Saturday, 10 August 2013 10:34

በኢድ ተቃውሞ ከ2ሺ በላይ ሰዎች ታስረዋል

Written by  ሰላም ገረመው
Rate this item
(12 votes)

በፖሊስና ተቃውሞ ባሰሙ ወጣቶች በተፈጠረው ግጭት በርካቶች ቆስለዋል
በበርበሬ ተራ አካባቢ የነበረው ግጭት ከፍተኛ ነበር

በአወሊያ ት/ቤት በእስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ዙሪያ፣ ከዚያም አልፎ በአክራሪነትና በሃይማኖት ነፃነት ጉዳይ፣ ሲብስም የፖለቲካ ጥያቄዎች እየተጨመሩበት ሲብላላ የቆየው አለመግባባት ወደ ግጭት የተሸጋገረው ከአመት በፊት የረመዳን የፆም ወቅት ቢሆንም፤ ባለፈው ሃሙስ እለት የኢድ በዓል ላይ የተፈጠረው ግጭት ብዙ ሰዎችን ለጉዳት የዳረገና ከሁለት ሺ በላይ ሰዎች የታሰሩበት ሆኗል፡፡ 
ሃሙስ ጠዋት በአዲስ አበባ ስታዲየም እና በዙሪያው ባሉ ጎዳናዎች የተከበረው የኢድ በዓል ላይ የተቃውሞ እንቅስቃሴ እንደሚካሄድ ቀድሞም ሲጠበቅ የነበረ ነው፡፡ የተቃውሞ እንቅስቃሴው አስተባባሪዎች በበራሪ ወረቀትና በኢንተርኔት የተቃውሞ ጥሪ ሲያስተላልፉ ሰንብተዋል፡፡ በስታዲየምና በዙሪያው የኢድ በዓል ስነ ስርዓት እንደተጠናቀቀ፣ የተቃውሞ አስተባባሪዎች ድምፅ የተሰማው ስታዲየሙ ውስጥ ሲሆን፣ በየአካባቢውና በዙሪያው ባሉ ጎዳናዎች ተስፋፍቶ ተስተጋብቷል፡፡

አጀማመሩ ላይ ግጭት አልተፈጠረም፡፡ የተቃውሞ ድምፅ እያሰሙ የሚጓዙትና በየአቅጣጫው የተሰማሩ ፖሊሶች ሲገጣጠሙ ነው ግጭት የተፈጠረው፡፡ በተለይ ከስታዲየም ወደ ሲኒማ ራስና አውቶቡስ ተራ፣ ወደ ፒያሳና መርካቶ፣ ወደ ባምቢስና ፍላሚንጎ በሚወስዱ አቅጣጫዎች ከተፈጠሩት ግጭቶች ሁሉ ወደ መርካቶና አውቶቡስ ተራ በሚወስደው በርበሬ ተራ አካባቢ የነበረው ለበርካታ ሰዓታት የዘለቀና የከፋ ነው፡፡
በየቅያሱና በየሰፈሩ ጭምር ዱላ በያዙ ፖሊሶችና ድንጋይ በሚወረውሩ አካባቢው ተረብሾ የዋለ ሲሆንና በየጎዳናው ላይ የሚታየው ትዕይንት የግጭቱን ስፋት ያሳያል፡፡
የተወረወሩ ድንጋዮች መንገዱን ሸፍነውታል፡፡ በፖሊስ የተደበደቡ ወይም በድንጋይ የተፈነካከቱም ሞልተዋል፡፡
በረብሻው ወቅት ከየአቅጣጫው በፖሊስ እየተያዙ የሚመጡ ሰዎች ትንሿ ስታዲየም ውስጥና ፖስታ ቤት አካባቢ ባለው ፓርክ ውስጥ ነበር ታስረው እንዲቆዩ የተደረገው፡፡ ችግር ፈጥረዋል ተብለው በሁለት ቦታዎች ተይዘው የነበሩ ሰዎች ቁጥር 3ሺ ይደርሳሉ ተብሎ የሚገመት ሲሆን ከፊሎቹ አመሻሽ ላይ ተለቀዋል፡፡ ቀሪዎቹ ግን በየክፍለ ከተማው በእስር እንዲያድሩ ተደርጓል፡፡ ባለፉት ሳምንታት መጀመሪያ በአንዋር መስጊድ ከዚያም በቦኒ መስጊድ እና በቶፊክ መስጊድ ሦስት ተቃውሞዎች መካሄዳቸው ይታወሳል፡፡
“የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች ይፈቱ”፣ “የደሴው ሼህ ግድያ ድራማ ነው”፣ “መጅሊሱ (ምክር ቤቱ) እኛን አይወክልም”፣ “ምርጫው ፍትሀዊ አይደለም”፣ “በ22 ዓመታት ውስጥ ኢትዮጵያን ያስተዳደረ ሙስሊም የለም”፣ “አህበሽ የተባለው አስተሳሰብ ይቅር”፣ “መንግስት በሀይማኖት ጣልቃ አይግባ”፣ “አወሊያ የሙስሊሙ ተቋም ነው” የሚሉ ጥያቄዎችና መፈክሮች ሲስተጋቡም ቆይቷል፡፡

Read 35499 times