Print this page
Saturday, 06 July 2013 10:46

ፈርጅ ያለው ነጠላ አሰርቼ መልክ የሌለው ሰው ይለብሳል

Written by 
Rate this item
(5 votes)

ከነአያ አንበሶ በታች ያሉት የዱር አራዊት ሁሉ ተሰብስበው ትልቅ ግብዣ ተደረገና ዳንሱ፣ ጭፈራው፣ ዳንኪራው ቀለጠ! ደራ!
ከደናሾቹ መካከል ጥንቸል ተነስታ፤
“ዝም ብለን ከምንደንስ እንወዳደርና ምርጥ ዳንሰኛው ይለይ!” አለችና ሃሳብ አቀረበች፡፡
በሃሳቡዋ ሁሉም ተስማሙና ጭፈራው ቀጠለ፡፡ ሁሉም በተራ በተራ ወደ መድረክ እየወጣ ችሎታውን አሳየ፡፡
በመጨረሻ ዳኞች ተሰይመው ውጤት ተነገረ፡፡ በውጤቱ መሰረት አንደኛ - ዝንጀሮ፣ ሁለተኛ ቀበሮ፣ ሶስተኛ - ጦጣ ሆኑ፡፡
ዝንጀሮ መመረጡን በማስመልከት መድረክ ላይ ወጥቶ ተጨማሪ ዳንስ በማሳየት ታዳሚዎቹን አራዊት አዝናና፡፡ ንግግርም አደረገ፡፡
አራዊቱ በጣም በመደሰት ንጉሣችን ይሁን ብለው ወሰኑ፡፡
በዝንጀሮ ንጉሥ መሆን ቀበሮና ጦጣ ቅናት እርር ድብን አደረጋቸው፡፡ ስለዚህ መዶለት ጀመሩ፡፡
ጦጣ፤ “አያ ቀበሮ መቼም ከዳኝነት ስተት ነው እንጂ ዝንጀሮ ከእኛ በልጦ አይመስለኝም፡፡ አንተስ ምን ይመስልሃል?”
ቀበሮም፤
“እኔም እንዳንቺው ነው የማስበው፡፡ የዘመድ ሥራ ነው የተሰራው፡፡ ግን አንዴ ሆኗል ምን ይደረጋል?”
ጦጣ፤ “አንዴ ሆኗል ብለንማ መተው የለብንም”
ቀበሮ፤ “ምን እናደርጋለን ታዲያ?”
ጦጣ፤ “እኔ ወጥመድ ላዘጋጅ፡፡ አንተ እንደምንም ብለህ ወጥመዱጋ አምጣልኝ” አለችው፡፡ “ወጥመድ ላይ ሥጋ አድርጌ እጠብቃችኋለሁ፡፡ አንተ ዝንጀሮን ትጋብዘዋለህ”
ቀበሮ በሃሳቡ ተስማምቶ ዝንጀሮን ሊያመጣው ሄደ፡፡
ዝንጀሮ በአዲስ የሹመት ስሜት እንደሰከረ፤ እየተጐማለለ ይመጣል፡፡
“ይህን የመሰለ ሙዳ ሥጋ አስቀምጬልሃለሁ” አለው ወደ ሥጋው እያሳየው፡፡
ዝንጀሮም፤ “አንተስ? ለምን አልበላኸውም?” ይሄን የመሰለ ሙዳ እንዴት ዝም አልከው?” አለው፡፡
ቀበሮ፤ “ውድ ዝንጀሮ ሆይ! ለንግሥናህ ክብር ይሆን ዘንድ ብዬ ያዘጋጀሁት ነውና ስጦታዬን ተቀበለኝ?” አለው እጅ በመንሳት፡፡
ዝንጀሮ “ስጦታህን ተቀብያለሁ፤” ብሎ ወደወጥመዱ ዘው አለ፡፡ እዚያው ታስሮ ተቀረቀረ!!
ተናደደ!! በምሬትና በቁጭት በደም ፍላት ተናገረ፤
“ለዚህ አደጋ ልትዳርገኝ ነው ለካ ያመጣኸኝ? አንት ሰይጣን! ለንዲህ ያለ ወጥመድ ነበር ለካ ስታባብለኝ የነበረው? አረመኔ!” አለው፡፡
ቀበሮም፤ እየሳቀ፤
“ጌታዬ ዝንጀሮ ሆይ! የአራዊት ንጉሥ ነኝ እያልክ፤ ግን እቺን ቀላል አደጋ እንኳን ማለፍ አልቻልክም!” ይሄ የመጀመሪያ ትምህርት ይሁንህ ብሎ ጥሎት ሄደ፡፡
***
“ሹመት ያዳብር” የሚለውን ምርቃት የሀገራችን ህዝብ ጠንቅቆ ያቃል፡፡ በልቡ ግን “አደራዬን ተቀበል” የሚል ጠንካራ ማስጠንቀቂያና ጠንካራ መልዕክት ልኮ ማስገንዘቡ ነው፡፡ ካልሆነ አደራ በላ ትሆናለህ!
አደራ! ሲባል፤ የመብራት የውሃዬን ነገር አደራ ማለቱ ነው፡፡
አደራ! ሲባል፤ የትምህርትን ነገር ጠንቅቀህ ምራ ማለት ነው፡፡ ውስጡን በደምብ መርምር ማለት ነው፡፡
አደራ ሲባል፤ የኢንዱስትሪውን ሂደት፤ የትራንስፖርቱን (የባቡሩን፣ የመኪናውን፣ የአየሩንና የእግሩን ጉዞ) ነገር በቅጡ በቅጡ ያዙት ማለት ነው፡፡ የአካባቢ ጥበቃውንና የሳይንስና ቴክኖሎጂው ጉዳይ ዕውነተኛ አሠራር፣ ብስለትና ከዓለም ጋር የሚሄድ እንዲሆን ማድረግ ዋና ነገር ነው ማለት ነው፡፡
አደራ! ሲባል በተለይ የገቢዎችን ነገር፣ እከሌ ከእከሌ ሳትሉ ኢወገናዊ በሆነ ዐይን በማየት፤ የታረመ፣ የተቀጣ፣ ከስህተቱ የተማረ አካሄድ እንድትሄዱ ማለት ነው፡፡
አደራ ሲባል በአጭሩና በጥብቁ ቋንቋ
“አደራ - በላ አትሁኑ” ማለት ነው፡፡
በተለምዶ እኛ አገር “ባለፈው ሥርዓት” የሚል ፈሊጥ አለ፡፡ “ያለፈው ሹም ጥፋተኛ ነበር፣ ደካማ ነበር እኔ ግን አንደኛ ነኝ…” ዓይነት አንድምታ ያለው ነው ያለፈው ሹም የበደላችሁን እኔ እክሳለሁ! እንደማለትም አለበት፡፡ ይህን እንጠንቀቅ፡፡
የተሻሪም የተሿሚም ሂደት ተያያዥ ሥርዓት ነውና ሰንሰለቱ ተመጋጋቢ ነው፡፡ እንጂ የወረደው ጠፊ፣ የተሾመው ነዋሪ ነው ማለት አይደለም፡፡ በቅንነት፣ በሰብዓዊነት፣ በለሀገር አሳቢነት ካላየነው፤ ሁሉም ነገር ከመወነጃጀል አይወጣም፡፡ በተሰበሰበ ቀልብ፣ በሙያ ክህሎትና በዲሞክራሲያዊ አረማመድ ነው ፍሬያማ ለመሆን የሚቻለው፡፡ ያንን ካልተከተልን “ንጉሥ ነኝ እያልክ ይቺን ቀላል አደጋ እንኳን ለማለፍ አቃተህ” እንባባላለን፡፡
ጐባጣውን የምናቃናው፣ ጐዶሎውን የምንሞላውና የምናስተካክለው፤
መዋቅር የምናጠናክረው፣ እዚህጋ ተሳስተናል እንተራረም የምንባባለው፤ ለሀገር ይበጃል፣ ብለን ነው፡፡ የሾምነውና ያስቀምጥነው ሰው ተስተካክሎ የተበጀውን ሥርዓት ለግል ጥቅሙ ካዋለ፤ አደራውን ከበላ፣ አድሎኛ ከሆነ፣ በመጨረሻም ያለውን ሁኔታ ከመጠበቅ አልፎ በማሻሻል፤ ለውጥ ካላመጣ፣ የወላይትኛው ተረት እንደሚለው፤ “ፈርጅ ያለው ነጠላ አሰርቼ፤ መልክ የሌለው ሰው ይለብሳል” ሆነ ማለት ነውና ከወዲሁ እንጠንቀቅ፡፡ “ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል”ን እንዋጋ!
“ሸክላ ሲሰበር ገል ይሆናል፡፡ መኳንንትም ሲሻሩ ህዝብ ናቸው” የሚለውንም አንዘንጋ!

Read 3744 times
Administrator

Latest from Administrator