በሶስት ቋንቋዎች የፓርቲው ልሳኖች ይዘጋጃሉ
አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ የራሱን ማተሚያ ቤት ለመክፈት ባለፉት ሶስት ወራት በአገር ውስጥና በውጭ ባከናወነው የገቢ ማሰባሰቢያ ጥረት በቂ ገንዘብ ማግኘቱን በመግለጽ የማተሚያ ማሽን የግዢ ጨረታ አወጣ።
በፓርቲው ሲዘጋጅ የነበረው “ፍኖተ ነፃነት” ጋዜጣ በማተሚያ ቤት እጦት እንደተቋረጠ የገለፁት የፓርቲው አመራር አባል፣ ማተሚያ ማሽን ተገዝቶ ስራ ሲጀምር “ፍኖተ ነፃነት”ም ለአንባቢያን ትደርሳለች ብለዋል፡፡ ከጋዜጣው በተጨማሪ በትግርኛና በኦሮሚኛ ቋንቋዎች የሚዘጋጁ ጋዜጦችና ሌሎች ህትመቶችንም እንደሚሰራ ፓርቲው ጠቅሶ፣ ፓርቲዎች በንግድ ስራ ውስጥ መግባት ስለማይችሉ ለግል ጋዜጦች የህትመት አገልግሎት አንሰጥም ብሏል። የሀገር ውስጥ አቅራቢዎች በጋዜጣ ላይ በወጣ የጨረታ ማስታወቂያ በቀረበው ዝርዝር መረጃ መሠረት መሳተፍ እንደሚችሉ የተናጋሩት የፓርቲው ተወካይ፤ ማሽኑን ከሀገር ውስጥ መግዛት ያስፈለገበት ምክንያት ከውጭ ተገዝቶ ሲገባ ያለውን ረጅም ጊዜ ለመቀነስና ማሽኑን በተመጣጣኝ ዋጋ ለመግዛት እንደሆነ ገልፀዋል፡፡