Saturday, 27 July 2013 14:40

“የድንቂቱ ኢትዮጵያ ድንቃድንቆች” ይመረቃል

Written by 
Rate this item
(2 votes)

በህንዳዊው መምህርና ፀሐፊ ሚ/ር ጆሴፍ ፍራንሲስ የተዘጋጀ “የድንቂቱ ኢትዮጵያ ድንቃድንቆች” (“This is Ethiopia – A Book of Fascinating Facts”) የተሰኘ ስለ ኢትዮጵያ የተለያዩ ድንቅ መረጃዎችን ያካተተ አዲስ መፅሐፍ የፊታችን ረቡዕ ከምሽቱ 12 ሰዓት ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉጌታ ሰኢድ ዳምጠው በተገኙበት በካፒታል ሆቴል ይመረቃል፡፡
መፅሐፉ፤ ኢትዮጵያን ልዩ የሚያደርጋትን ከ245 በላይ መረጃዎች ያካተተ ሲሆን የተዘጋጀበትም ዓላማ፤ በተለይ የውጭ አገር አንባቢያንና ዳያስፖራዎች፣ ስለ ኢትዮጵያ መረጃዎችን በቀላሉና በአጭሩ እንዲቀስሙ ለማድረግ ነው ተብሏል፡፡ በመፅሐፉ ጀርባ ላይ አስተያየታቸውን ያሰፈሩት የታሪክ ባለሙያው ፕ/ር ሪቻርድ ፓንክረስት፤ “ስለ ኢትዮጵያ ብዙ የማናውቃቸው አስደናቂ ነገሮች መኖራቸውን… መፅሃፉ እንድንገነዘብ ያደርገናል፡፡ መፅሃፉ ያካተታቸው መረጃዎች ብዙ አንባቢዎችን ሊያስደምሙ የሚችሉ ናቸው” ብለዋል፡፡
መፅሃፉ በእንግሊዝኛና በአማርኛ የተዘጋጀ ሲሆን ትርጉሙን የሰራው ደራሲ አማረ ማሞ ነው፡፡ የውስጥ ገፆቹ ሁሉ ባለቀለም ሆነው የተዘጋጀው “የድንቂቱ ኢትዮጵያ ድንቃድንቆች” መጽሐፍ መረጃዎች በተዋቡ ምስሎች ተደግፈው ቀርበውበታል፡፡ ላለፉት 30 ዓመታት ኢትዮጵያ ውስጥ በመምህርነት ያገለገለው ሚ/ር ጆሴፍ ፍራንሲስ፤ ከዚህ ቀደም “የአድዋ ጦርነት”፣ “ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ” እና “የአፄ ቴዎድሮስ ልጅ፣ ልዑል ዓለማየሁ” የተሰኙ የልጆችና ወጣቶች መፃህፍትን አሳትሟል፡፡

Read 3976 times