Saturday, 17 August 2013 11:11

ድምፃዊ ኢዮብ መኮንን ሆስፒታል ገባ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(9 votes)

ለተጨማሪ ህክምና ዛሬ ወደ ኬኒያ ይሄዳል
“አንድ ቃል” በተሰኘው የመጀመሪያ አልበሙ ተወዳጅነትንና እውቅናን ያተረፈው ድምፃዊ ኢዮብ መኮንን፣ “ስትሮክ” ተብሎ በሚታወቀው ህመም ቅዱስ ገብርኤል ሆስፒታል የገባ ሲሆን ለተጨማሪ ህክምና ወደ ኬንያ ይሄዳል ተብሏል፡፡ በጅጅጋ ከተማ ተወልዶ ያደገው የ38 ዓመቱ ድምፃዊው፤ በቅዱስ ገብርኤል ሆስፒታል ኢንቴንሲቭ ኬር ዩኒት (ICU) ውስጥ በህክምና ላይ እንደሚገኝ ባለቤቱ ወ/ሮ ቲና ተአረ ተናግራለች፡፡ 
ትላንትና ረፋዱ ላይ በሆስፒታሉ ያገኘናት ባለቤቱ ወ/ሮ ቲና፣ ማክሰኞ ጠዋት የእህቱን ልጅ ት/ቤት አድርሶ ከተመለሰ በኋላ የቤቱን መጥሪያ እንደተጫነ መውደቁንና በድንጋጤ ወደ ሆስፒታል ይዘውት እንደመጡ ገልፃለች፡፡
“ከዚህ በፊት የከፋ ህመም አጋጥሞት አያውቅም፣ ባለፈው እሁድም ኮሌስትሮልን ጨምሮ ጠቅላላ የጤና ምርመራ አድርጓል” ብላለች፡፡ ኢዮብ ለተጨማሪ ህክምና ዛሬ ወደ ኬኒያ እንደሚሄድም ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ ይሁን እንጂ ከመጀመሪያው አሁን የጤና መሻሻል እንዳለው ባለቤቱ ተናግራለች፡፡

Read 23028 times