Saturday, 24 August 2013 11:38

እኛና ስብሃት (የሞተው ማነው?)

Written by  ሌሊሳ
Rate this item
(10 votes)

… በጫጫታው መሀል ዝም ማለት … አድማጭ ያደርጋል፡፡ የሚደመጥ ነገር ሳይኖር ዝም የሚል ግን በህይወት አለመኖሩን እንዳረጋገጠልን ይቆጠራል። ህይወት እንዳልሞተች የምናረጋግጠው ህያው ነኝ ባይ ሲገልፃት ነው፡፡ የሞተው ሰውዬ ስብሐት ገ/እግዚአብሔር መሆኑኑ ተማምነን ቀብረነው ነበር። አሁንም ግን መግለፁን ቀጥሏል፡፡ … አልሞተም ማለት ነው፡፡ ወይ እኛ ሞተናል፡፡
ስብሐት ሞቶም እያነጋገረን ነው፡፡ አንዳንድ ሙታንን ልንቀብራቸው አንችልም፡፡ አንደፍርም። ሞተው ቢመሩን እንመርጣለን፡፡ በህይወት ያለነው ከእነሱ ጋር አንመጥንማ! እነሱን በማሞገስ አልያም እነሱን በመርገም ብቻ ነው አለመሞታችንን የምናረጋግጠው፡፡ እረፍት ልንሰጣቸው አንችልም። እነሱን ሳንመረኮዝ ምን ላይ እንቆማለን? ከእነሱ መቃብር ጋር የእኛ ትንሳኤ ተሳስሯል፡፡ የኛ የትንንሾቹ ሰዎች፡፡ We stand on the shoulder of giants not to see further … በህይወት መኖራችን ራሱ ስለሚያጠራጥረን ነው፡፡
በጫጫታው መሀል ዝም ማለት አልቻልኩም። … ሚልኪ ባሻ ጀመረው፡፡ ሙታንን ቀስቅሶ ማናገሩን፡፡ ጠርጢዎስ መለሰለት፡፡ ጠርጢዎስ ከቫቲካን … ሁሌ መልስ ነው የሚሰጠው፡፡ መልሱ ላልተጠየቀበት ጥያቄ መሆኑ የለመድነው አባዜው ነው፡፡ … የሆነ ነገርን ሁሌ መመርኮዝ ያስፈልገዋል። “መንጠልጠል” ያለው የአለፈው ሳምንት ፀሀፊ ጠርጢዎስን በተለይ ይገልፀዋል፡፡ … ጠርጢዎስ፡- reacts on Issues before acting towards them … ከዚህ በፊት በሀይማኖት ክርክሮች ላይ አይተነዋል፡፡ በሰው ሀሳብ ላይ ከመመርኮዝ አልፎ … መገንደስ ይወዳል፡፡ “ጥሪዬ ነው” ብሎ ወደሚያምንበት ሀይማኖቱ አቅጣጫ ነው የሚገነደሰው፡፡ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ እንደዛ አይነት ሰው ነው … It takes all kinds!
መጀመሪያ ሰላሳ ሰዎች ሆነን በሰውየው ትከሻ ላይ ወጣን፡፡ ሩቅ ለማየት ወይንም ስብሐትን ለመግለፅ ሳይሆን … ራሳችንን ለመግለፅ ወይንም ለማየት ብለን ነው፡፡ ሰውየው ሞቷል፡፡ እኛ ስናመሰግነውም ሆነ ስንሰድበው አይሰማውም። ስለዚህ፤ ምስጋናውም ሆነ ክብሩ … ጥቅሙም ሆነ ጉዳቱ … ለተንጠለጠልንበት ሀውልት ሳይሆን ለእኛው ነው፡፡
እሺ! … ሰላሳ ሰዎች የተንጠለጠሉበት መፅሐፍ በሰላሳ ሺ ሰዎች (ወይንም በላይ) እየተነበበ ሊሆን ይችላል አሁን፡፡ በሰላሳ ሺ አፎች ስለ መፅሐፉ ይወራል፡፡ የተወራው በሀምሳ እጥፍ ተባዝቶ ይራገባል፡፡ ይሄ ሁሉ ሰው ስለ ስብሐት ሲያወራ፤ የስብሐት መልክ እንደ አነበበው ተመልካች እይታ ብዙ ሆኖ ቢሆን “እሰየው” ነበር፡፡ “ስብሐት የሰውን ሁሉ መልክ ይመስላል፤ ወይንም ስብሐት ህይወትን በሙሉ የሚመስል ገፅታ አለው … ስብሐት ህይወት ነው፤” ብለን እንስማማ ነበር፡፡ አሁን ባልኩት ብዙ ገፅታ መስማማት ማለት፤ ህይው መሆን ማለት ነው፡፡ እኛም ሆነ ስብሐት በእኛ ውስጥ ወይንም አማካኝነት ህያው ሆነ ማለት ነበር፡፡
ለምሳሌ፤ የአጋፋሪ እንደሻሁ (ገፀ ባህሪ) በእርግጠኝነት የጥበብ (ውበት) ልኬት ናቸው፤ ካልን… የህይወትም ልክ ናቸው፡፡ ምክንያቱም ጥበብ ህይወትን አጠቃሎ የሚወክል፣ የሚገልፅ፣ የሚተረጉም ነገር ስለሆነ ነው፡፡ በአጋፋሪ እንደሻው አማካኝነት ራሳችንን ማየት ካቃተን፣ ድርሰቱ ለህይወት፣ ከህይወት … ለህያዋን አይደለም፡፡ በአጋፋሪ እንደሻው ራሳችንን ማየት ቢያቅተን እንኳን … ቢያንስ ስብሐትን እንዳናይ መጠንቀቅ ነበረብን፡፡
“ሀምሌትን ስናይ ሼክስፒርን አየን” ከማለት አይተናነስም፡፡ ያሳዝናል … ያሳፍራል፡፡ ስብሐት ምን ያድርግ … ሌቱም አይነጋልኝ ላይ ስላለው የክንፈ ገፀ ባህሪ? የሌቱም አይነጋልኝ መፅሐፍን በዛሬው እለት ከገበያ ገዝቶ ቤቱ ገብቶ እሚያነብ ሰው ተጠያቂ የሚያደርገው ለንባቡ (አንብቦም ለመፀየፉ) … ያው የፈረደበትን ስብሐት ነው፡፡ ሰውየው እኮ ሞቷል፡፡ … ለኒዩክሊየር ጦር መሳሪያ ስጋት ኤንሪኮ ፈርሚ እና አንስታይን ምን ያድርጉ? … ጦር መሳሪያውን አሁን ያለ ሰው ነው ለክፉም ሆነ ደግ መርጦ የሚጠቀምበት … የቦንቡ መነሻና መድረሻ አሁን ያለ ሰው ራሱ ነው።
በ “ሌቱም አይነጋልኝም” ውስጥ ያለው ገፀ-ባህሪ ሳይሆን አሁን በማንበብ ላይ ያለ ሰው ነው ልክ ወይንም ስህተት፡፡ በሀምሌት ገፀ ባህሪ ውስጥ ሼክስፒርን ይቅርና … ሀምሌትንም ራሱን በማይቀያየር መልክ አናገኘውም፡፡ የኢትዮጵያዊው ሀምሌት ከእንግሊዛዊው ይለያል፡፡ እንደ ተዋናዩ የአተረጓጐም ብቃት … ገፀ ባህሪውን የመረዳት … ወይንም ወደ አካል ቋንቋ ቀይሮ የማቅረብ አቅም፡፡ የስብሐትም ሁኔታ ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡
“If Hamlet has something of the definiteness of a work of art, he has also all the obscurity that belongs to life. There are as many Hamlets as there are melancholies.” (The critic as Artist)
“አምስት ስድስት ሰባት” ላይ ያለው ድህነት … የስብሐት አይደለም፡፡ በፅሁፍ ላይ የሰፈረው ገፀ-ባህሪ የኢትዮጵያዊ ሁሉ ነው፡፡ የገፀ ባህሪውንም፤ ገፅ እና ባህሪ ደራሲው የሚስለው እኮ አንባቢው ልቦና ውስጥ ነው፡፡ … አንባቢ እኮ በፈጠራው ስራ ላይ ከግማሽ በላይ ባለቤት ነው፡፡ ደራሲው የሚፅፈው በሰዎች ልቦና ላይ ነው፡፡ “አምስት ስድስት ሰባት” ላይ ያለው ድህነት የእናንተ ነው፡፡ ስብሐት የሚባል ሰው ከእንግዲህ የለም … እረፉት!” ስብሐት አለ፤ ወንጀለኛ ወይንም ጠንቅ ነው… ብለን ስንወነጅለው እንኑር የምትሉ ከሆነ … እናንተ ናችሁ የሌላችሁት፡፡ የስብሐት ህይወት ላይ የምታነሱት የግብረ ገብ ጥያቄ … መቅረብ ያለበት … ለእናንተ ነው፤ ለእሱ አይደለም። “ቢግ ብራዘር አፍሪካ” ላይ ተደረገ ለተባለው ነውር ተጠያቂው ስብሐት ሊሆን አይችልማ፡፡ እናንተው ናችሁ ተጠያቂ፡፡ ቤቲም ልትጠየቅ አትችልም … ቤቲ ገፀ ባህሪን ተላብሳ ተወነች፡፡ እናንተ ገፀ ባህሪውን ተላብሳችሁ ተመለከታችኋት፡፡ ገፀ ባህሪውን ተላብሳችሁ ስብሐትን እንዲፅፋችሁ ወሰወሳችሁት። እሱ ለመፃፍ የተወሰወሰውን ያህል እናንተ ለማንበብ ተወስውሳችኋል፡፡ በሱ ውስጥ የምታነቡት ራሳችሁን ነዋ!
ስለዚህ ስብሐት ስንት መልክ አለው? ከተባለ … እኔ የምመልሰው “የእናንተን መልክ ብዛት” ብዬ ነው፡፡ ስብሐት ከስንት ብሔር መጣ? እናንተ ከመጣችሁበት የብሔር አማራጭ፡፡ ከስንት ማህፀን? እናንተን ካማጣችሁ የማህፀን ዥንጉርጉርነት … ወዘተ፡፡ ግን ተመልሼ ደግሞ ተጠራጠርኩ … ዥንጉርጉር ቢሆን ኖሮማ አመጣጣችሁ፤ ከሁለት አይነት የዕይታ አማራጭ ውጭ በተመለከታችሁ ነበር፡፡ ስብሐትን ወደ ልቅ ወሲብ አባትነት እና ልቅ የነፃነት ተሟጋች ከፍላችሁ ቁጭ አትሉም ነበር፡፡
… ከሁለት አማራጭ በላይ ያለ ለማስመሰል … በሁለት ድምፅ ደጋግሞ ለመዘመር … በየሳምንቱ ብዕር እና መርዝ እየቀላቀላችሁ የምታጠጡን ለምንድነው? … ብዕር በሽቶም ሆነ በመርዝ ቢሞላ ለስብሐት አይጠቅመውም፡፡ አይጐዳውም፡፡ ጉዳቱም ሆነ ጥቅሙ ለእናንተው ለራሳችሁ ነው፡፡ እንዲያውም ምን ጉዳት አለው? … ጥቅም ብቻ ነው። ግን ጥቅሙ “በስብሐት ላይ ተከራከርኩ!” ለማለት ያህል ብቻ ነው … በስብሐት ላይ ተከራከርኩ … ከሚሉት የበለጠ ደግሞ “አከራከርኳቸው!” የሚሉት የበለጠ ትርፍ ያገኛሉ፡፡ ስብሐት ቢወገዝም ሆነ ቢሞገስ የመፅሐፉ ሽያጭ ከፍ እያለ ይሄዳል፡፡ “ሰላዩ ተያዘ” ወይንም “ሰላዩ አመለጠ” የሚለውን ዜና የሚያትሙ መፅሔቶች በሁለቱም ረገድ ብዙ ኮፒ ይሸጣሉ፡፡ “The spy catcher effect” እያሉ ይጠሩታል፡፡ win win situation…ነው፡፡
እንጂማ፤ ስብሐትን የሚከተሉ ሰዎች በህገ መንግስቱ የህግ ከለላ አይነፈጋቸውም፡፡ በቤተ ክርስቲያኑም ፍትሀት አይከለክላቸውም፡፡ የስነ ምግባር አስተሳሰባችን ከመሰረቱ በተነቃነቀበት የወቅቱ ትውልድ ላይ … ደራሲውን በስነ ምግባር ለመክሰስ መሞከር … ከራስ ጋር ፍልሚያ ውስጥ መግባት ነው፡፡
በራችንን ለውጭው አለም ተፅኖዎች ከፍተን፣ ግን ዘግተን ለመቀመጥ የምንሞክረው በር፤ ምንም አይነት የስነ-ልቦና መሀንዲስ (ለበሩ) ማጠፊያ… ለክርክራችሁ ደግሞ ማጣፊያ መፍትሔ ሊሰጣችሁ አይችልም፡፡ ስብሐት … በመስታወት የማይታየውን ማንነታችንን አውጥቶ … አሳየን፡፡ በተፈጥሮአዊነት የአፃፃፍ ዘዴ ተጨባጩን ሲያሳየን ወነጀልነው፡፡ … ተፈጥሮአዊነትን ትቶ የሀያ አንደኛውን ክፍለ ዘመን የአፃፃፍ ዘይቤዎች … ሱሪያሊዝምም … ሆነ ፋንተሲ … መጻፍ ሲጀምርም ወነጀልነው፡፡ በተፈጥሮአዊነት ተፈጥሮአችንን ስላሳየን ወነጀልነው፡፡ በምናባዊ የአፃፃፍ ዘይቤ ተፈጥሮአችንን “ሮማንቲሳይዝ” አድርጐ ሳያሳየን ሲቀርም ወንጀል ሆነ፡፡ “The nineteenth century dislike of Realism is the rage of caliban seeing his own face in the glass. The nineteenth century dislike of Romanticism is the rage of caliban not seeing his own face in a glass” (The Picture of DNIAN GRAY) ለምን ታሳየናለህ? … እና ለምን አላሳየኸንም? የሚለውን ግራ የተጋባ ጥያቄ መመለስ የሚችለው … ምን ማየት እና አለማየት እንደሚፈልግ የሚያውቅ ሰው ብቻ ነው፡፡ ይህንን መምረጥ የሚችል ሰው ደግሞ ራሱ ደራሲ ነው። ተራ አንባቢ የተሰጠውን መቀበል የተጣለበት ፍርጃ ነው፡፡ ተቀብሎ ሲያበቃ “አልቀበልም” የሚል ድንፋታ የትም አያደርስም … ጋዜጣ ላይ ስምን አትሞ ከማስነበብ በሚገኝ “በህይወት አለሁ ለካ!” የጉራ ባዶነት ውስጥ ከመሳከር በስተቀር፡፡

Read 5086 times