓጉሙን ነው። “ግልብጣዊ” ያልሁት የፈጣሪን ትዕዛዝ በአግባቡ አለመተግበር፤ ወይም ያላዘዘውን የእሱ ቃል አስመስሎ የመተርጐም አባዜ ያለ ስለሚመስለኝ ነው፡፡
ፈጣሪ “ብዙ! ተባዙ!”...ሲል “ተፈጥሮአዊ ግንኙነት ፈጽማችሁ ዘራችሁን አብዙ” ማለቱ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ለመውለድ፣ ለመባዛት ደግሞ ሁለት መሠረታዊ ጉዳዮች ያስፈልጋሉ፡፡
አንደኛው የሴቷ ቅድመ ማረጫ ጊዜ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በወንዱ በኩል ያለው አካላዊ ብቃትና ጤናማነት ናቸው፡፡ ከሁለቱ አንዱ ከጐደለ ዘርን ማብዛት አይቻልም፡፡
ነገር ግን ሙሴ እስራኤላውያኑን ከግብጽ ምድር መርቶ ሲና በረሃ ካደረሳቸው በኋላ የተለያዩ ሕግጋትን ማውጣት ጀመረ፡፡ ከሕግጋቱ መካከልም በወር አበባ ጊዜ ያለች ሴት ርኩስ መሆኗን፣ እሷ ብቻ ሳትሆን የተኛችበት አልጋ፣ የነካችው ዕቃ ሁሉ የረከሰ መሆኑን፣ እንዲሁም በወር አበባ ጊዜ ያለችውን ሴት የተገናኛት ወንድ ሁሉ ርኩስ መሆኑን የደነገገበት ሥርዓት ይጠቀሳል፡፡
ከእሱ በኋላ የተነሱ የሃይማኖት ተቋማትና መሪዎችም ይህንኑ መርህ እየቀባበሉ ተግባራዊ ሲያደርጉት ቆይተዋል፡፡ የዕምነት ተቋማት ብቻ ሳይሆኑ በባህላዊ ሥርዓት የሚመሩ አንዳንድ የዓለማችን ህዝቦች ዘንድም ሴት በምትወልድበትም ሆነ የወር አበባ ጊዜዋ ሲደርስ ከቤቷ እንደምትገለል አንዳንድ ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡
ዛሬም ሴት ቤተክርስቲያን ቆማ ማስቀደስ ብትችልም መቀደስ ግን አይፈቀድላትም፡፡ ይህም ሐዋርያው ጳውሎስ “ሴት ትማር እንጂ በአደባባይ አታስተምር” ሲል ከሰጠው አስተምህሮ የተነሳ ይመስላል፡፡ ምክንያቱም የእነ ጳውሎስ መሠረት ኦሪት ነው፡፡ የወር አበባም “በሄዋን ስህተት ምክንያት የመጣ የመርገም ውጤት ነው” ብለው ያምናሉ፤ ይሰብካሉ፡፡
ዛሬም አንዳንድ ገዳማት ለሴቶች ጉብኝት እንኳ ፍጹም ክልክል ናቸው፡፡ ግን ለምን? ጥያቄዬ ከዚህ ነው የሚጀምረው፡፡ ሙሴ “በወር አበባ ላይ ያለች ሴት የረከሰች ናት…” ሲል ቃሉ ከፈጣሪ ሥልጣንና ጥበብ ጋር የሚጋጭ ይመስለኛል፡፡
ምክንያቱም፤ የወር አበባ ልክ እንደ ዛፉ፣ እንስሳቱ፣ ሰው፣ አራዊቱ ሁሉ የፈጣሪ ሥራ ነው። በመሠረቱ ዛፍ ካላበበ አያፈራም፡፡ እርግጥ ነው በሥራቸው የማያፈሩ ልዩ ተፈጥሮ ያላቸው ተክሎችና የሰብል ዓይነቶች አሉ፡፡ ሰውና እንስሳት ግን የዚያ ዓይነት ተፈጥሮ የላቸውም፡፡
ሴቶች ልክ እንደ ጽጌረዳ፣ ቡና፣ ማንጐ ወዘተ ዘር ሊሰጡ ካስፈለገ ማበብ አለባቸው፡፡ አበባቸው ቆመ ማለት ጠወለጉ ማለት ነው፡፡ ጠወለጉ ስል ከወር አበባቸው ፍጹም መቋረጥ በኋላ ዘር አይሰጡም ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ሴቶች በወር አበባቸው ወቅት የረከሱ ከሆኑ ተስገብግበን የምንቀጥፋቸው፣ ወይም ለምንወደው የምናበረክታቸው አበባዎች ሁሉ ርኩሳን ናቸው ማለት ነው፡፡
በመሆኑም የወር አበባ የርኩሰት ምልክት ሊሆን አይችልም፡፡ በመሠረቱ ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደው ከሴት እንጂ ከወንድ አይደለም፡፡ የወር አበባ የምታየው ሴት የረከሰች ብትሆን ኖሮ ለምን ከ”ቅዱሱ” ወንድ አይወለድም ነበር? ወይም የመለኮቱን ተአምር ለማሳየት ሲል ከድንጋይ፣ ከዛፍ፣ ወይም ከእንስሳት ወዘተ ከአንዱ መወለድ የሚያቅተው አይመስለኝም። ሴት ከወንድ ይልቅ ቅድስትና ለመውለድ ከፈጣሪ የታደለች በመሆኗ ነው፡፡
አይሁድ አንዲት ጋለሞታ አምጥተው “ስትገለሙት” ወይም “ስታመነዝር ተገኝታለችና በድንጋይ ተወግራ ትሙት” ብለው ከኢየሱስ ፊት አቀረቧት፡፡ እሱ ግን “አዎ ትዕዛዜን ጥሳ ስታመነዝር ከተገኘች በድንጋይ ውገሯት” ከማለት ይልቅ “ከእናንተ ንፁህ የሆነው ይውገራት” አለና አሳፈራቸው፡፡ ከእሷ ጋር ነፍሳቸውን ሲያጡ እያደሩ ቀን “አመንዝራለች” ያሏት አይሁድም በሃፍረት ተሸማቀቁ፡፡
የኢየሱስን ትንሣኤ ቀድመው የተረዱትም ቅዱሳት አንስት እንጂ ሲከተሉት የኖሩት ሐዋርያት አይደሉም። ያ ቦታ ምንአልባት እኛ አገር ቢሆን ኖሮ “ሴቶች እንዲገቡ አይፈቀድም” መባሉ የሚቀር አይመስለኝም።
ዓለምን ያስጨነቁ ነገሥታትን፣ ደጋግ ጳጳሳትን፣ ቀሳውስትን፣ ምስኪን አርሶአደሮችን፤ ከሁሉም በላይ በፈጣሪም በሰውም ዘንድ ትልቅ ክብር ያገኙ ቅዱሳንን የወለደች ሴት እንጂ ወንድ አይደለም፡፡ ታዲያ የቅዱሳን እናት ለምንድን ነው ቤተ መቅደስ ገብታ የማትቀድሰው? አምጣ የወለደችው ቄስ፤ ለምን ከእሷ የተሻለ ክብር አግኝቶ በእሷ ላይ ሰለጠነ? መልሱ “ጉልበት ስላለው” የሚል ይመስለኛል፡፡
ያ ባይሆን ኖሮ ክርስቶስ ሰምራ ለዘመናት ስትጸልይባቸው በኖሩት ገዳማት ሴት እንዳትገባ አይከለከልም ነበር፡፡ ለነገሩማ እነሙሴ ዛሬ ቢኖሩ ኖሮ ያንን ህግ ሊያወጡ አይችሉም ነበር። ጳውሎስም የቅኔዋን ሊቅ ወ/ሮ ገላነሽ ሐዲስንና ሌሎችን ሊቃውንት ቢያይ ኖሮ “የሚሠሩትን አያውቁምና ይቅር…” ማለቱ አይቀርም ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡
ሌላው ቀርቶ ሴቶቹ ራሳቸው ተቀብለውት፣ ራሳቸውን እንደ በደለኛ አይተውት፣ ጉዳዩን “አዎ በበደላችን ምክንያት የመጣብን ስለሆነ ይቅር ይበለን” በሚል ስሜት ራሳቸውን ከቤተክርስቲያንም ሆነ ከጠበልና ከሌሎች ቦታዎች ሲያገልሉ ማየት የተለመደ ሆኗል፡፡ ለነገሩ ጉዳዩ አያሌ ዘመናትን ያስቆጠረ ስለሆነ እንዲህ ማድረጋቸው ላያስደንቅ ይችላል፡፡
በበርካታ የኦርቶዶክስና የካቶሊክ አብያተ ክርስቲያናት ቅድስት ድንግል ማርያም፣ በእንግሊዝ ቅድስት ማርጋሬት፣ በሀገራችንም ማርያምን ጨምሮ ቅድስት ክርስቶስ ሰምራ፣ ቅድስት አርሴማ፣ እና በርካታ ሴት ጻድቃንና ሰማዕታት ቤተክርስቲያን በስማቸው ተሰርቶላቸው በወጉ ይከበራሉ፡፡
ክርስቶስ ሰምራን የመሳሰሉት እንዲያውም ትዳር መስርተው ልጅ የወለዱ ቅዱሳት ናቸው፡፡ እናም የወር አበባቸው አላረከሳቸውም፡፡ ለነገሩማ ዛሬ በአሜሪካ ለግብረ ሰዶማውያን ሳይቀር ግብረ ሰዶማዊ ጳጳስ ተሹሞ የካቶሊክን እምነት እየሰበከ ነው፡፡
ከዚህ የባሰ ርካሽ ነገር ምን አለ? ሆኖም ልብ ሊባል የምሻው ቁም ነገር፣ አሜሪካ ውስጥ ግብረሰዶማዊ ጳጳስ ስለተሾመ እኛም በዚህ አይነቱ የዘቀጠ ጉዳይ እንዘፈቅ ማለቴ አይደለም፡፡ ግን ሴቶች እና ያለባቸው ሰው ሰራሽ ጣጣ ሁልጊዜም ስለሚገርመኝ ነው ይህችን አጭር አስተያየት ለመጻፍ የተነሳሳሁት፤ እስኪ እንወያይበት?!

Read 8593 times