Saturday, 24 August 2013 10:47

“የችግሩ ትልቁ ምንጭ ያለው አገር ቤት ነው”

Written by  ኤልሳቤት እቁባይ
Rate this item
(2 votes)

ባለፈው ሀምሌ ወር በሳኡዲ አረቢያ በቤት ሰራተኛነት ተቀጥረው የሚሰሩ ሶስት ኢትዮጵያውያን በግድያ ወንጀልና የግድያ ሙከራ ፈፅመዋል በሚል ተወንጅለዋል፡፡
ይሄንን ተከትሎም አንድ የሳኡዲ ባለስልጣን፤ ኢትዮጵያውያን የቤት ሰራተኞች ወደ አገራቸው እንዳይመጡ መወሰኑን ተናግረዋል፡፡ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ለሥራ የሚጓዙ ኢትዮጵያውያን ከአገራቸው መንግስት የሚደረግላቸው ጥበቃና ከለላ ስለመኖሩ፣ በየአገራቱ የሚገኙ ኤምባሲዎችና ቆንስላ ፅ/ቤቶች በዚህ ረገድ ምን ተግባራትን እንደሚያከናውኑና የሳኡዲውን ጉዳይ በተመለከተ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ ከኢትዮጵያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ጋር አጭር ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡

በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት በችግር ላይ ለሚገኙ ኢትዮጵያውያን ምን እየተደረገ ነው?
በህገ ወጥ መንገድ የሚሄዱት ላይ የእውቀት ችግር አለ፡፡ የሚሄዱበትን አገር ቋንቋ፣ ስነልቦና፣ በአጠቃላይ ያለውን ነገር ሳያውቁ የሚሄዱ ይበዛሉ፡፡ በስደት ላይ ያሉ ዜጎችን የማስመለስ ስራ እየተሰራ ነው፡፡ ቢሆንም ማነቆዎች አሉ፡፡ ስራው እየተሰራ ያለው በተለያዩ ሀይሎች ነው፡፡ ፖሊስ፣ ኢሚግሬሽን፣ ዓለምአቀፍ የስደተኞች ጉዳይ ድርጅት (አይኦኤም) ፣ ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ፣ ሰራተኛና ማህበራዊ፣ በውጪ ያሉ የኢትዮጵያ ቆንስላ ፅህፈት ቤቶችና ሌሎችም በየፊናቸው ይሰራሉ፡፡ ችግሩ ግን እጅግ የተወሳሰበ ነው፡፡
ወደ መካከለኛው ምስራቅ በህገወጥና በህጋዊ መንገድ በሚሄዱት መካከል ያለው ልዩነት የአካሄድ ነው እንጂ የሚገጥማቸው ችግር ተመሳሳይ ነው ይባላል...
ትክክል ነው፡፡ በህገወጥ ተሄደ በህጋዊ መንገድ ችግሩ ተመሳሳይ ነው፡፡ በሚሄዱበት አገር ማህበራዊ ዋስትና አላቸው ወይ? የጤና ኢንሹራንስ እና ሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮችም ምላሽ ይፈልጋሉ፡፡ ችግር ሲደርስባቸው የሚያመለክቱበት መንገድ አለ ወይ? ወደ አገራቸው መመለስ ቢፈልጉ መመለስ የሚችሉበት መንገድ አለ? ወዘተ-- የሚሉት መፈተሽ አለባቸው፡፡ ከሌሎቸ የእስያ አገራት ለተመሳሳይ ስራ ወደ አረብ አገራት የሚሄዱ ሰዎቸ ለሚሰማሩበት ሥራ ስራ ስልጠና ይወስዳሉ፡፡ በኛ በኩል ይህ የለም፡፡ በህጋዊ መንገድ ቢኬድም የሚሰራው ስራ ህጋዊ ነው ወይ የሚለው አጠያያቂ ነው፡፡ የሚጠብቃቸው አቀባበልም መታየት አለበት፡፡
ኢትዮጵያ በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት በቂ እና የተሟሉ ኤምባሲዎች አላት ማለት ይቻላል?
በውጪ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የሚሰራው ስራ አደጋ ከደረሰ በኋላ እሳት የማጥፋት ሰራ ነው፡፡ በመካከለኛው ምስራቅ ኤምባሲዎች ያሉን በተወሰኑ ቦታዎች ነው፡፡ የሰው ሀይል እና የገንዘብ ብቃታቸው ከችግሩ ጋር ተመጣጣኝ ነው ወይ የሚለው እየታየ ነው፡፡ በአንዳንድ አካባቢዎች ብዙ ኢትዮጵያውያን በመጠለያ ውስጥ ናቸው፡፡ እነዚህን ዜጎች ተመላልሶ መጠየቅ፣ ፍርድቤት ጉዳይ ያለባቸውን የህግ ድጋፍ መስጠት፣ የካሳ ጥያቄ ለሚያነሱ የህግ ምክር መስጠት የመሳሰሉትን በዝርዝር አይቶ የማስፈፀም አቅም ላይ ችግር አለ፡፡
ኤምባሲዎቹ ወይም ቆንስላ ፅህፈት ቤቶቹ በመካከለኛው ምሥራቅ ተቀጥረው የሚሰሩ ኢትዮጵያውያንን ያውቋቸዋል?
ከአገር ቤት ከወጡ በኋላ በኤምባሲዎቹ የመመዝገብ ባህል በጣም አነስተኛ ነው፡፡ መመዝገብ እንዳለባቸው ግን መረጃ አላቸው፡፡ በህጋዊ መንገድ የሚጓዙትም በሰራተኛና ማህበራዊ ሚኒስቴር በኩል ተዋውለው ቪዛቸውን ካገኙ በኋላ ይሄዳሉ እንጂ ኤምባሲዎቹና ቆንስላ ፅህፈት ቤቶቹ መረጃ የላቸውም፡፡ ከሰራተኛና ማህበራዊ ሚኒስቴር ጋር ያለው ቅንጅትም እጅግ የላላ ነው፡፡ አሁን እየተጀመሩ ያሉ ስራዎች አሉ፡፡ ነገር ግን ከችግሩ ስፋት ጋር ሲነፃፀር በቂ አይደለም፡፡ ሌላው ከዚህ በቤት ሰራተኛነት የሚሄዱት እንኳንስ ከኤምባሲ ጋር ሊገናኙ ከማህበረሰባቸው ጋር እንኳን እንዲገናኙ አይፈቀድላቸውም፡፡ በተቀባይ አገሮች በኩል ሰራተኞቹ እንዲህ አይነት ግንኙነት እንዲፈጥሩ አይበረታቱም፡፡ በአካል አግኝቶ ችግራቸውን ለማወቅ ይቅርና በስልክም ማግኘት አስቸጋሪ ነው፡፡
ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ይህን ችግር ለመፍታት ምንድነው የሚያደርገው ?
እንግዲህ ከላይ የተጠቀሱት ችግሮችና የተቀባይ አገሮች ህግ ተደምረው ለጉዳዩ አፈጣኝ እልባት እንዳይሰጠው አስተዋፅኦ ያደርጋሉ፡፡ በውጪ ጉዳይ ሚሲዮኖች ወደ እዚህ የሚገባው ቅድም እንዳልኩት አደጋ ከደረሰ በኋላ ነው፡፡ የችግሩ ትልቁ ምንጭ ያለው አገር ቤት ነው፡፡ ትልቁ መፍትሄ መሰጠት ያለበት አገር ቤት ነው፡፡ የሚሄዱት ወገኖች አውቀውና ሰልጥነው እንዲሄዱ ማድረግ፤ ወደዚያ እንዳይሄዱ ስራን መፍጠር እና መልካም አስተዳደርን ማጠናከር ያስፈልጋል፡፡
የሰሞኑ የሳኡዲ ሁኔታስ እንዴት ይታያል?
የህገወጥ ዝውውር ምንጭ፣ መተላለፊያና ተቀባይ አገሮች አሉ፡፡ እዚህ ላይ ሶስቱም ወገኖች ተቀራርበው መስራት አለባቸው፡፡ የውጪ ጉዳይ አንዱ ድርሻም ይሄ ነው፡፡ የሳኡዲውን ሁኔታ በተመለከተ እንደዚህ ዓይነቶቹ ውንጀላዎች በየጊዜው ይቀርባሉ፡፡
ሰሞኑን ግን ጨምረዋል፡፡ እንዲያውም አንድ የአገሪቱ ባለስልጣን የቤት ሰራተኞች ከኢትዮጵያ መምጣት የለባቸውም ብለዋል---
ይህን ውንጀላ ማጣራቱ አስቸጋሪ ቢሆንም በጥቅሉ እነዚህ ሰዎች የሚሰሩት ስራ እጅግ አስከፊ ነው፡፡ የስሜት መናወጥ አለ፡፡ አንዳንዴ የተሰጣቸውን ስራም አያውቁትም፡፡ ዘመናዊ እና የረቀቁ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ለመጠቀም ልምዱ የላቸውም፡፡ በዚህ ምክንያት በራሳቸው እና በተቀጠሩበት ቤት የቤተሰብ አባላት ላይ ጉዳት ሊያደርሱ ይችላሉ፡፡
በሀምሌ ወር ብቻ ሶስት ኢትዮጵያውያን የቤት ሰራተኞች የግድያ እና የግድያ ሙከራ አድርገዋል በሚል ተወንጅለዋል፡፡ በውጪ ጉዳይ በኩል ምን እየተደረገ ነው?
ውጪ ጉዳይ ዜጎችን መታደግ በሚል ማእቀፉ፣ የህግ የምክር አገልግሎት የሚሰጥበት፤ ጉዳያቸው ፍርድ ቤት ከቀረበ በትክክል ሊዳኝ የሚችልበትን ሁኔታ መከታተል፣ ጠበቃ ቀጥሮ መሟገት እንዳለበት ያስቀምጣል፡፡ ለዚህ ሁሉ አቅም አለ ወይ? ከተባለ የለም ፤ እጥረት አለ። ነገር ግን ተቋሙ ግዴታ አለበት፡፡ አንዳንድ ሚሲዮኖች ያደርጋሉ፤ አንዳንዶች አያደርጉም፡፡ ለምሳሌ በፑንትላንድ የሰው ህይወት አጥፍቶ የነበረን ኢትዮጵያዊ ጉዳይ ሚሲዮናችን ከአገሪቱ መንግስት ጋር ባደረገው ውይይት የተጠየቀውን ካሳ አንድ ግለሰብ ከፍሎለት ነፃ ወጥቷል፡፡
በቅርቡ ከሳኡዲ የተሰማው “ልጅ ገደለች፤ በሻተር አነቀች” የሚለው ውንጀላ የት እንደደረሰ ባላውቅም፤ ሰሞኑን በመካከለኛው ምስራቅ የሚገኙ የኛ ሚሲዮን ሀላፊዎች አዲስ አበባ ስብሰባ አድርገዋል፡፡ ምን ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው በስፋት ተወያይተዋል፡፡ ደካማ የቆንስላ እንቅስቃሴ ባለባቸው ፅህፈት ቤቶች ላይ ጠንከር ያለ ዜጎችን የመደገፍ ስራ እንዲሰራ አስፈላጊውን የሰው ሀይል ማሟላት እና የገንዘብ አቅምን ማጠናከር፤ ከአገሩ መንግስት ጋር እንደ አስፈላጊነቱ በጉዳዩ ላይ መወያየት እና በየአካባቢው ከሚገኙ የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ጋር መወያያት የሚሉት በመፍትሄ ተቀምጠዋል፡፡ አንዳንድ አካባቢዎች አስከሬን መጫኛ እንኳን የሚጠፋበት አጋጣሚ አለ፡፡ ለዚህ ደግሞ ከመንግስት የተመደበ በጀት የለም፡፡
የኢትዮጵያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር በተለይ ከመካካለኛው ምስራቅ አገሮች ጋር በተያያዘ ለዜጎች ግድ የለውም፤ የሳኡዲን የስራ ስምምነት የወሰደው አንዳንድ አገሮች በዜጎቻቸው ላይ በሚደርሰው እንግልት ሳቢያ ስምምነቱን በማቋረጣቸው እንደሆነ ይነገራል፡፡ በዚህ ላይ የመስሪያ ቤቱ ምላሽ ምንድን ነው?
ከመካካለኛው ምስራቅ አገሮች ጋር ያለን ስምምነት የሌበር ስምምነት ነው፡፡ እስከአሁን ሲሰራበት የነበረው አሰራር ለሁለቱም ወገኖች ከሚሰጠው ጥቅም አንፃር ታይቶ ነው፡፡ እነሱ ሰራተኛ ይፈልጋሉ፤ እኛ ደግሞ ሰራተኛ አመንጪ አገር ነን፡፡ የሳኡዲንም የተፈራረምነው በአለም አቀፍ ህጎች እና በሌሎቸ ተዛማጅ ህጎች መብታቸው እንዲጠበቅ ይደረጋል በሚል ነው፡፡
በመንግስት በኩል የስራ ጉዞውን ለማስቆም እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው የሚባለው እውነት ነው?
መንግስት ገብቶበት ስርአት ማስያዙ ተገቢ ነው፡፡ ለስራ የሚደረግ ዝውውር ግን አለም አቀፍ ክስተት ነው፡፡ መንግስት ያንን ማስቆም አይችልም፡፡ ለዜጎች ጥበቃ ሲባል ለጉዞ የተዘጉ አንዳንድ አገራት ግን አሉ፡፡
የሳኡዲንስ ጉዳይ በተመለከተ?
በቅርቡ የሳኡዲ መንግስት አወጣው ከተባለውና ከላይ ከተጠቀሰው ውጪ ሁለታችን ቁጭ ብለን አልተነጋገርንም፡፡ ቀጣዩን መከታተል ነው የሚሻለው፡፡

Read 2613 times