Saturday, 06 July 2013 11:02

ወሎ ውስጥ በ1ቢ ብር ወጪ ሆስፒታል ሊገነባ ነው

Written by 
Rate this item
(4 votes)

በአንድ ቢሊዮን ብር ወጪ በደሴ ከተማ ውስጥ ይገነባል ለተባለው የወሎ ተርሸሪ ኬርና ቲቺንግ ሆስፒታል ግንባታ የሚውል ገቢ የማሰባሰብ ሥራ በይፋ ተጀመረ፡፡ ለሆስፒታሉ ማሰሪያ የሚሆን ገቢ የማሰባሰቡ ሥራ ባለፈው ረቡዕ በሸራተን አዲስ በይፋ በተከፈተበት ወቅት እንደተገለፀው፤ ሆስፒታሉ በብሔራዊ ደረጃ ከፍተኛ የህክምና ተቋም እንዲሆን ከማድረጉ በተጨማሪ የስልጠናና የምርምር ማዕከል ይሆናል፡፡ ከ750 በላይ አልጋዎች ይኖሩታል ለተባለው ለዚህ ሆስፒታል ግንባታ፤ የወሎ ተወላጆች የሆኑ ባለሀብቶችና በውጭ አገር የሚኖሩ የአካባቢው ተወላጆች ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደርጋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም በዚሁ ወቅት ተገልጿል፡፡

የኢፌዲሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የትምህርት ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንንን ጨምሮ የክልሉ ተወላጆች የሆኑ ታላላቅ የመንግስት ባለስልጣናት በተገኙበት በሸራተን አዲስ በተካሄደው ፕሮግራም ላይ እንደተገለፀው፤ በመጪው ዓመት የሆስፒታሉ ግንባታ የገቢ ማሰባሰቢያ ዓመት እንዲሆን እቅድ ተይዟል፡፡ የደሴ ከተማ አስተዳደር ጢጣ በተባለው ሥፍራ ለሆስፒታሉ ግንባታ የሚውል 40 ሄክታር መሬት የሰጠ ሲሆን የሆስፒታሉ የመሰረት ድንጋይም ህዳር 16 ቀን 2004 ዓ.ም የኢፌዲሪ ምክትል ጠቅላይ ሚ/ር እና የትምህርት ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን፣ የአማራ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ አያሌው ጐበዜና የፕሮጀክቱ የበላይ ጠባቂ ሼክ አሊ መሐመድ ሁሴን አልአሙዲ በተገኙበት መቀመጡ የሚታወስ ነው፡፡

Read 3521 times