የግእዝ ቋንቋ እንዲያንሰራራ ያለመ ኪነጥበባዊ ዝግጅት ነገ ማምሻውን በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ በኮሌጁ የምግብ አዳራሽ የሚቀርቡትን ድራማ፣የጥንታዊ ፅሁፎች ንባብ ፣ቅኔ፣ የግዕዝ ግሰሳ (ትንተና) ፣ጭውውትና ዜናን በግእዝ የኮሌጁ የግእዝ ቋንቋ ተማሪዎች እና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች በህብረት እንደሚያዘጋጁት የጠቀሰው የአዘጋጆቹ መግለጫ፤ ለግእዝ ቋንቋ እና ለኢትዮጵያ የቀድሞ ስልጣኔ አክብሮት ያላቸው ወገኖች ሁሉ በነፃ ዝግጅቱን መከታተል እንደሚችሉ አብስሯል፡፡ የኮሌጁ የግእዝ ክፍለ ትምሕርት ኃላፊ መምህር ዘርአዳዊት አድሓና ስለጉዳዩ ማብራሪያ ጠይቀናቸው፤ ኮሌጁ ከ2002 ዓ.ም ጀምሮ ቋንቋውን በዲፕሎማ ደረጃ እያስተማረ መሆኑን ገልፀው “በየዓመቱ ደብረ ታቦር ሲከበር ክርስቶስ ለተማሪዎች ምስጢር መግለጡን አስታውሰን ከአብነት ትምህርት ቤቶችን በወረስነው ትውፊት ከበዓለ ደብረታቦር ጋር እናከብረዋለን” ብለዋል፡፡