Saturday, 24 August 2013 10:20

ኖርዌይ ኤምባሲ እና ኢ/ር ኃይሉ እየተወዛገቡ ነው

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(4 votes)

“ያከራየኋቸውን ቤት ለመልቀቅ እምቢተኛ ስለሆኑ ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አሳውቄያለሁ”
- ኢ/ር ኃይሉ

ኖርዌይ ኤምባሲ ከኢ/ር ኃይሉ ሻውል የተከራየውን ባለ ሁለት ፎቅ የመኖሪያ ህንፃ ለ15 አመታት ሲጠቀምበት እንደቆየ የገለፁት የአዲስ አድማስ ምንጮች፣ በሁለቱ ወገኖች መካከል ውዝግብ የተፈጠረው ቤቱን ልቀቅ፣ አልለቅም በሚል ነው ብለዋል፡፡ በ97 ምርጫ የምርጫ ዘመቻ ቅንጅትን በፕሬዚዳንትነት የመሩት ኢ/ር ኃይሉ ሻውል፣ ከኤምባሲው ጋር በነበራቸው የኪራይ ውል መሰረት ከ7 ወራት በፊት ቤቱን እንዲያስረክባቸው እንደጠየቁ ተናግረዋል፡፡ በ3200 ካሬ ሜትር ግቢ ውስጥ የተሰራው ባለ ሁለት ፎቅ መኖሪያ ህንፃ በ1200 ካሬ ሜትር ላይ ያረፈ ነው፡፡
ቤቱን ስለምንፈልገው ልቀቁልን በማለት ከሰባት ወራት በፊት በደብዳቤ ብንጠይቅም፤ ኤምባሲው ለመልቀቅ ፈቃደኛ አልሆነም የሚሉት ኢ/ር ሃይሉ፣ ከአንድ አመት በፊትም ኤምባሲው ቤቱን እለቃለሁ ቢልም ፈቃደኛ ሳይሆን ቀርቷል ብለዋል፡፡ “ቤቱን በትክክል ከፈለጋችሁት ግዙን” በማለት ለኤምባሲው አማራጭ አቅርበው ተቀባይነት እንዳላገኘም ጨምረው ገልፀዋል፡፡
ጉዳዩን ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ማሳወቃቸውን ኢ/ር ኃይሉ ጠቅሰው፣ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱም ኤምባሲው ቤቱን እንዲለቅ ጥያቄ አስተላልፏል ብለዋል፡፡
“ህግና ስርዓትን ተከትዬ ቤቱን እንዲለቁ በትዕግስት ጠብቄያለሁ፡፡ እምቢ ካሉ በግል ንብረቴ ከእነርሱ ጋር እንካ ሰላንቲያ አልገጥምም” ያሉት ኢ/ሩ፤ ጥቁርን በመናቅና በማን አለብኝነት የሚካሄደውን ህገወጥነት ፈፅሞ አልቀበልም ብለዋል፡፡ ኤምባሲው የያዘብኝ ቤት ከመኖሪያ ቤቴ ጋር በአጥር ስለሚገናኝ በቤቴ በኩል አፍርሼ በመግባት ግቢውን ለማስተካከል ወስኛለሁ ብለዋል ኢ/ር ኃይሉ፡፡ ወደ ኤምባሲው በተደጋጋሚ ደውለን ጉዳዩ የሚመለከታቸውን ምክትል አምባሳደሯን ለማነጋገር ብንሞክርም “አሁን ቴሌ ኮንፈረንስ ላይ ነኝ፤ ማናገር አልችልም” የሚል ምላሽ በፀሀፊያቸው በኩል ተናግረው፤ መረጃ ለመስጠት ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል፡፡
ስለዚሁ ጉዳይ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት ወደ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ፕሮቶኮል ክፍል ደውለን ጉዳዩ የሚመለከታቸውን ሀላፊ ለማግኘት ሙከራ ብናደርግም ለስብሰባ ከግቢ ውጭ ናቸው በሚል ምላሽ ልናናግራቸው አልቻልንም፡፡

Read 26657 times